Site icon ETHIO12.COM

ኦነግ የሽግግር መንግስት ምስረታውን አልቀበልም አለ፤

በኢትዮጵያ የሽግግር መንግስት እንዲቋቋም የቀረበውን ሰነድም ሆነ አዋጅ እንደማያውቀው ራሱን ትክክለኛ የኦነግ ባለቤት አድርጎ የሚያቀርበው ክፍል አስታወቀ። በአቶ ዳውድ ኢብሳ የሚመራው ኦነግ ከኦፌኮ ጋር በመሆን ” የኤርትራ ሰራዊት ከትግራይ ይውጡ” የሚል ጥያቄ አካቶ ያቀረበውን ሰነድ ” የማይሰራ” ብሎታል።

በአቶ አራርሳ የሚመራው ኦነግ በሰጠው መግለጫ በአገሪቱ ለውጥ ከተፈጠረ በሁዋላ ወደ አገር ቤት ሲገቡ የሽግግር መንግስ፣ ጊዜያዊ መንግስት የሚለው ጥያቄ እንደማያስኬድና ምርጫ ብቻ እንደሚያዋጣ አስቀድመው አቅጣጫ ማስቀመጣቸውን ገልጸዋል።

ከመቶ በላይ ፓርቲ ባለበት አገር የሽግግር መንግስት እንዲቋቋም ማሰብ የተወሳሰበ ችግር እንደሆነ የተያዘ አቋም እንዳለ ያመለከቱት ምክትል ሊቀመንበሩ አቶ ቀጀላ መርዳሳ ከሰኔ 24 ጀምሮ በኢትዮጵያ የሽግግር መንግስት እንዲቋቋም የቀረበው ሰነድም ሆነ አካሄድ ድርጅታቸው ኦነግ አያውቀውም። ቀርቦለት የመከረበት አግባብም የለም። ቢጋበዙም ሊቀበሉት እንደማይችሉ አመልክተዋል።

በኢትዮጵያ ሁሉን ያካተተ የሽግግር መንግስት እንዲመሰረት አዋጅ ያዘጋጁት አቶ ዳውድ የሚመሩት ኦነግና ኦፌኮ ናቸው። ፕሬዚዳንቷንና የአገር መከላከያን ያሳተፈ ሁሉን አካታች የሽግግር መንግስት አወቃቀር ይፋ ያደረገው አዋጅ የኤርትራ ሰራዊት ከትግራይ ነቅሎ እንዲወጣ የሚጠይቅ መሆኑ ይታወሳል።

ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ በምርጫ ተወዳድረው ያላሸነፉ ፓርቲዎች እንደተሳትፏቸው ብልጽግና ከታች እስከ ላይናው መዋቅር እንደሚያሳትፋቸው መግለሳቸውን ተከትሎ የወታውን አዋጅ አቶ ቀጀላ ” ሊሰራ የማይችል” ሲሉ አጣጥለውታል። ሳይለዩ በፊት ጀመሮ ከያዙት ስትራቴጂ ጋር የሚጋጭ በመሆኑና ጥቅም ስለማያመጣ፣ በተለይ በዚህ ጊዜ እንዲህ ያለውን ጉዳይ ማንሳት አግባብ ባለመሆኑ ከምርጫ ውጪ የሚደረግ ማናቸውም እንቅስቃሴ ተቀባይነት እንደሌለው ጠቅሰው ” በአቶ አራርሶ ቢቂላ የሚመራው የኦሮሞ ነጻነት ግንባር በኦሮሞ ፌዴራላዊ ኮንግረስና ዳውድ ኢብሳ በሚመሩት የኦሮሞ ነጻነት ግንባር ስም እየተሰራጨ ያለውን የሽግግር መንግስት አዋጅ ” አንቀበልም ብለዋል።

በአቶ ዳውድና እሳቸውን አግልሎ ራሱን የኦነግ ወራሽ ያደረገው የአቶ አራርሶ ኦነግ የልዩነታቸው አንዱና ዋና ምክንያት ድርጅቱ ከመርህ ውጪ ከትህንግ ጋር ግንኙነት ማድረጉ፣ ግንኙነቱ በፓርቲ ደረጃ ሳይሆን በግል መሆኑ፣ ይህን ድርጊት አቶ ዳውድ እንዲያሻሽሉ ቢጠየቁ ፈቃደኛ ሊሆን ባለመቻላቸው ፓርቲው የሰላምና የጦርነት ሁለት አማራጭ ይዞ መጓዝ አይችልም በሚል ምክንያት እንደሆነ አቶ ቀጀላ መናገራቸው ይታወሳል። ከሁሉም በላይ ትህነግ በኦሮሞ ሕዝብ ላይ የፈጸመው ግፍ ሊረሳ የማይችል ሆኖ ሳለ ከዚህ ድርጅት ጋር ማበር ኦሮሞን እንደመካድ ጭምር እንደሚቆተርም አስታውቀው ነበር።

አዋጁ ይፋ ከመሆኑ በፊት ለአሜሪካ መንግስት በዶክተር መረራ አማካይነት መቅረቡ በተለያዩ ሚዲያዎች ሲገለጽ መቆየቱም የሚታወስ ነው። በዚህም መነሻ ይሁን በሌላ በግልጽ ባይታወቅም አሜሪካና ሌሎች አገራት ምርጫውን አወድሰው፣ ምርጫ ቦርድን እንደሚያምኑ ምስክርነት ሰጠው ሁሉን ያካተተ ውይይት እንዲደረገ ደጋግመው መጠየቃቸው አይዘነጋም።

አዋጁን አቶ ታዬ ደንደአ ” የባንዳዎች ሴራ” ሲሉ ባጭሩ እንዳጣጣሉት የሚታወስ ነው። በሌላ በኩል ደግሞ መንግስት ሁሉን ያካተተ ውይይት ለማዘጋጀት አስቀድሞ ዕቅድ እንዳለው በሰላም ሚኒስቴር አማካይነት አመልክቷል።

Exit mobile version