Site icon ETHIO12.COM

ኦሮሚያ ክልል ለጤና ጣቢያዎች አንድ ሺህ ሃኪሞችን ለመቅጠር ማስታወቂያ ቢያወጣም ተመዝጋቢ ጠፋ

የኦሮሚያ ክልል ጤና ቢሮ አንድ ሺህ አንድ መቶ ሀኪሞችን ለመቅጠር ባለፈዉ ዓመት ሰኔ ወር 2015 ዓ.ም ያወጣውን ማስታወቂያ ተከትሎ ተመዝጋቢ ስራ ፈላጊ ሃኪሞች ባለማግኘቱ በጀቱን ማዛወሩን አስታወቀ። ሃኪሞች ከተመረቁ በሁዋላ ስራ ማጣታቸው በተደጋጋሚ የሚገለጸውን ሮሮ እንደነበር ይታወሳል።

“ቢሮው ማስታወቂያ ቢያወጣም ተቀጣሪዎችን ባለማግኘቱ በጀቱን ወደ ሌላ ዘረፍ ማዛወሩን ለኢትዮ ኤፍ ኤም አስታዉቋል” ሲል ገጹ እንዳስታወቀው ክልሉ የሃኪሞች እጥረት እንዳለበት ሃላፊው አስታውቀዋል።

የቢሮዉ ምክትል ሃላፊ ዶ/ር ጉሻ በለኮ በሰኔ 2015 ላይ 1ሺህ 1መቶ ሀኪሞችን ለመቅጠር ማስታወቂያ የወጣ ቢሆንም ተቀጣሪዎችን ባለማግኘቱ ቢሮዉ በጀቱን ለሌላ ጉዳይ ማዋሉን ቢያስታውቁም አሁንም ከተገኘ ሃኪም መቅጠር እንደሚፈልጉ ገልጸዋል። ይሁን እንጂ በምን ምክንያት ገበያው ላይ ሃኪም ማግኘት እንዳልተቻለ አላብራሩም። “ለሁለት ወራት ያክል ማስታወቂያዉን ክፍት ባደርግም ገበያ ላይ ተቀጣሪዎችን አላገኘሁም” ከማለት ውጭ ዝርዝር አላቀረቡም።

በክልሉ በተያዘው አሰራር በየአንዳንዱ ጤና ተቋም ሀኪሞች መኖር አለባቸው። በዚሁ መሰረት በገጠር ጤና ተቋማት ሃኪሞችን መድቦ ለማሰራት ማስታወቂያ ቢወጣም ሀኪሞችን ማግኘት አልተቻለም። በዚህም ሳቢያ በምትኩ የጤና ኤክስቴንሽን ባለሙያዎችን፣ አዋላጆችን እና ነርሶችን ለመቅጠር መገደዳቸውን ሃላፊው ገልጸዋል፡፡

“ከዚህ በፊት ለመላዉ ኦሮሚያ አገልግሎት የሚሰጡ የጤና ባለሙያዎች ቁጥር 72ሺህ ነበር” ያሉት ሃላፊዉ አሁን ላይ ቁጥሩ ወደ 85ሺህ ከፍ ማለቱን ግልጸዋል፡፡

“በተቻለን አቅም ማስታወቂያ አዉጥተን ገበያ ላይ የነበሩትን ለመዉሰድ ሞክረናል። ነገር ግን አሁንም የሀኪሞች ዕጥረት አለብን” ያሉት ሃላፊው፣ “ማስታወቂያዉን አይተዉ የመጡትን እንቀጥራለን ፤ካልመጡ ግን ገበያዉ ላይ የሰዉ ሃይል እንደሌለ ነዉ የሚቆጠረዉ” ብለዋል። ይህ ንግግራቸው “ተመርቀው ስራ አላገኙም፣ አይ ይህቺ አገር” በሚል ሲወቅሱና ሲያማርሩ የነበሩ አካላትን መረጃ ጥያቄ ውስጥ የሚጥል ሆኗል።

ሃላፊዉ በተጨማሪም ባለፈዉ ዓመት ሃኪሞችን ለመቅጠር ባወጣነዉ ማስታወቂያ ሀኪሞችን ማግኘት ስላልቻልን ወደ 7 መቶ አከባቢ የሚሆኑ የተለያዩ ባለሙያዎችን ቀጥረናል ሲሉም ነግረዉናል፡፡

ከኦርሚያ ብቻ ሳይሆን ከተለያዩ አካባቢ አስተዳእሮች እንደሚሰማው ሃኪሞች ገጠር ገብተው ማገልገል አይፈልጉም። ምንም የሰላም ችግር በሌለባቸው አካባቢዎች እንኳን ቢሆን ለተወሰነ ጊዜ ገጠር ገብተው ያስተማራቸውን ህዝብ የማግለገል ተነሳሽነት የላቸውም። እርግጥ አስፈጊ የመኖሪያ ሁኔታዎች መሟላት እንዳለባቸው ቢታመንም “ገጠር ግብቶ የመስራት ፍላጎት ማጣት በአገር ደረጃ መነጋገሪይ፣ በማህበራቸው ዘንዳም አጀንዳ ሊሆን ይገባል” የሚሉ አሉ።

Exit mobile version