ኢትዮጵያ በስንዴ ምርትና በአረንጓዴ ሌጋሲ እያስመዘገበች ያለው ውጤት ዓለምን ከማስደነቅ አልፎ ምስላኤ እያደረጋት ኢሆንም፣ በብሄር ፖለቲካ ላበዱ ሚዲያዎች ዜናው ዜና አለመሆኑ በርካቶችን የሚያስገርም ጉዳይ ሆኗል። ተሰምቶ በማይታውቅ ደረጃ ኢትዮጵያ በበጋ መስኖ 120 ሚሊዮን ኩንታል ስንዴ ለማምረት እየሰራች መሆኗና ላለፉት ሁለት ዓመታት ለስንዴ ግዢ አንድ ብር ከካዝናዋ አለመንካቷ ለመላው ኢትዮጵያዊያን ኩራት ሊሆን በተገባ ነበር።
የሚመረተውን ምርት ወደ ገባያ በማውጣት የተፈጠረውን የኑሮ ውድነት ለማረጋጋት መንቀሳቀሱ ላይ ትኩረት እንዲደረግ፣ በንግድ አሻጥር ላይ የተሰማሩትን በማጋለጥ ዘንዳ ሚዲያዎች ድጋፍ ማድረግ ይገባቸው እንደነበር በርካቶች በግርምት ይገልጻሉ። መልካም ስራን አድንቆ ጥፋትን ነቅሶ የማሳየትና የመተቸት ባህል የነተፈበት የአገራችን ሚዲያ የርሃብና ልመና ታሪክን ሊያስወግድ የሚችል ዘመቻን ቸላ ማለታቸው የሚገስገርማቸው ” ለኢትዮጵያ ሚዲያዎች ሞት፣ስደት፣ ውድመትና ጦርነት ብቻ ነው ወይ ዜናቸው” ሲሉ ይጠይቃሉ።
የታቀደው 120 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ሲሆን የመሰብሰብ ሂደቱ በፍጥነት እየተሰራ ነው። ከ58 ሚሊዮን ኩንታል በላይ የተገኘው ከአንድ ነጥብ 7 ሚሊዮን ሄክታር መሬት ላይ ብቻ ነው። በዘር የተሸፈነው ከ3 ሚሊዮን ሄክታር በላይ ሲሆን የምርት ማሰባሰቡ ስራ ሲጠናቀቅ 120 ሚሊዮን ኩንታል ስንዴ ተጠቃሎ ገቢ ይሆናል
በበጋ መስኖ ስንዴ እስካሁን ከአንድ ነጥብ ሰባት ሚሊዮን ሄክታር መሬት ላይ ምርት መሰብሰብ እንደተቻለ ግብርና ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡ ከተሰበሰበው ምርት ከ58 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት እንደተገኘም ተገልጿል፡፡
በግብርና ሚኒስቴር የሕዝብ ግንኙነትና ኮሙኒኬሽን ሥራ አስፈጻሚ አቶ ከበደ ላቀው ለኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት እንደገለጹት፤ በበጋ መስኖ ስንዴ ልማት ሦስት ሚሊዮን ሄክታር መሬት ታርሶ በስንዴ ዘር የተሸፈነ ሲሆን ምርቱ በመሰብሰብ ላይ ይገኛል፡፡ ወደ 120 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ለማግኘት ታቅዶ በሰፊ ርብርብ ሲሰራ መቆየቱን አቶ ከበደ ተናግረዋል፡፡ እስካሁን በተደረገው እንቅስቃሴም አንድ ነጥብ ሰባት ሚሊዮን ሄክታር መሬት ላይ ያለ የበጋ መስኖ ስንዴ ምርት መሰብሰቡን ጠቅሰዋል፡፡
እንደ ሥራ አስፈጻሚው ገለጻ፤ እስከ መጋቢት 30 ቀን 2016 ዓ.ም በተደረገው አጠቃላይ እንቅስቃሴ በባህላዊ መንገድ ወደ አንድ ነጥብ ሁለት ሚሊዮን ሄክታር፣ በኮምባይነር ከ431 ሺህ ሄክታር መሬት በላይ በድምሩ አንድ ነጥብ 7 ሚሊዮን ሄክታር መሬት ላይ ያለ የበጋ መስኖ ስንዴ በመሰብሰብ 58 ነጥብ አምስት ሚሊዮን ኩንታል ምርት ማግኘት ተችሏል፡፡
የመሰብሰብ ሥራውም ተጠናክሮ ቀጥሏል፡፡ የበጋ መስኖ ስንዴ የግብርና ምርትን በአይነትና በመጠን እንዲያድግ ከማድረግ አንጻር ከፍተኛ ሚና እንዳለው ጠቅሰው፤ ሥራው ከሀገራዊ ለውጡ ወዲህ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ አማካኝነት እንደተጀመረና
በስፋት በማምረት የሕዝቡን የምግብ ሥርዓት ለማሻሻል እየተሠራ እንዳለ ገልጸዋል፡፡ ልማቱ ከለውጡ ማግስት ከተጀመረ ጊዜ ጀምሮ አሁን ላይ የስንዴ ፍላጎትን በሀገር ውስጥ የመሸፈን አቅም መፈጠሩንም ሥራ አስፈጻሚው ገልጸዋል፡፡
የሚያስፈልገውን የስንዴ ምርት በመኸርና በበጋ መስኖ ማምረት ተችሏል በማለት፤ የሁለቱ ወቅቶች ምርት ተደምሮ አጠቃላይ በሀገር ውስጥ የሚያስፈልገው የስንዴ ፍላጎት እየተሟላ መሆኑን አመላክተዋል፡፡ ይህ በቀጣይ ተጠናክሮ ሲቀጥል ደግሞ ወደ ውጪ በሰፊው ኤክስፖርት የማድረግ እድሉ እየሰፋ እንደሚሄድም ነው የተናገሩት፡፡
የበጋ ስንዴ ኢትዮጵያ በምግብ ሉዓላዊነቷን ለማስከበር ከምታደርጋቸው ጥረቶች አንዱ አካል መሆኑንም ሥራ አስፈጻሚው ጠቅሰዋል፡፡ በግብርናው ዘርፍ እቅድ ተይዞባቸው የሚሰሩት ስንዴ፣ ሩዝ፣ አረንጓዴ አሻራ እና የእንስሳት እርባታ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማስጠበቅ የሚሠሩ መሆናቸው ተናግረዋል፡ ፡
የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት በተያዘለት የበጋ ወራት በፍጥነትና በጥራት እንዲጠናቀቅ ከመንግሥት ከፍተኛ አመራር እስከ ባለሙያው ድረስ ሥራው በመናበብ እየተሠራ እንዳለ ገልጸዋል፡፡