Site icon ETHIO12.COM

“ቤኒሻንጉል ወደ ሱዳን ለመቀላቀል የሚያደርጉትን ትግል አረቦች ይደግፉ”የሚል ጥሪ ቀረበ

ግብጻዊያን የፓለቲካ ተንታኞች እና አክቲቪስቶች ኢትዮጵያን ለማደከምና ለማፍረስ ከአሁን የተሻለ ጊዜ የለም በሚል የተቀናጀ ሥራ እየሰሩ መሆናቸውንና የአረብ አገሮች እገዛ እንዲያደርጉ በግልጽ ጥሪ እያቀረቡ ነው። አምስት ሚሊዮን የሚሆነው የቤኒሻንጉል ሕዝብ ሱዳናዊና አረብ ነው ብለዋል። ይህ የተባለው የአማራ ክልል ላይ የታየውን ተቃውሞ ተከትሎ ነው።

ከሰሞኑ ግብጻዊያኑ የፓለቱካ ተንታኝና አክቲቪስቶች በግልጽ በአገሪቱ መገናኛ ብዙኃን እና ማህበራዊ ሚዲያዎች ብቅ እያሉ በኢትዮጵያ የውስጥ ጉዳይ በመግባት የተለያዩ አገር አፍራሽ ሥራዎችን ሃሳብቸውንና ፍላጎታቸውን እየገለጹ ናቸው።

በአገሪቱ ታዋቂ የሆነው የፓለቲካ ተንታኝ ከሰሞኑ በቴሌቪዥን ሥርጭት ላይ ቀርቦ “የቤንሻንጉል ክልል የሡዳን መሬት ሥለሆነ ወደሡዳን ለማካለል የአረብ አገራት ድጋፍ እንዲያደርጉ” ሲል ጥሪ አቅርቧል።

“ቤንሻንጉሎችን መሬቱ የኛ ስለሆነ ለቃችሁ ውጡ እያሉ የአማራ እና የኦሮሞ ብሄር ተወላጆችን እያባረሩዋቸው ነው” ሲል የተናገረው ይህ ግብጻዊ፤ “ግድቡ ያለው በዚሁ ክልል ስለሆነ ጉሙዞች እንደ ደቡብ ሱዳን ህዝቦች ነፃ እንዲወጡ ማገዝ አለብን” ብሏል።

“ይሄንን አጋጣሚ በመጠቀም የአብይ አህመድን መንግስት ማዳከም አለብን ይህንን ማድረግ ካልቻልን ሌላ ተጨማሪ እንድሎችን አናገኝም” በማለት ሲናገር ተደምጧል። በተመሳሳይ ሼሪፍ ኤልሳሊይ የተባለ አክቲቪስት ከሰሞኑ “በኢትዮጵያ በሁሉም ክልሎች ያሉ የሽምቅ ተዋጊዎች’ የግብፅ መንግስት ድጋፍ እንዲሰጣቸው ጠይቀዋል፤ መንግስታችንም ይሄንን ተቀብሎ ወደስራ ገብቷል” ሲል መግለጹ ይታወሳል። ይሄው ግለሰብ “የኢትዮጵያ ማዕከላዊ መንግስት ተዳክሟል፤ ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር የሚዋጉ ሀይሎች የግብፅ ስትራቴጂካዊ ወዳጆች ናቸው፤ መንግስት መሰራት ያለበትን እየሰራ ነው። ሁሉንም ነገር ለእናተ ማሳወቅ የለበትም” ሲል መግለጹም አይዘነጋም። የግብጻዊውን የፓለቲካ ተንታኝ መልዕክት የያዘውን ቪዲዮ ከስር ያለውን ሊንክ ተጭነው ያገኙታል ሲል የዘገበው ኢፕድ ነው።


Exit mobile version