Site icon ETHIO12.COM

የቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል በኦክስጅን እጥረት ሳቢያ ታካሚዎችን ለመርዳት መቸገሩን አስታወቀ

የቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ሚሌኒየም ሜዲካል ኮሌጅ በኦክስጅን እጥረት ሳቢያ ታካሚዎችን ለመርዳት እየተቸገረ መሆኑን አስታወቀ፡፡

በተጨማሪም በሆስፒታሉ ያጋጠመውን የኦክስጅን አጥረት ተከትሎ ቀደም ሲል ለሌሎች ሆስፒታሎች ይሰጥ የነበረውን አቅርቦት ማቋረጡንም ነው የገለጸው።

በሆስፒታሉ የፋሲሊቲ መሃንዲስ አቶ ሰለሞን ሸዋንግዛው በአሁኑ ወቅት የኮቪድ-19 ወረርሽኝ እየተባባሰና የታማሚዎች ቁጥርም እያሻቀበ በመምጣቱ ለኦክስጅን ፈላጊ ታካሚዎች ፈተና ሆኗል ነው ያሉት፡፡

እጥረቱን ለመፍታት በማዕከሉ 24 ሰዓት እየተሰራ ቢሆንም ችግሩን ማቃለል አዳጋች መሆኑን ጠቁመዋል።

ችግሩ በዚሁ ከቀጠለ ኦክስጅን የሚያስፈልጋቸው ታካሚዎችን ፈጽሞ ማከም የማይቻልበት ደረጃ ላይ ሊደርስ ይችላል የሚል ስጋት እንዳላቸውም ነው ያስረዱት።

የችግሩን አሳሳቢነት በመገንዘብ ማህበረሰቡ የኮቪድ-19 ተጋላጭነትን ለመቀነስ ጥንቃቄ እንዲያደርግ ማሳሰባቸውንም ኢዜአ ዘግቧል።

በሌላ ተመሳሳይ የኮቪድ ዜና

በህንድ 314 ሺህ 835 ሰዎች በ24 ሰዓታት ውስጥ ኮቪድ 19 እንደተገኘባቸው የሀገሪቱ የጤና ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡ በሀገሪቱ ከየትኛውም የዓለም ክፍል በተለየ ሁኔታ ወረርሽኙ እየተስፋፋ መሆኑን መረጃዎች ያሳያሉ፡፡

ባለፉት ሰባት ተከታታይ ቀናትም በየዕለቱ ከ200 ሺህ ሰው በላይ በወረርሽኙ እየተያዘ ይገኛል፡፡ ከዚህ ቀደም ህንድ በወረርሽኙ አማካኝነት በአንጻራዊነት አነስተኛ የሟቾች ቁጥር ስታስተናግድ ቆይታለች፡፡

ሆኖም ከቅርብ ሳምንታት ወዲህ የሟቾች ቁጥር እየጨመረ መምጣቱ ነው የተገለጸው፡፡ በ24 ሰዓታት ውስጥም 2 ሺህ 104 ሰዎች ለሕልፈት ተዳርገዋል፡፡

በሀገሪቱ እያጋጠመ ያለው የሖስፒታል አልጋና የኦክስጅን እጥረት ሁኔታውን አሳሳቢ ደረጃ ላይ እንዳደረሰው እየተነገረ ይገኛል፡፡ የደልሂ ከፍተኛ ፍርድ ቤትም ከኦክስጅን አቅርቦት ጋር በተያያዘ ማዕከላዊ መንግስትን ወቅሷል ሲል ቢቢሲ ነው የዘገበው


Exit mobile version