Site icon ETHIO12.COM

በደቡብ ክልል የእርስ በርስ ግጭት በማስነሳት ጉዳት አድርሰዋል የተባሉ ከ35 በላይ ግለሰቦች በእስራት ተቀጡ

በደቡብ ክልል ባስኬቶ ልዩ ወረዳ በ11 ቀበሌ የእርስ በእርስ ግጭት በማስነሳት ለአራት ሰዎች ህይወት መጥፋትና 31 ሺህ ሰዎች ከቀያቸው እንዲፈናቀሉ አድርገዋል  የተባሉ ከ35 በላይ ተከሳሾች  ከ8ስምንት እስከ 20 አመት በሚደርስ ጽኑ እስራት ተቀጡ። ተከሳሾቹ መስከረም 16 ቀን 2011 ዓ.ም በ11 ቀበሌዎች ባስነሱት የእርስ በርስ ግጭት ከ88 ሚሊየን ብር በላይ የሚገመት ንብረት ወድሟል ተብሏል።

የቅጣት ውሳኔው ያስተላለፈው የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 3ኛ የአርባምንጭና አካባቢው ተዘዋዋሪ ወንጀል ችሎት ነው። የቅጣት ውሳኔ ው ከተላለፈባቸው መካከል የባስኬቶ ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ ሳሙኤል ደሳለኝ፣ የባስኬቶ ልዩ ወረዳ የደኢህዴን ድርጅት ሃላፊዎች የነበሩ አቶ አናጋው ደጀኔ፣ አቶ አለም ብርሃን ካሳሁን እና  የባስኬቶ ልዩ ወረዳ የደኢህዴን ድርጅት ገጠር ዘርፍ ሃላፊ የነበሩት አቶ  ዳንኤል ገረመው ይገኙበታል።

ግሰለቦቹ የባስኬቶ ልዩ ወረዳ እና የመንግስት አመራሮች የነበሩና በነሃሴ 12 ቀን 2010 ዓ.ም በቡድን በመደራጀት ከመለኮዛ ወረዳ 11 ቀበሌዎችን በሃይል ወደ ባስኬቶ ለመውሰድ የእርስ በርስ ግጭት እንዲነሳ እና የሰው ህይወት እንዲጠፋ ንብረትም እንዲወድም ማድረጋቸውን ዐቃቤ ህግ አመላክታል።

በአጠቃላይ ሰባት ክሶች በየደረጃው የቀረበባቸው ሲሆን ተከሳሾቹ ወጣቶችን አደራጅተው ለዘመናት ተከባብሮ በፍቅርና በአንድነት የኖረን ህዝብ እርስ በርስ እንዲጋጭ ማድረጋቸው በክሱ ተጠቅሷል።

በዚህ መልኩም መስከረም 16 ቀን 2011 ዓ.ም በዚህ ግጭት መነሻ የአራት ሰዎች ህይወት ማለፉን እና 88 ሚሊየን 885 ሺህ 487 ብር ግምት ያለው ንብረት መውደሙም በክሱ ተመላክቷል። በተጨማሪም በወቅቱ 31 ሺህ የአካባቢው ህዝብ ከመኖሪያ ቀየው እንዲፈናቀል ማድረጋቸውንም በክሱ ጠቅሷል።

ተከሳሾቹ ነሃሴ 12 ቀን 2010 ዓ.ም ጀምሮ በተለያዩ ጊዜያት ማህበረሰቡን እየሰበሰቡ ባስኬቶ ወረዳ ተካለን የዞን ጥያቄ እናነሳለን በማለት በግድ ቃለ መሃላ እንዲፈፅሙ ሲያስገድዱ እንደነበረም ተጠቁሟል።

በተጨማሪም በዚህ የማይስማማ ቤቱ ይቃጠላል እራሱም በ30 ጦር ተወግቶ ይገደላል እያሉ ማስፈራሪያ ሲሰጡ እንደነበርም ነው የተጠቀሰው። በዚህ መልኩ የእርስ በርስ ግጭት ማስነሳት ወንጀል ክስ ቀርቦባቸው የዐቃቤ ህግ፣ የሰውና የሰነድ ማስረጃ የተሰማ ሲሆን ተከሳሾቹም እንዲከላከሉ ተደርጓል።

ይሁንና እራሳቸውን በበቂ መልኩ መካላከል ባለመቻላቸው የጥፋተኝነት ፍርድ ያስተላለፈው ፍርድ ቤቱ በተከሰሱበት ወንጀል 46ኛ፣ 48ኛ እና 49ኛ ተከሳሾችን እያንዳንዳቸውን በ20 አመት ጽኑ እስራት እንዲቀጡ የወሰነ ሲሆን ቀሪ ተከሳሾችን እያንዳንዳቸውን እስከ 8 አመት በሚደርስ ጽኑ እስራት እንዲቀጡ ወስናል።

በታሪክ አዱኛ –  (ኤፍ ቢ ሲ)

Exit mobile version