ETHIO12.COM

ቴሌና ሳፋሪኮም በማያውቁት ኔትዎርክ የቴሌኮም ወንጀል ሲፈጽሙ የነበሩ 30 ግለሠቦች እጅ ከፍንጅ ተያዙ፤ የደህንነት ስጋትም ነበር

መሳሪያዎቹ በሕገወጥ መንገድ ወደ ኢትዮጵያ የሚገቡ ሲሆን ከኢትዮቴሌኮምም ይሁን ከሳፋሪኮም ምንም እውቅና የሌላቸው ነገር ግን ከውጭ ሀገር ወደ ኢትዮጵያ የሚደረጉ የስልክ ጥሪዎችን ኢትዮ ቴሌኮም ወይም ሳፋሪኮም በዘረጋው ኔትወርክ ሳይሆን ራሳቸው በዘረጉት የማጭበርበሪያ ጌትዌይ ለደንበኞች የሚያቀርቡ መሆናቸውን መግለጫው አመልክቷል

በአዲስ አበባ፣ ሸገር ከተማ፣ ቢሾፍቱ፣ ሞጆ፣ አዳማ፣ ሐዋሳ እና ጂማ ከተማ በተደረገ የተቀናጀ ኦፕሬሽን ከ73 በላይ የቴሌኮም ማጭበርበሪያ መሣሪያ እንዲሁም 30 ተጠርጣሪ ግለሠቦች እጅ ከፍንጅ በቁጥጥር ሥር እንዲውሉ መደረጉ ተገልጿል፡፡

የኢንፎርሜሽን መረብ ደኅንነት አስተዳደር ከብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት እና ከፌደራል ፖሊስ ጋር በመተበበር እንዲሁም ከቴሌኮም አገልግሎት ሰጭ ተቋማት ባለሙያዎችና ከማኅበረሰቡ ጋር በመቀናጀት ላለፉት 3 ወራት በቴሌኮም ማጭበርበር ወንጀል ተዋንያን ላይ ጥብቅና ምስጢራዊ ክትትል ሲያደርጉ መቆየታቸውን ተቋማቱ ግኝቱን አስመልክተው ለመገናኛ ብዙኃን በላኩት መገለጫ አስታውቃዋል፡፡

ተጠርጣሪዎቹ የግለሠብ ቤቶችን በመከራየት የማጭበርበሪያ መሳሪያዎችን ተጠቅመው ወንጀሉን ሲሰሩ መቆየታቸው በመግለጫው ተጠቅሷል፡፡ ለዚሁ ሕገ ወጥ ተግባር ሲውሉ የነበሩ ከ200 ሺህ በላይ የሳፋሪኮምና ኢትዮቴሌኮም ሲም ካርዶችም ተይዘዋል ተብሏል፡፡

በቁጥጥር ስር ከዋሉ የማጭበርበሪያ ጌትዌይ መካከልም በ1 ጊዜ 127 የኢትዮቴሌኮም ወይም ሳፋሪኮም ሲም ካርድ መያዝ የሚችል መሣሪያ መገኘቱም ተገልጿል፡፡

በመሳሪያዎቹ አማካኝነት የሚፈጸሙት የማጭበርበር ድርጊቶች ኢትዮጵያ ከዓለም አቀፍ የቴሌኮም አገልግሎት ማግኘት የሚገባትን የውጭ ምንዛሪ ያሳጣልም ነው የተባለው፡፡ ኢትዮቴሌኮምና ሳፋሪኮም ባለፉት 6 ወራት ብቻ በዚህ ሕገ ወጥ ተግባር ከ500 ሚሊየን ብር በላይ ማጣቱንም ተቋማቱ በሰጡት በግለጫ አስታውቀዋል፡፡ በማጭበርበሪያ መሳሪያዎች የተነሳ በቴሌኮም አገልግሎት አሰጣጥ ላይም አሉታዊ ተጽዕኖ እንደሚፈጥር ተጠቁሟል፡፡

መሳሪያዎቹ በሕገወጥ መንገድ ወደ ኢትዮጵያ የሚገቡ ሲሆን÷ከኢትዮቴሌኮምም ይሁን ከሳፋሪኮም ምንም እውቅና የሌላቸው ነገር ግን ከውጭ ሀገር ወደ ኢትዮጵያ የሚደረጉ የስልክ ጥሪዎችን ኢትዮ ቴሌኮም ወይም ሳፋሪኮም በዘረጋው ኔትወርክ ሳይሆን ራሳቸው በዘረጉት የማጭበርበሪያ ጌትዌይ ለደንበኞች የሚያቀርቡ መሆናቸውን መግለጫው አመልክቷል፡፡

በማጭበርበሪያ መሳሪያው የሚፈጸመው ሕገወጥ ድርጊት ሀገራዊ ጥቅምን ከማሳጣትና የደኅንነት ሥጋት ከመደቀን ባሻገር የቴሌኮም ደንበኞች በሚፈጠረው የትራፊክ መጨናነቅ ጥራት ያለው የኔትዎርክ አገልግሎት እንዳያገኙ ያደርጋልም ተብሏል፡፡

በዚህም ደንበኞች በቴሌኮም አገልግሎት ሰጪ ተቋማት እንዲሁም በመንግሥት እንዲማረሩና ሀገራዊ መረጋጋት እንዳይኖር አስተዋጽኦ ማበርከቱን መግለጫው አስታውቋል፡፡

በማጭበርበር ወንጀሉ ላይ የሚሳተፉ ግለሠቦች ሰፊ ኔትዎርክ እንዳላቸው የተገለጸ ሲሆን÷ከዓለም ዓቀፍ ተዋንያን እስከ ሀገር ውስጥ ቤት አከራይ ድረስ ትስስር መፍጠራቸውን የተቋማቱ መግለጫ አስታውቋል፡፡

የማጭበርበሪያ መሳሪያ ከጎረቤት ሀገራት በድንበር በኩል እስከ መሀል ከተማ ድረስ የሚቀባበሉ ደላሎች፣ በርካታ የኢትዮቴሌኮምና ሳፋሪኮም ሲም ካርድ እንዲሁም ሞባይል ካርድ ለእነዚህ አጭበርባሪዎች የሚያደርሱ ተባባሪ ወንጀለኞች እንደሚገኙበት ተመላክቷል፡፡

ተጠርጣሪዎች መቀመጫቸውን ኬንያ፣ ሶማሊያ እና ሌሎች ሀገራት ካደረጉ ዜጎች ጋር በመመሳጠር እና ተቀጥረው በመሥራት ተሳትፎ ሲያደርጉ እንደተደረሰባቸውም መግለጫው ጠቁሟል።

በኦፕሬሽኑ በተያዙት መሳሪያዎች እና በተጠርጣሪዎች ላይ የፌደራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ቀጣይ ምርመራውን አጠናክሮ በመቀጠል በቀጣይ ለሕዝብ የማሳወቅ ሥራ የሚያከናውን ይሆናልም ተብሏል፡፡

ሁሉም አካላት እነዚህና ሌሎችም መሰል ወንጀሎች ከጸጥታ እና ደኅንነት ተቋማት እይታ እንደማይሰወሩ ተገንዝበው ከሕገወጥ እንቅስቃሴ ሊቆጠቡ ይገባልም ተብሏል።

ህብረተሰቡ በወንጀል የሚሳተፉ ግለሠቦችና ተቋማት መኖራቸውን ጥርጣሬ ሲያድርበት በአካባቢው ለሚገኙ የጸጥታ አካላት ጥቆማውን በማቅረብ ሕገወጦችን ለመከላከል በሚደረገው ጥረት የበኩሉን አስተዋጽኦ አጠናክሮ እንዲቀጥልም ተቋማቱ አሳስበዋል፡


Exit mobile version