Site icon ETHIO12.COM

በሃላይደጌ አሰቦት እጩ ብሄራዊ ፓርክ በተከሰተ የእሳት አደጋ እስካሁን ከ100 ኪሎ ሜትር ስኩየር የሚገመት ሳርና ቁጥቋጦ

በሃላይደጌ አሰቦት እጩ ብሄራዊ ፓርክ በተከሰተ የእሳት አደጋ እስካሁን ከ100 ኪሎ ሜትር ስኩየር በላይ የሚገመት ሳርና ቁጥቋጦ መውደሙን የፓርኩ አስተባባሪ አስታወቁ።

ባለፈው ሀሙስ መጋቢት 2 ቀን 2013 ዓ.ም ቀትር ላይ በፓርኩ ሰሜናዊ ክፍል የተከሰተውን የእሳት አደጋ በአብዛኛው መቆጣጠር እንደተቻለ የፓርኩ አስተባባሪ አቶ መሐመድ እድሪስ ለኢዜአ ተናግረዋል።

አደጋውን ለመቆጣጠር ባለፉት ሶስት ቀናት ከፍተኛ ጥረት ሲደረግ መቆየቱን ገልጸዋል።

የእሳት አደጋውን ለመቆጣጠር የአፋር ክልል እሳት አደጋ መከላከያ ቡድን፣ የክልሉ የልማት ድርጅቶች፣ የአሚባራና ሃሩካ ወረዳ አመራሮችና ነዋሪዎች እንዲሁም የአገር መከላከያ ሠራዊት አባላት ከፍተኛ ተሳትፎና ጥረት ማድረጋቸውን አመልክተዋል።

“ይሁንና በአካባቢው ባለው ከፍተኛ ንፋስና ሙቀት ቃጠሎውን ፈጥኖ ለመቆጣጠር አላስቻለም” ሲሉ የቁጥጥር ጥረቱ ፈታኝ እንደነበር አስረድተዋል።

እስከ ትናንት ምሽት ድረስ ከፍተኛ የእሳት ቃጠሎ በነበረባቸው አካባቢዎች እሳቱን ለማጥፋት በተደረገ ጥረት አብዛኛውን ክፍል መቆጣጠር እንደተቻለ አስታውቀዋል።

ዛሬም በፓርኩ የተለያዩ ቦታዎች ላይ ተበታትነው የሚገኙ አነስተኛና ቀላል እሳቶችን የማጥፋት ስራ እየተከናወነ መሆኑን ጠቁመው፤ አደጋው በቁጥጥር ስር የሚውልበት ደረጃ ላይ መድረሱን ገልጸዋል።

ለሶስት ቀን በዘለቀው ቃጠሎ ከ100 ኪሎ ሜትር እስኩየር በላይ የሸፈነ ሳርና ቁጥቋጦ ሙሉ በሙሉ መውደሙን አመልክተው፤ በቃጠሎው በዱር እንስሳትና አእዋፎች ላይ ጉዳት መድረሱን ጠቁመዋል።

የእሳት አደጋው መንሰኤ ሰው ሰራሽ መሆኑን ያመለከቱት አስተባባሪው፤ ዝርዝር የአደጋው መንስኤና የጉዳት መጠን በሚመለከታቸው አካላት ተመርመሮ የሚገለጽ መሆኑን አመላክተዋል።

ከ1965 ዓ.ም ጀምሮ በጥብቅ የዱር እንስሳት ክልልነት ተዋቅሮ በ2006 ዓ.ም ወደ እጩ ብሄራዊ ፓርክነት ያደገው ሃላይደጌ አሰቦት ፓርክ በአፋር ክልል ገቢ-ረሱና በኦሮሚያ ክልል ምእራብ ሃረርጌ ዞኖች ውስጥ እንደሚገኝ ተናግረዋል።

ፓርኩ ትልቁ የሜዳ አህያ፣ የሜዳ ፍየልና ሳላ ጨምሮ የዱር እንስሳትና አእዋፍ መጠለያ መሆኑን አቶ መሐመድ አስታውቀዋል።

Exit mobile version