Site icon ETHIO12.COM

የ30 ሰዎች ህይወት እንዲያልፍ፣ 13,500 ነዋሪዎች ከቄዬአቸው እንዲፈናቀሉ እና 1,396 ቤቶች እንዲቃጠሉ ያደረጉ ጽኑ እስራት እንዲቀጡ ተወሰነ፡፡

የፌዴራል ዐቃቤ ህግ በእነ ዳዊት አብዲሳ መዝገብ ክስ ካቀረበባቸው 117 ሰዎች መካከል በ89ኙ ላይ እንደ ወንጀል ተሳትፏቸው ከ7 – 23 ዓመት በጽኑ እስራት እንዲቀጡ ተወሰነ፡፡

ቅጣቱ ሊጣል የቻለው ተከሳሾቹ በነኃሴ ወር 2010 ዓ.ም በቤኒሻንጉል ጉምዝ ክልል በአዳቡል ድማሉ ወረዳ፤ በደለቲ፣ ኮንቦድሽ እና በዮንግ ቀበሌዎች ብሄርን መሰረት አድርገው በፈጸሙት ወንጀል የ30 ሰዎች ህይወት እንዲያልፍ፣ 13,500 ነዋሪዎች ከቄዬአቸው እንዲፈናቀሉ እና 1,396 ቤቶች እንዲቃጠሉ በማድረጋቸው እንደየ ወንጀል ተሳትፏቸው በወንጀል ህጉ አንቀጽ 240 (3) እና 539 (1) ሀ ስር ክስ ተመስርቶባቸው የነበረ እና ጉዳዩን ቀርቦለት የነበረውም የፌዴራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ተዘዋዋሪ ወንጀል ችሎት የክርክር ሂደቱ ተጠናቆ የካቲት 5 ቀን 2013 ዓ.ም በዋለው ችሎት በሰጠው ፍርድ መሰረት በ89 ተከሳሾች ላይ እንደተሳትፏቸው ደረጃ ጥፋተኛ መሆናቸውን አረጋግጦ ከ7 ዓመት እስከ 23 ዓመት ጽኑ እስራት እንዲቀጡ በመወሰኑ ነው፡፡

ዐቃቤ ህግ በቀጣይም በተለያዩ ቦታዎች በንጹሀን ላይ በተፈጸሙ ወንጀሎች ዙሪያ የሚያካሂዳቸውን ምርመራዎች ውጤታማነት በማረጋገጥ የህግ ተጠያቂነትን በማስፈን እና የህዝቡን ሰላም እና መረጋጋት ለማረጋገጥ በሚደረግ ጥረት ውስጥ በህግ የተጣለበትን ኃላፊነት ለመወጣት ተገቢውን ጥረት የሚያደርግ መሆኑን እየገለጸ ህዝቡም ወንጀል አድራጊዎችን በማጋለጥ፤ መሸሸጊያ በማሳጣት የራሱን ሚና እንዲጫወት የዘውትር ትብብሩን እንጠይቃለን፡፡

attorney general

Exit mobile version