Site icon ETHIO12.COM

ልጃቸውን በስለት ለቤተ ክርስቲያን የሰጡት ፊሊፒንሳዊው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ካህን

ዳንቴ አሎንዞ ካህን ናቸው። አገልግሎታቸው በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ነው። ክርስቲያኒቱ ለጥቂቶች ብቻ የተፈቀደውንም ምስጢር ያውቃሉ። ሁለተኛ ቄስ ሆነው ቅዳሴ ይመራሉ። ከቅዳሴ በኋላ ምዕመናንን ያቆርባሉ። ታቦት ይይዛሉ። ሌላም ሌላም አገልግሎት ይሰጣሉ። ተወልደው ያደጉት በሩቅ ምሥራቋ አገር ፊሊፒንስ ነው። ፓኒኪ ታርላ በተሰኘችው ከተማ ልጅነታቸውን አሳልፈዋል።

በዚያች ከተማ ጎዳናዎች ላይ ከጥቂት አስርት ዓመታት በፊት ዳቦ ይሸጡ ነበር። የዳቦ ንግዳቸውን ጠዋት ጨርሰው ከሰዓት ማርሻል አርት ይማራሉ። አብዛኛው የልጅነት ጊዜያቸው እንዲህ ነበር ያለፈው። ያኔ ኢትዮጵያ የምትባል አገር፣ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ የሚባል ሃይማኖት ስለመኖሩ አያውቁም።

ለነገሩ በፊሊፒንስ የኦርቶዶክስ ክርስትና ብዙም አይታወቅም። በአገራቸው ከፍተኛ ቁጥር ያለው ሕዝብ የሮማ ካቶሊክ እምነት ተከታይ ሲሆን፣ እስልምና ሁለተኛውን ደረጃ ይይዛል።

“ፊሊፒንስ እያለሁ ስለ ኦርቶዶክስ ክርስትና ፍጹም ሰምቼ አላውቅም” ይላሉ። ታዲያ ዳንቴ የኢትዮጵያ ኦርቶክስ ተዋህዶን ከማወቅ አልፈው አገልጋይ ለመሆን እንዴት በቁ?

እሳቸው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ተከታይ የሆንኩበት አጋጣሚ “እጅግ የሚገርመኝ እና ተዓምር ነው” ሲሉ ይገልጹታል። አንድ ቀን፣ “የእግዚአብሔርን መንግሥት ለማወቅ” መጽሐፍ ቅዱስ ገልጠው ማንበብ ጀመሩ።

መጽሐፍ ቅዱስ ሲያነቡ የመጀመሪያቸው ነበር።

“ይህ የእኔ ቤተክርስቲያን ነው አልኩ። ሥርዓተ አምልኮቱ ሲጀምሩ፣ ማልቀስ ጀመርኩ። ልክ ሕጻናት እንደሚያለቅሱት ነው ያለቀስኩት። በጣም ስሜታዊ ሆኜ ነበር። እግዚያብሔርን አላውቅም ነበር አልኩኝ።”

በመጀመሪያዎቹ ገጾች ልባቸውን የያዘ ቃል አገኙ። ኦሪት ዘፍጥረት ምዕራፍ 2 ቁጥር 13 ላይ ያለው ጥቅስ “ቀልቤን ገዛው” ይላሉ። ያ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍልም “የሁለተኛውም ወንዝ ስም ግዮን ነው፤ እርሱም የኢትዮጵያን ምድር ሁሉ ይከብባል” ይላል። ይህ አጋጣሚ ስለኢትዮጵያ ለማወቅ ጉጉትን ፈጠረባቸው። ይህ ሲሆን ወደ ካናዳ ተሰደዋል።

“በምኖርበት ቶርንቶ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያንን ማፈላለግ ጀመርኩ” ሲሉ ይገልጻሉ።

ከብዙ ፍለጋ በኋላ፣ በካናዳ ጃማይካውያን በአውሮፓውያኑ 1977 ያቋቋሙት መድኃኒዓለም የተሰኘ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክስርስቲያንን አገኙ።

ከቤተ ክርስቲያኑ ደጃፍ ቆመው አንኳኩ።

ምላሽ ግን አልነበረም። ስልክ ደወሉ። በቀጣዩ ሳምንት እንዲመጡ ተነገራቸው።

“ጥሩ አጋጣሚ” ሆኖ ያ ቀን በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን የክርስቶስ ትንሳኤ የሚከበርበት ምሽት ነበር።

“በዚያን ጊዜ ካቶሊክ ነበርኩ። አንድ ሳምንት ቀደም ብዬ በካቶሊካውያን የሚከበረውን ትንሳኤ አክብሪያለሁ” ሲሉ ያስታውሳሉ።

የሆነው ሆኖ በዚያች የፋሲካ ምሸት በካናዳ የሚገኘው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ደረሱ።

“ልክ ስደርስ ሥርዓተ አምልኮቱ ተጀምሮ ነበር። በሕይወቴ በጣም ስሜቴ የተነካው ያኔ ነው። ምንም የማውቀው ነገር ባይኖርም፣ ይህ ትክክለኛ ቦታ ነው አልኩ። በመጀመሪያ ቅጽበት የነበረኝ ስሜት በጣም ጠንካራ ነበር” ይላሉ።

ያዩት ሥርዓተ አምልኮ ለእሳቸው ፍጹም አዲስ ቢሆንም፣ ቋንቋው ባይገባቸውም ነገሩ በሕይወታቸው ትልቅ ለውጥ ይዞ እንደሚመጣ ግን ተገንዘበውታል።

“ይህ የእኔ ቤተክርስቲያን ነው አልኩ። ሥርዓተ አምልኮቱ ሲጀምሩ፣ ማልቀስ ጀመርኩ። ልክ ሕጻናት እንደሚያለቅሱት ነው ያለቀስኩት። በጣም ስሜታዊ ሆኜ ነበር። እግዚያብሔርን አላውቅም ነበር አልኩኝ።”

በዚያው ቀን አንድ ምዕመን ስለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ታሪክ የሚያትት መጽሐፍ እንደሰጣቸው ያስታውሳሉ።

ያ መጽሐፍ ብዙ ረድቷቸዋል። ከጊዜ በኋላም የኢትዮጵያ ኦርቶክስ ተዋህዶ እምነትን ተቀብለው ተጠመቁ። ገብረ መድኅን የሚል የክርስትና ስምም ተሰጣቸው።

“የቤተክርስቲያን አገልግሎትን የጀመርኩት ከጽዳት ነው”

ዳንቴ የኦርቶዶክስ ክርስትናን ተቀብለው ብቻ አላቆሙም። የቤተክርስቲያኒቱን የአምልኮ ሥርዓት መማር ጀመሩ።

በእንግሊዝኛ የተዘጋጁ መጻህፍትን ያነባሉ።

አባ ደስታ ከተባሉ አባት የኦርቶዶክስ አስተምህሮቶችን፣ ሥርዓተ አምልኮን፣ ታሪክን እና ሌሎች መጽሐፍትን ለሁለት ዓመታት ተማሩ።

አባ ደስታ ለእሳቸው ብቻ ሳይሆን በካናዳ ለሚገኙ የኦርቶዶክስ ተዋህዶ ተከታይ ጃማይካውያን ትህምርትን ይሰጡ ነበር።

እሳቸው በ1993 ዓ.ም. ከካናዳ ሲወጡ፣ ቀሲስ ዳንቴ እስካሁን ድረስ እያገለገሉ ወደሚገኙበት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የቶሮንቶ ቅድስት ማርያም ካቴድራል አመሩ።

ወደዚህ ቤተክርስቲያን “የማይመጣ የውጪ ዜጋ የለም።”

ስለኢትዮጵያ የሰሙ ወይም ያነበቡ የውጭ አገራት ዜጎች ይመጣሉ፤ ይጠይቃሉ። ማገልገል እንፈልጋለን ይላሉ። ይህ የተለመደ ነው።

ችግሩ የሚዘልቁት “እጅግ በጣም” ጥቂቶቹ ናቸው።

“ብዙዎች ይመጣሉ። ቋንቋው እና ባህሉ አዲስ ሲሆንባቸው ተመልሰው ይሄዳሉ” ይላሉ አቶ ዓለማየሁ።

አቶ ዓለማየሁ ዘነበ በቤተክርስትያኑ ለ32 ዓመታት አገልግለዋል።

በቶሮንቶ ዩኒቨርሲቲ በሥነ መለኮት የተመረቁ ሲሆን፣ አሁን ላይ የመንበረ ብርሃን ቅድስት ማርያም ካቴድራል ጽህፈት ቤት ኃላፊ ናቸው።

ዳንቴ አሎንዞንም በደንብ ያውቋቸዋል።

ከጥቂት ጊዜያት በኋላ ዳንቴ መጥተው እንደሚመለሱት ሌሎች የውጭ አገራት ዜጎች እንዳልሆኑ ተረዱ።

የሚመላለሱበት ድግግሞሽ፣ ትህትናቸው እና ትጋታቸው የተለየ ሆኖ አገኙት።

“እኛ ይህን ሁሉ ስናይ ‘ይሄ ሰውዬ ለካ የምሩን ነው’ አልን. . . ለቤተክርስቲያን ልዩ ፍቅር እና ታማኝነት አለው። ከሰው ጋር ተግባቢ ነው። ቤተሰቡንም ይዞ ይመጣ ነበር። ልጆቹም እዚህ ካሉት ልጆች ጋር ወዲያው ነበር የተግባቡት። እኛም በትልቅ ደስታ ነበር የተቀበልነው” ሲሉ ይናገራሉ።

የቤተክርስቲያኒቱ አግልግሎት በግዕዝ እና በአማርኛ መሆኑ የቀሲሱ ዳንቴን የአገልግሎት ጉዞ ፈታኝ አድርጎታል።

ቢሆንም አገልግሎታቸው ቀጥሏል።

“እውነትን እንዳገኘሁ ሲገባኝ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የምችለውን አገልግሎት ለመስጠት ወሰንኩኝ። በእኔ አቅም ሊሠራ የሚችል ሥራን መሥራት ጀመርኩ። ጽዳት እና ምግብ የሚያበስሉትን ማገዝ ጀመርኩ። ስፈልገው የነበረውን እውነት ስላገኘሁ ቤተ ክርስቲያንን የሕይወቴ አንድ አካል አደረኳት” ሲሉ ይገልጻሉ።

ከዓመታት የትምህርት እና የቤተክርስቲያን አገልግሎት በኋላ ድቁናን እንዲቀበሉ መወሰኑ ተነገራቸው። አላመኑም። “በወቅቱ የተፈጠረብኝን ስሜት ቃላት አይገልጸውም” ይላሉ።

በዚህ መካከል የተወለዱት ሁለት ልጆቻቸውን ወደ ቤተክርስቲያን ሁልጊዜ ይዘዋቸው ይመጡ ነበር።

“ልጆቹ መዘምራን ክፍል ውስጥም ገብተዋል። ዮሐንስ [ወንዱ ልጃቸው] የሦስት ዓመት ልጅ እያለ [አባቱ] ትንሽ ከበሮ ሰርቶለት ሁልጊዜ ከፊት ቆሞ ይዘምር ነበር” ሲሉ አቶ ዓለማየሁ ይናገራሉ።

የዳንቴ ክህነት እና አገልግሎት

ዳንቴ ግንቦት 3/ 2008 ዓ.ም. ድቁናን ከአቡነ መቃሪዮስ ተቀበሉ።

ይኼኔ ዕድሜያቸው 39 ዓመት ነበር።

ድቁናን ሲቀበሉ እጅግ ደስ ብሏቸዋል። ደስ ቢላቸውም “ይህ ለእኔ አይገባም፣ ብቁ አይደለሁም” ብለውም ነበር።

እዚህ ደረጃ ለመድረስ ከሊቀ ካህናት ምሳሌ እንግዳ እና ከሌሎች መምህራን ለዓመታት ለድቁና የሚያበቃቸውን ትምህርት በእንግሊዝኛ ተምረዋል።

ለአገልግሎት ብቁ እንደሆኑ ሊቀ ካህናት እንግዳ ምስሌ ትልቅ አስተዋጽኦ እንደላቸው ይናገራሉ።

ለዚህ ሥርዓት አዲስ ስለሆንኩ ብዙ ነገር አላወቅም ነበር የሚሉት ዳንቴ “በእያንዳንዱ ነገር ‘ቀጥሎ ምን ላድርግ?’ እያልኩ እጠይቅ ነበር” ሲሉ ይገልጻሉ።

አቶ ዓለማየሁ ደግሞ “በጣም ትሁት ሰው ስለሆነ የሚያወቀውን ለመናገር አይደፍርም። ለዚያ ብቁ መሆኑ ከታመነ በኋላ ነው ወደ ድቁና እንዲሄድ የተደረገው. . . ለቤተክርስቲያን ትጉህ እና ታማኝ ነው” ሲሉ ይመሰክሩላቸዋል።

በግዕዝ እና በአማርኛ የተጻፉ ግን በላቲን ፊደል የተቀረጹ መጻህፍትን አጥንተዋል።

ቋንቋውን ለመናገር ይቸገሩ እንጂ አንዳንድ መጽሐፍትን በቃላቸው ይዘዋል።

በዚህ ሁኔታ፣ በተለይ በእንግሊዝኛ የቤተ ክርስቲያንን አግልግሎት መስጠት ጀመሩ።

በዚህ ጊዜ የዳንቴ አራተኛ ልጅ በዚያው ቤተክርስቲያን የድቁና ትምህርትን ከሌሎች ሕጻናት ጋር እየተከታተለ ነበር።

ይህ ከሆነ ልክ ከ10 ዓመታት በኋላ የዳንቴ የዲያቆንነት አገልግሎት አበቃ።

ቅስናን ለመቀበል እና ቀሲስ ለመባል ተመረጡ።

የጠበቁት ግን አልነበረም።

“የቤተክርስቲያኑ አስተዳዳሪ መጥተው ቄስ ልትሆን ነው ሲሉኝ። ደነገጥኩ ‘ዝግጁ አይደለሁም እኮ’ ስላቸው ‘ልጅህ ዲያቆን ሊሆን ነው። አንተም እሱም ዲያቆን መሆን አትችሉም፣ ይህ የቤተክርስቲያንን ሕግ ይጻረራል አሉኝ’፤ ‘እንኳን ለቅስና ለድቁናው እኮ በደንብ አልበቃሁም አልኳቸው’ ” ይላሉ።

የሆነው ሆኖ፣ ሚያዚያ 28/ 2010 ዓ.ም. ቅስናን ተቀበሉ። ቀሲስ ዳንቴ (ቀሲስ ገብረ መድኅን) ተባሉ።

“እውነት ለመናገር ይህ ለእኔ ትልቅ ነገር ነው። …በዚህ ባህል ውስጥ አላደግኩም። ዕድገቴ በምዕራባውያኑ ባህል ውስጥ ነው” የሚሉት ቀሲሱ ‘ለዚህ አልገባም’ ቢሉም የተሰጣቸውን ኃላፊነት ተቀበሉ።

ቀሲስ ዳንቴ በቅዳሴ ወቅት ረዳት ወይም ሁለተኛ ቄስ በመሆን ሥርዓቱን ይመራሉ። ከቅዳሴ በኋላ ምዕመናንን ያቆርባሉ።

በክብረ በዓላት ወቅት ደግሞ ታቦት ይይዛሉ።

ለመጀመሪያ ጊዜ ታቦት እንዲይዙ ሲነገራቸው “ይህንን ለማድረግ ብቁ አይደለሁም” ብለው ተከራክረዋል።

“ግድ መሆኑን ስረዳ፣ ፈጣሪ ይቅር በለኝ። እኔ ይህንን ለማድረግ አልበቃሁም አልኩኝ” ይላሉ።

በተጨማሪም በቅዳሴ ወቅት የወንጌል ንባቦችን በእንግሊዝኛ ያነባሉ።

በግዕዝ እና በአማርኛ ቋንቋ ክርስትና ለማንሳት እና ለማጥመቅ እየተማሩም ነው።

“ለአንዳንድ የእንግሊዝኛ ተናጋሪ ምዕመናን መንፈሳዊ አባታቸው” እንደሆኑ አቶ ዓለማየሁ ጠቅሰዋል።

ከዚህም ውጪ በእጅ ሙያቸው ቤተ ክርስቲያንን ያግዛሉ።

“ካህናት፣ ዲያቆናት እና ምዕመናን በፍቅር ነው የሚያዩዋቸው እንጂ መጠራጠር እና አይችሉም ብሎ ማሰብ የለም” በማለትም አቶ ዓለማየሁ ይናገራሉ።

ዲያቆን ዮሐንስ አሎንዞ፡ በስለት የተሰጠው ልጅ

የምስሉ መግለጫ,ዲያቆን ዮሐንስ አሎንዞ (ከመሐል)

ዳንቴ በ1971 ዓ.ም. ልክ 16 ዓመት ሲሞላቸው የተወለዱበትን፣ ያደጉበትን ዳቦ የሸጡበትን የፊሊፒንስ መንደሮች ጥለው ወደ ካናዳ ተሰደዱ።

ከዚያ ጊዜ ጀምሮ ኑሯቸው ካናዳ ሆነ።

ቤተሰባቸው ትልቅ ነው – 13 ወንድም እና እህት አላቸው።

ወደ ካናዳ የተሰደዱት ግን እሳቸውን ጨምሮ ሰባት የቤተሰቦቻቸው አባላት ናቸው።

ከ28 ዓመታት በፊት በ1988 ዓ.ም. ትዳር መሠረቱ።

ጋብቻቸው በካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ሥርዓት ካናዳ ውስጥ ነበር የተፈጸመው።

ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ጋር ከመተዋወቃቸው በፊት የተወለዱት ሦስት ልጆቻቸውም በካቶሊክ ቤተክርስቲያን ውስጥ ተጠምቀዋል።

ከዚያ በኋላ የተወለዱት 2 ልጆች ግን በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ሥርዓት የክርስትና ጥምቀት ተደርጎላቸዋል።

ዮሐንስ እና ማክዳ የሚል ስምም ተሰጥቷቸዋል።

ቀሲስ ዳንቴ ወደዚህ ሕይወት ከመጡ በኋላ ወንድ ልጃቸው ዮሐንስ ከቤተክርስቲያን ጋር የተለየ ቁርኝት እንዲኖረው ወሰኑ።

ከ 20 ዓመታት በፊት የሆነውን ልክ ዛሬ እንደሆነ ያስታውሱታል።

“ኦርቶዶክስን በተቀልኩበት የመጀመሪያዎቹ ጊዜያት ዮሐንስ የጸሎቴ ሁሉ አካል ነበር። ‘ፈጣሪ ወንድ ልጅ ስጠኝ። ስሙን ዮሐንስ ብዬ አንተን እንዲያገለግል እሰጠዋለሁ’ ስል ለመንኩ። ይህ ከሆነልኝ ወደ ኢትዮጵያ እሄዳለሁ [ብዬ ተሳልኩ] አልኩ። ይገርማል፣ ፈጣሪ አደረገው። ዮሐንስ በ1996 ዓ.ም. ተወለደ። እኔ ደግሞ 2001 ላይ ወደ ኢትዮጵያ ሄድኩ” ይላሉ።

የምስሉ መግለጫ,ዮሐንስ ክራርን ጨምሮ ሌሎች የዜማ መሳሪያዎችን ይጫወታል

በኢትዮጵያ የአንድ ወር ቆይታቸው በርካታ አካባቢዎችን ረግጠዋል። በርካታ ገዳማትን እና አብያተ ክርስቲያናትን ተሳልመዋል።

ወደ ጣና፣ አክሱም፣ ጎንደር ላሊበላ፣ ደብረዳሞ እና ሌሎች ቦታዎች ተጉዘው በገዳማቱ ‘ለጸሎታቸው ምላሽ የሰጣቸውን’ ፈጣሪ አመሰግነዋል።

የኦርቶዶክስ ተዋህዶ መነሻቸው ጃማይካውያን የመሠረቱት ቤተ ክርስቲያን መሆኑን አስበው ወደ ሻሽመኔ አቅንተው ጃማይካዎችን ጎብኝተዋል።

ወደ ዮሐንስ እንመለስ።

ቀሲስ ቃላቸውን ጠበቀው ልጃቸው ቤተ ክርስቲያንን እንዲያገለግል ሰጥተውታል። “ልጄ ይህንን ያደርግልኛል ብለው ሳይሆን ቤተ ክርስቲያንን ያገለግላል ብለው ነው የተሳሉት። እግዚያብሔር የለመኑትን ነው ያደረገላቸው. . .የገቡትን ስለት ሰጥተዋል። የሚጠየቁት ነገር የለም” ይላሉ አቶ ዓለማየሁ። ልጃቸው “በቤተክርስቲያኑ ካሉት ዲያቆናት የሚመረጠው ነው” ሲሉም ጨምረዋል። ዮሐንስ ቤተ ክርስቲያንን ከልጅነቱ ጀምሮ ያውቃል።

‘ሀ ሁ’ ብሎ ፊደል ቆጥሮ የጀመረው ትምህርት እስከ ዜማ ደርሷል። ዲያቆን ሆኖ መቀደስ የጀመረው ግን በ13 ዓመቱ ነበር።

በቤተ ክርስቲያኑ በወር አንድ ጊዜ በሚሰጠው የእንግሊዝኛ ቅዳሴ ላይ መሪ ዲያቆን ሆኖ ማገልገል የጀመረው ያኔ ነው።

ዮሐንስ ትርጉሙን ባይረዳውም በአማርኛ መጻፍ እና ማንበብ ይችላል።

ሆኖም ለድቁና የበቁትን መጽሐፍት ትርጉም በእንግሊዝኛ ይነገረዋል።

ዮሐንስ ዲያቆን ብቻ አይደለም ዘማሪም ነው።

ዘማሪ ብቻ አይደለም፣ ክራር ይገርፋል፣ ማሲንቆም ይጫወታል፣ ከበሮ ይመታል።

ከዚያም አልፎ፣ እንጨት ቆርጦ፣ ክሮችን ወጥሮ ክራር እና ማሲንቆን ይሠራል።

የእሱ ታናናሾችንም ያስተምራል። በዩቲዩብ እና ቲክ ቶክ ላይ የሙዝር እና የዜማ መሳሪያ አጨዋወትን የሚያሳይ ቪዲዮም ይጭናል።

የዮሐንስ ሥራ ብዙ ነው።

ከድምጽ ማጉያው ፊት ቆሞ ምዕመናኑን የሚመስጥ ዜማ ያሰማል።

ያ ድምጽ ማጉያ እክል ቢገጥመው ዮሐንስ ይጠግነዋል።

በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ‘የቴክኒክ ችግር’ ካጋጠመ ዮሐንስ አለ።

ለዚያ ነው አቶ ዓለማየሁ የዲያቆን የሐንስ ተግባር “ከሚጠበቀው በላይ ነው” የሚሉት።

“በጣም ትሁት ነው። ሲታዘዝ ‘እሺ፣ ወዴት እንጂ ማን ያዘኛል?’ የሚል ነገር የለውም” የሚሉት አቶ ዓለማየሁ “ዮሐንስ [በግዕዝ እና በአማርኛ] ዳዊት፣ ወንጌልና መልዕክቶችን ሲያነብ ብዙ ኢትዮጵያውያን በጣም ይጸጸታሉ። ‘ልጆቻችንን እኛ ሳናስተምር። እሱ ከሌላ ቋንቋ መጥቶ እንዲህ አይነት አገልግሎት ሲሰጥ በራሳችን እናፍራለን’ ይሉናል” ይላሉ።

በአውሮፕላን ቴክኒሺያንነት የተመረቀ ሲሆን ካልጋሪ በሚገኝ አንድ የአውሮፕላን ኩባንያ እየሠራ ይገኛል። በትምህርቱም የተመሰገነ ነው።

የምስሉ መግለጫ,“ዮሐንስ የሦስት ዓመት ልጅ እያለ [አባቱ] ትንሽ ከበሮ ሰርቶለት ሁልጊዜ ከፊት ቆሞ ይዘምር ነበር”

ዮሐንስ ስለ ቤተክርስቲያኑ ሲናገር “የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያንን ካልኖርክበት አትረዳውም. . . እኔ እዚያ ነው ያደግኩት። ሁልጊዜ በየሳምንቱ እሄዳለሁ። የሳምንቱን ጉልበት የማገኘው ከቤተ ክርስቲያን ነው” ይላል።

አሁን በሥራ ምክንያት ካደገበት ቤተ ክርስቲያን ቢርቅም አገልግሎቱ ግን እንደሚቀጥል ይጠቅሳል።

“በምችለው መጠን ቤተ ክርስቲያንን አገለግላለሁ። እርግጠኛ ነኝ ፈጣሪ ለእኔ ያለው ነገር አለ። ማን ያውቃል? ካህን ወይም መነኩሴ እንድሆን ይፈልግ ይሆናል። ዲያቆን የሆንኩት ራሱ በእኔ ዕቅድ አይደለም። በእሱ ዕቅድ እና ባዘጋጀልኝ ነገር እምነት አለኝ” ብሏል።

የንግሥተ ሳባን ታሪክ እጅግ እንደሚወዱት የሚናገሩት ቀሲሱ፣ በንግሥቲቱ ሌላኛው ስም የመጨረሻዋን ልጃቸውን ‘ማክዳ’ ብለዋታል።

በጥርስ ሕክምና የተመረቀችው ማክዳ በዘማሪነት ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ታገለግላለች።

በግዕዝ እና አማርኛ ቋንቋዎችም ትዘምራለች።

የምስሉ መግለጫ,ዲያቆን ዮሐንስ አሎንዞ

“ቤተሰቦቼ አእምሮዬ የታመመ መስሏቸው ነበር”

ቀሲስ ዳንቴ ወደ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ሲመጡ ቤተሰቦቻቸውን ለማሳመን “እጅግ አስቸጋሪ” ጊዜያትን አሳልፈዋል።

“እኔ እውነቱ ሲገለጥልኝ እነሱ በተሳሳተ መንገድ ነበር የተረዱኝ። ያበድኩ መስሏቸው ነበር። ጤነኛ እንደሆንኩ ለማረጋገጥ ከመካከላቸው አስቀምጠው ያዋሩኝ ነበር። እንዴት እንደምመልስ፣ እንዴት እንደማወራ ይከታተሉኝ ነበር። በሁለተኛው ጊዜ ደግሞ እኔን ለመርዳት የአእምሮ ጤና ባለሙያ ጋር ደወሉ” ይላሉ።

ቀጥለው “ቤተሰቦቼ ጃማይካውያኑ ጓደኞቼ የምበላው ምግብ ውስጥ የሆነ ነገር ያደረጉብኝ ነበር የመሰላቸው” ብለዋል።

ነገሩ ካለፈ በኋላ እናታቸው ለቤተሰቦቻቸው የነገሩትን ለዳንቴ ነግረዋቸዋል።

“እናቴ ለቤተሰቡ ‘ወንድማችሁ አላበደም። በራሱ ለሕይወቱ እጅግ አስፈላጊ የሆነውና የሚያስደሰተውን ነገር አግኝቷል። ከዚህ ነገር ልታላቅቁት አትቸሉም’ ብላቸዋለች” ሲሉ ይገልጻሉ።

ቢሆንም እህት እና ወንድሞች አልተስማሙም። በተለይ ከታላቅ ወንድማቸው ከባድ ተቃውሞ ገጥሟቸዋል። ብዙ ውይይት እና ክርክር ማድረጋቸውን ያስታውሳሉ። የተቀየረ ነገር አልነበረም።

‘ሃይማኖት የግል ነው’ በሚል ቤተሳባዊነቱ ቀጠለ።

“እኔ የእነሱን ምርጫ አክበራለሁ፤ እነሱም የእኔን ያከብራሉ” ሲሉ ጠቅሰዋል።

የፊሊፒንስ እና የካናዳ ጥምር ዜግነት ያላቸው ቀሲስ ዳንቴ የተከበሩ የእጅ ባለሙያ ናቸው። በኢንዱስትሪ ውስጥ ብረቶችን ቅርጽ እያወጡ ለልዩ ልዩ አገልግሎት ያውላሉ።

“አባቴ በቤተ ክርስቲያን ካለው አገልግሎት ባሻገር እጅግ ጎበዝ የእጅ ባለሙያ ነው። ሥራውን ጠንቅቆ ያውቃል። ጥሩ የፈጠራ ችሎታ አለው” ይላል ዲያቆን ዮሐንስ።

በትውልድ አገራቸው ፊሊፒንስ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የማስገንባት ዕቅድም አላቸው።

ዕቅድ ብቻ ሳይሆን ሥራ ጀምረዋል። 10 ሺህ ካሬ ሜትር መሬት ላይ ቤተክርስቲያን ለማስገንባት የሚሆን መሬት በግላቸው ገዝተዋል።

“በአገሬ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶን ማስተዋወቅ እፈልጋለሁ። ሰዎች በዚያ እንዲያመልኩ፣ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት እንዲመጡ እፈልጋለሁ” ይላሉ።

ልጃቸው ዮሐንስ “አባቴ ለሐይማኖታችን እጅግ ታማኝ እና ትጉህ ነው” ሲል አቶ ዓለማየሁ የዳንቴ ቤተሰብ “የክርስቶስን መንገድ የተከተሉ ናቸው” ሲሉ መስክረውላቸዋል።

ወደ ኢትዮጵያ ዳግም የመመለስ ሀሳብ እንዳላቸው እና አማርኛ መማር እንደሚፈልጉ የሚገልጹት ቀሲስ ዳንቴ ደግሞ “በኢትዮጵያም ይሁን በቤተ ክርስቲያናችን ብዙ ፈተና እንዳለ አውቃለሁ። ምንም ቢሆን ኢትዮጵያ የእኔ ዕጣ ፈንታ ነች። ለኢትዮጵያ ያለኝ ፍቅር መቼም አይቀየርም” ብለዋል።

ዘገባው የቢቢሲ አማርኛ ነው

Exit mobile version