Site icon ETHIO12.COM

የጦር ሜዳ የጉዞ ማስታወሻ ከበር ተክላይ – አዲጉዶም

የጀነራሎቹ ጀግንነትና ጓዳዊነት-ከበር ተክላይ – አዲጉዶም !ጁንታው በሰሜን ዕዝ ላይ ጥቅምት 24 ምሽት 2013 ዓ.ም የፈፀመውን ጥቃት ተከትሎ ፣ በራያ ግንባር ፣ የጋዜጠኞችን ቡድን ለማስተባበርና ለመከላከያ ሚዲያ ለመዘገብ ከስራ ባልደረቦቼ ጋር በከፍተኛ ወኔና ቁርጠኝነት ተሰልፈናል።ኢትዮዽያን የማፍረስ እና የማዳን ትንቅንቁ ቀናት አስቆጥሯል ። በግንባሩ የደቡብ ምስራቅ አቅጣጫ በቢሶበርና ጨርጨር በተባሉ ቦታዎች ላይ አፍራሹ ሀይል መሽጏል ።

የሞት ሽረት ትግል ከምስራቅ ዕዝ ጋር እያደረገ ስለነበር ፣ በአላማጣ አቅጣጫ ሳይጀመር ለተወሰኑ ቀናት እንድንቆይ አድርጎናል።ይሁን እንጅ በነዚህ ቦታዎች ላይ ሲከላከል የነበረው የጁንታው ኃይል በጀግኖች የምስራቅ ዕዝ አባላት እና በአየር ኃይላችን ከፊሉ ሲደመሰስ ከፊሉ ደግሞ እግሬ አውጭኝ በማለት ፈረጠጠ።ከዚህ በኋላም የደቡብ ዕዝ እና የምስራቅ እዝ በጋራ በአንድ አቅጣጫ መፋለም ቀጠሉ ።እኔም በዚህ ወቅት ነበር የሁለቱን ጀነራሎች ጓዳዊነት፣ጀግንነት፣ቁርጠኝነት፣የውጊያ ጥበብና በሳል የአመራር ሰጭነት ጥበብን በቅርብ ለማየት እድሉን ያገኘሁት ።ጀነራሎቹ የምስራቅ እዝ ዋና አዛዥ ( አይበገሬው ) ሜ/ጀነራል ዘውዱ በላይ እና የደቡብ ዕዝ ዋና አዛዥ ( ነጎድጓዱ ) ሜ/ጄነራል ሰለሞን ኢተፋ ናቸው።

ከሜ/ጀነራል ሰለሞን ኢተፋ ጋር ከቆቦ እስከ በር ተክላይ ድረስ በነበረው የግዳጅ አፈፃፀም ሂደት በተደጋጋሚ የማገኛቸው የነበረ ሲሆን ፤ ከሜ/ጄ ዘውዱ በላይ ጋር ግን የተገናኘነው በርተክላይ የተባለው ቦታ ላይ የጁንታው ምሽግ ከ3ቀናት በኋላ ሲሰበር ነው።በተለይም ሁለቱም ጀነራሎች በርተክላይን አለፍ ብሎ ካለው ተራራ ላይ በማጥቃት ዕቅዶቻቸው ላይ በጋራ ከመከሩ በኋላ ፣ ፊት ለፊት መሆኒን አልፎ ፀሀፍት በተባለ ቦታ ላይ የሚገኘው 3ኛው የጠላት ምሽግ በፍጥነት እንዲሰበር ትዕዛዝ ሰጡ ።ውጊያውን በቀጥታ በቅርብ ርቀት በመሆን በሚመሩበት ወቅት የነበራቸው መተሳሰብ ፣ መከባርና መደማጥ በቃላት ሊገልፁት የሚከብድ ከአንድ ማህፀን የወጡ ወንድማማቾች እስኪመስሉ የሚደንቅ ነበር።አብረው የነበሩ ከፍተኛ አመራሮችም ትዕዛዞችን በመቀበልና በማስፈፀም የነበራቸው ቅንነትና ቁርጠኝነት እጅጉን ይገርማል።በነጋታው ፀሀፍት ላይ የነበረው የጁንታው ምሽግ በተያዘው ዕቅድ መሠረት በ21ኛ ክ/ጦር በሚገርም ጀግንነትና ብቃት ተሰበረ።

ከዚህ በኋላ ሁለቱም ጀነራሎች የግንባሩ አስቸጋሪ በሆነው ገርበገው የተባለው ቦታ ላይ የመሸገውን ሀገር አፍራሽ ለመደምሰስ በሚያስችሏቸው የውጊያ ዕቅዶች ላይ ከመከሩ በኋላ ሁለቱም ወደፊት ለመሄድ ተነሱ።ሁለቱም ጀነራሎች በጦር ሜዳ መነፅሮች አካባቢውን በደንብ ከቃኙና ካርታውን አንብበው ከጨረሱ በኋላ የግድ አንዳቸው መቅደም ነበረባቸው። በዚህን ጊዜ ሜ/ጀ ዘውዱ ቆፍጠን ባለ አነጋገር ” ሰለሞን በቃ እኔ ፊት እሄዳለሁ አንተ እዚህ ቆይ ” ብለው ከተራራው ጫፍ ላይ መውረድ ጀመሩ።ነገር ግን ሜ/ጀ ሰለሞን እሺ ብለው አልተቀበሉም ። ”አይደለም ዘውዱ ፣ እኔ ነኝ የምሄድ አንተ እዚህ ቆይ ” አሉና እሳቸውም መንገድ ጀመሩ ። በዚህ ጉዳይ ላይ ‘ እኔነኝ የምቀድም ‘ ፣ ‘ እኔነኝ’ እያሉ ጓዳዊነትና ፍቅር በተሞላበትና ‘ ከአንተ በፊት እኔ ነኝ ቀድሜ መሞት ያለብኝ ‘ በሚል ስሜት ጭቅጭቅ አዘል ንግግር አደረጉና ተግባቡ ። ሁለቱም ከተራራው በፍጥነት መውረድ ጀመሩ። እኛም በቻልነው አቅም ሂደቱን በፎቶና በምስል ለማስቀረት አብረን ቀጠልን።

በዚህ ወቅት የታዘብኩት ፣ ሁለቱም ጀነራሎች ውጊያው ከተጀመረ ጀምሮ እንደማንኛውም ተዋጊ ኃይል ብርዱና ፀሀዩ እንደተፈራረቀባቸው ከጠቆረ ፊታቸውና ከደረቁ ከንፈሮቻቸው በአይኔ በብረቱ በማየት ተገንዝቤአለሁ።ነገር ግን ምንም አይነት ፈተና ቢገጥማቸውም ያላቸው ጀግንነት ፣እልህ፣የአሸናፊነት መንፈስና ወኔ ከፊታቸው ላይ ይነበባል። ሀሳባቸው ኢትዮዽያ ናት ። እሷ ህልውናዋ ከተረጋገጠ ፣ በቃ እፎይ ይላሉ ። እስከዛው ግን ስለራሳቸው የሚጨነቁበት ደቂቃ የላቸውም ።ሰአታት እየተቆጠሩ ነው ።

ጁንታው ከማይጨው እና ከመቀሌ አቅጣጫ የከባድ መሳሪያ ድብደባ መሆኔና አካባቢው ላይ በማድረግ ወደፊት የገሰገሰው የወገን ሀይል የሎጀስቲክስና የሰው ኃይል ድጋፍ እንዳያገኝ ለማድረግ ያለ የሌለ ኃይሉን መጠቀም ጀመረ ።ይሁን እንጂ በየ10 ደቂቃው ከመሆኒ መግቢያ እስከ ፀሀፍት ባለው አስፓልት ላይ የሚወረወሩት የመድፍ ቁምቡላዎች ፣ ሰራዊታችንንም ሆነ ጀነራሎቻችንን የማስቆም አቅም አልነበራቸውም ።

ስለሆነም ከጥቂት ደቂቃዎች በሗላ ሁለቱም ጀነራለች በፍጥነት ከተራራው ላይ በመውረድ እንደ በረዶ የሚዘንበውን የጥፋት እሳት ከምንም ሳይቆጥሩ መኪኖቻቸውን በማስነሳት ወደፊት ሸመጠጡ – ምሱን ሊሰጡት ።እኛም ጀግንነትንና ቆራጥነት ተጋባብን መሰለኝ ከኋላቸው በመከተል ወደፊት በፍጥነት ተጓዝን።ለተከታታይ 4 ቀናት ሜ/ጀነራል ዘውዱ እና ሜ/ጄ ሰሎሞን ፊት ለፊት በመሆን ውጊያውን እየመሩ እንዳሉ ብናውቅም ፣ ሞርተርና ከዚያ በታች ያሉ የቡድን መሳሪያዎች የሚደርሱበት ቦታ ተጠግተው ስለነበርና እኛም ከዚህ በላይ እንድንጠጋ ስላልተፈቀደልን ሳንገናኝ ቀረን ።

ከ4ቀናት በኋላም የግንባሩ መሪ ሌ/ጀ ባጫ ደበሌ እና የግንባሩ የካባድ መሳሪያዎች አስተባባሪ ሜ/ጄ ዓለምሸት ደግፌ ገርበገው ከሚባለው የፅንፈኛው ወሳኝ ምሽግ ፊት ለፊት በጋራ በተመራው ውጊያ ሞሽጉ ሲሰበር ከነበሩት አመራሮች መካከል አሁንም ሁለቱ ጀነራሎች ሬዲዮዎቻቸውን በመያዝ ያለ እረፍት ሲያስተባብሩ አገኘናቸው። እልህ ፣ ቁጭትና የአትንኩኝ ባይነት ስሜት በፊታቸው ላይ ይንቦገቦጋል ። ያስፈራሉ ።ሁለቱም በቦታው ብዙ አልቆዩም አሁንም መኪኖቻቸውን በማስነሳት እንደ ልማዳቸው ወደፊት ሸመጠጡ – ለቀጣይ የድል ተልዕኮ !እኛም ዕለቱ አስቸጋሪው ምሽግ የተሰበረበት ቀን ስለነበር በኮ/ል ደጀኔ ፀጋዬ የድል መግለጫ ካገኘን በኋላ በፍጥነት ወደ ቆቦ በመመለስ ዜናው ለኢትዮጵያ ህዝብ እንዲደርስ አደረግን።

በማግስቱ እንደተለመደው የውጊያ ቀጣናዎችን በማቆራረጥ ሰራዊታችንና አመራሮቻችን ወደ ሚገኙበት ቦታ ተጉዘን አዲቀይህ የሚባለውን ቦታ እንዳለፍን አዲመስኖ ከሚባለው አካባቢ ደረስን።ይህ ቦታ ጁንታው ከመሸገባቸው ቤተ እምነቶች መካከል የመካነሰላም ቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስቲያን የሚገኝበት በመሆኑ የጋዜጠኞች ቡድን በአካል እየጎበኘን ሳለ ፣ ሜ/ጄ ዘውዱ እና ሜ/ጄ ሰሎሞን በቅርብ መኖራቸውን ስለሰማሁ ለጋዜጠኞች ቡድን መግለጫ እንዲሰጡ ለማቻቸት ወዳረፋበት ተጓዝኩ ።ሀለቱንም ጀነራሎች ከሌሎች አመራሮች ጋር ለአዲጉደም ትይዩ በሆነ አንድ ጉብታ ላይ አገኘኋቸው።

ቦታው ታላልቅና ሰፋፊ ድንጋዮች የሞላበት ነው።ሜ/ጄ ዘውዱ በላይ ያለምንም ፍራሽ ወይም ምንጣፍ በድንጋዩ ላይ ገደም ብለዋል። ሜ/ጄ ሶሎሞን ኢተፋ ደግሞ አንዱን ድንጋይ ደገፍ ብለው ተቀምጠዋል።ሰላምታ ከሰጠሁ በኋላ ከአጠገባቸው አረፍ ብዬ ስመለከት የሁለቱም ጀነራል መኮንኖች ፊቶች እጅግ ጠቁሯል። ነገር ግን ፈገግታ አይለያቸውም። አይኖቻቸው እጅግ ቀልተዋል ግን አያንቀላፋም – እንደ ንስር በጥልቀት ወደፊት ይመለከታሉ እንጂ።እኔም ይህን ሳይ እንዴት ቃለ ምልልስ እንደማደርግ እያሰላሰልሁ ሳለ ሜ/ጄ ዘውዱ ” ” ሶሎሞን ” ብለው ተጣሩና ” ሂድ ትንሽ እረፍ ” አሉ። ሜ/ጄነራል ሰሎሞን ግን ፍርጥም ብለው በመነሳት ወደታች ከሄዱ በኋላ ካርታቸውን አውጥተው ማንበብና መለካት ጀመሩ ።

ከጥቂት ደቂቃዎች በኋላም ሌ/ጄ ባጫ ደበሌ እና ሜ/ጄ አለምሸት ደግፌ አዲመስኖ በተባለው ቦታ ላይ መጡና መግለጫ ሰጡን።ከመግለጫው በኋላም ሁለቱም የእዝ አዛዦች ከግንባሩ መሪ አጭር መመሪያ ተቀብለው ወደፊት ሄዋኔን አልፈው ወደ አዲጉዶም አቅጣጫ እንደ ልማዳቸው መጡ።በነጋታው አዲጉዶም አካባቢ ሌ/ጄ ይመር መኮንንና ሜ/ጄነራል ዘውዱ በላይን እንዲሁም ሌሎች አመራሮችን ሳገኝ ሜ/ጄ ሰለሞንን ግን አላገኘኋቸውም። ምክንያቱም በሄዋኔ አድርገው ወደ ማይጨው በመመለስ ተቆርጦ የቀረውን ኃይል ለመደምሰስ ተመልሰው ነበርና።በዚህ ሁሉ ሁኔታ ፣ የጁንታው የከባድ መሳሪያ ድብደባ ያላንዳች እረፍት እንደ ቀጠለ ነበር ። በዛው መጠን የጀነራሎቹም የውጊያ ስልት ያደገ ስለነበር ላንቃቸውን ለመድፈን ጊዜ አልወሰደባቸውም ።

ም/መ/አ ንጉሴ ውብሊቀርፎቶግራፍ ም/መ/አ ንጉሴ ውብ

መከላከያ ፌስ ቡክ የተወሰደ

Exit mobile version