Site icon ETHIO12.COM

” የተጠላና የተናቀ ፓርቲ” ትህነግ በከፍተኛ ደረጃ በክልሉ መሁራን እየተወገዘ ነው

በመቀለ ዩኒቨርሲቲ የፖለቲካል ሳይንስ እና ስትራቴጂክ ጥናት ክፍል መምህር እና ተመራማሪ የሆኑት ገብረመድኅን ገብረሚካኤል፣ የህወሓት የአመራር ቀውስ ለብዙ ዓመታት የቀጠለ መሆኑን በመጥቀስ፣ የፓርቲው እውነተኛ እምነት ይህ ነው ወይ የሚል ጥያቄ ያነሳሉ።

“ህወሓት አሁን ብቻ ሳይሆን የቆየ የአመራር ቀውስ ገጥሞታል። በዚህ መልኩ ራሱን ከገመገመ ብዙ ዓመታት ተቆጥረዋል። ታድያ እንደዚህ ከሆነ የችግሩ ምንጭ የሆነው አመራር በተለይም ስትራቴጂካዊ እየተባለ በሚጠራው አመራር ላይ ለውጥ ይመጣል ተብሎ ነው የሚጠበቀው።

“ሆኖም ግን ይህ እየታየ አይደለም። ምክንያቱም አንደኛ ‘ችግሩ አለብኝ’ ብሎ እያመነ ያለው ከውጭ ጫና ስላለበት እና ተደጋጋሚ ትችት ስለሚደርስበት እሱን ለማረጋጋት እንጂ ‘በእርግጥ እምነቱ ነው ወይ? በዚህ መሰረት ራሱን ለመፈተሽ እና ለመታገል ቁርጠኛ ነው ወይ?’ የሚል ጥያቄ የሚያስነሳ ነው። ብልሹ መሪዎችን እና ድክመቶቹን ለመለወጥ ቅን የሆነ እውነተኛ የውስጥ ትግል ስለሌለው ይመስለኛል” በማለት ያስረዳሉ።

ከመሪዎቹ መካከል በአቅም ጎላ ብሎ መታየት የሚችል ተደማጭነት ያለው ሰው አለመኖሩንም እንደ ሁለተኛ ምክንያት አቶ ገብረ መድኅን ይጠቅሳሉ።

“ሁሉም በተመሳሳይ የብልሽት ደረጃ ላይ ናቸው። ውድቀቱ የአንድ ወይም የሁለት አይደለም። ድርጅታዊ፣ ስትራቴጂያዊ እና የአመራር ነው። የተሻለ ሆኖ የሚታይ ግለሰብ ወይም መሪ የለም። ማን ከማን ይበልጣል? ማን ነው ሊወጣ የሚችለው? ማን ይለወጣል? የሚል ጥያቄ አለ። እኔም እንደዛ ነው የማምነው” ብለዋል።

ቀደም ሲል በፖለቲካው ተሳትፎ የነበራቸው በአሁኑ ወቅት ግን የትግራይን ፖለቲካን በመከታተል የሚተነትኑ በአዲግራት የዩኒቨርሲቲ መምህር የሆኑት አብርሃ ተክሉም ከዚህ ጋር የሚስማማ ሐሳብ አላቸው።

“ህወሓቶች ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ እስካለፉበት ድረስ በአንፃራዊ ሁኔታ ያጋጠሙ ነገሮችን በተገቢው ማዕቀፍ ውስጥ አስገብተው የማየት ብቃቱ ነበራቸው። ‘ምንድን ነው ያጋጠመን? ለምን ተከሰተ?’ ይላሉ። ዓለም አቀፋዊ እና ቀጠናዊ ሁኔታን እንዲሁም ራሳቸውን ይመለከቱ ነበር።

“አሁን ያለው አመራር ግን ከዚህ ሂደት የተለየ ነው። የሐሳብ ለውጥ እንዳያመጣ በሐሳብ ደረጃ አይደሉም እየተሟገቱ ያሉት። የአመራር ለውጥ ያላመጡበት ምክንያት ደግሞ እርስ በርስ እየተጨቃጨቁ እና እየተባሉ ስላሉ ነው፤ ይህ ደግሞ ወደ ከፍተኛ አለመተማመን እና ጥርጣሬ ወስዷቸዋል” ብለዋል።

መምህር አብርሃ ተክሉ የውጭ ጣልቃ ገብነትም ሌላ ችግር ሊሆን እንደሚችል “ፓርቲው በተነጻጻሪ ዝግ በሆነ ሂደት ችግሮቹን የመፍታት ልምድ ነው ያለው። ዛሬ ላይ ግን ምስጢሮችን መደበቅ አይችልም። መረጃዎች በየጊዜው ነው የሚለቀቁት። በዚህ መጠንም ከውጪ ሆኖ ሁኔታውን ሊያባብሰው የሚሻ አካል በሚፈልገው ሰው በኩል የማተራመስ እንዲሁም መረጋጋት እንዳይኖር የማድረግ ዕድሉ ሰፊ ነው” በማለት ያስረዳሉ።

ህወሓት ችግሮቹን በስብሰባ እና በግምገማ የመፍታት ልምዱን የሚያደንቁ በርካታ ሰዎች ቢኖሩም፣ በፓርቲው ውስጥ የተለመደ የቡድንተኝነት አካሄድ ግን ፓርቲው እውነተኛ ለውጥ እንዳያመጣ እንቅፋት ሆኗል ይላሉ። በአሁኑ ጊዜም ፓርቲው በተመሳሳይ ሁኔታ በቡድንተኝነት ተከፋፍሎ ከሐሳብ ትግል ወጥቶ በመወነጃጀል እና በመካሰስ ላይ እንደሚገኝ የሚያመለክቱ መረጃዎች ከፓርቲው ከፍተኛ አመራሮች ሳይቀር እየተደመጡ ነው።

የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር ፕሬዝዳንት አቶ ጌታቸው ረዳ በአንድ ሕዝባዊ መድረክ ላይ ሲናገሩ፣ ፓርቲው ለሁለት ወራት ባካሄደው ስብሰባ በሕዝብ ቁልፍ ጉዳዮች ላይ አለመወያየቱን እና በግምገማው ወቅት ወደ አካባቢያዊነት እንዲሁም ሌሎች ጉዳዮችን ለማስተሳሰር የሞከሩ መሪዎች እንዳሉ በግልጽ አመልክተዋል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ፣ የህወሓት የቀድሞ አመራር አባል የሆኑት አቶ ስብሃት ነጋ በቅርቡ ትግራይ ሚድያ ሀውስ ለተባለው ቴሌቭዥን በሰጡት ቃለ-መጠይቅ በስም ያልጠቀሷቸው የተወሰኑ የክልሉ ሠራዊት አመራር እና የፓርቲው ሥራ አስፈፃሚ አባላትን “የሲአይኤ ወኪሎች” በማለት ፓርቲውን ለማፍረስ እያሴሩ ነው ሲሉ ከስሰዋል።

በአመራሩ መካከል ያለው ልዩነት የሐሳብ ወይስ የጥቅም ?

የመቀለ ዩኒቨርሲቲው መምህር ገብረመድኅን እንደሚሉት በፓርቲው አመራሮች መካከል ያለው መቧደን በጥቅም ላይ የተመሠረተ ነው።

“እኔ ከጥቅም አልፈው በሃሳብ እና በሕዝብ ጉዳዮች ላይ የተመሠረቱ አይመስለኝም። አንደኛው በሥልጣን ላይ ለመቆየት ሲሆን፣ ሌላኛው ደግሞ ወደ ሥልጣን ለመምጣት ነው የሚጥሩት” በማለት ያስቀምጣሉ።

መምህር አብርሃም ተክሉም ተመሳሳይ መረጃ እና ግንዛቤ ነው ያላቸው።

“ጥቅም ነው። መቧደኑ ለውጥን በሚፈልጉ እና ለውጡን በማይቀበሉት የሚገለጽ አይደለም። ‘አሮጌው አዲስ አመራሮች ወደፊት እንዳይመጡ እየተከለከለ ነው’ የሚለው አባባልም ከእውነታው የራቀ ነው” ይላሉ።

ህወሓት ረቡዕ ጥር 22/2016 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ ለ41 ቀናት ያካሄደውን ስብሰባ እና ግምገማ እንዳጠናቀቀ፤ “የስትራቴጂክ አመራር ድክመት ቁልፍ ችግሩ መሆኑን ለይቶ ማወቅ እንደቻለ” በመግለጽ በቀጣይ የአመራር ለውጥ እንደሚያደርግ አመልክቷል።

የፓርቲው የመንፈስ አባት ናቸው የሚባሉት አቶ ስብሃት ነጋ ከቴሌቪዥን ጣቢያው ጋር በነበራቸው ቆይታ “ከሰሃራ በታች ባሉ የአፍሪካ አገሮች ከህወሓት ጋር ሊወዳደር የሚችል ፓርቲ የለም” ሲሉ አስረግጠው ሲናገሩ ተደምጠዋል።

ቢቢሲ ያነጋገራቸው ሁለቱ የትግራይ ምሁራን እንደሚገመግሙት ግን ፓርቲው መሠረታዊ ለውጥ ካላመጣ ህልውናውን በቅርቡ የሚያከትም ይሆናል።

በመቀለ ዩኒቨርሲቲ የፖለቲካል ሳይንስ ምሑሩ አቶ ገብረመድኅን ገብረሚካኤል “ህወሓት ተጠናክሮ ይወጣል ብዬ አልጠብቅም። ለተወሰነ ጊዜ መቆየቱ አይቀርም። ምክንያቱም ሌላ የተዘጋጀ ኃይል እና አማራጭ የለም። እንደ ፓርቲ ግን በተለይም ሥልጣን ላይ ሆኖ ራሱን አስተካክሎ ወደ ተሻለ ደረጃ ይሸጋገራል ብዬ አላምንም” ሲሉ ደምድመዋል።

የአዲግራት ዩኒቨርሲቲ መምህሩ አብርሃም ተክሉ በበኩላቸው “የተጠላ እና የተናቀ ፓርቲ” ያሉት ህወሓት መሠረታዊ ለውጥ ካመጣ መዳን ይችላል የሚል ግምት አላቸው።

“ለሕዝብ ሲሉ የግል ፍላጎታቸውን ትተው ራሳቸውን ለመስዋዕትነት ዝግጁ እስከማድረግ ከመጡ መትረፍ ይችላሉ” በማለት ሐሳባቸውን ቋጭተዋል።

ሙሉውን ዘገባ ቢቢሲ ላይ ያንብቡ

Exit mobile version