Site icon ETHIO12.COM

ደሴ ዙሪያ – እንደ መሰንበቻው ከርቀት ተኩስ ይሰማል፣ ከሩቅ በተተኮሰ ከባድ መሳሪያ በተፈናቃዮች ማረፊያ ላይ ጉዳት ደረሰ

የአብኑ የሱፍ አሁን ከሁለት ሰዓት በፊት በግል ፌስ ቡኩ ያሰራጨው መረጃ ነው። አቶ ጌታቸው ረዳ እሱና ባልደረባው ወደ አዲስ አበባ እንደተመለሱ አድርጎ ቢገልጽም በየደቂቃው ከባልደረባው ጋር ሆኖ ከግንባር መረጃ እያሰራጨ እንደሚገኝ ተረጋግጧል። አቶ ጌታቸው ” የአማራ ደም አለብህ” በሚል ንዴት የወለደው ማስፈራሪያ ሰንዝረውበታል። ይሁን እንጂ እሳቸው የሚወከሉበት ሰራዊት ምን በወረራቸው የአማራ ክልል የፈጸመውን ወንጀል በምን መልክ እንደሚያዩት ወይም ሕዝብ እንዴት እንደሚሰማቸው ——

Yesuf Ibrahim በአሁኑ ሰዓት ወሎ የኒቨርሲቲን አልፈን ቦሩ መስመር ካለው የመከላከያ ሰራዊት ጋር ነን። ሰሞኑን በደረሰበት ከባድ ምት የተበታተነው ወራሪ ሀይል ደሴ ከተማ በየት በኩል ነው? እያለ በየአቅጣጫው እየተራወጠ ነው። አሁን በዙሪያው ከበቂ በላይ ሀይል አለ። ጧት ላይ በጦሳ በኩል ሰርጎ ለመግባት የፈለገው ተባራሪ ሀይል 20 ደቂቃ ባልሞላ ሰአት ተጠርጓል። በቦሩ አቅጣጫም በወንዝ፣ በጢሻና በየሸለቆው ተደብቀው የከረሙት አሁን ረሀብና ውሃ ጥም ሲከብዳቸው ከጉድጓዱ የግድ እየወጡ እሩምታ በመተኮስ ለማደናገር ሞክረው ነበር። እያንዳንዷን የጥይት ተኩስ በሽህ እያባዙ ፕሮፖጋንዳ የሚነፉት ናቸው የወያኔ ቀሪ ጉልበት ለመሆን እየሞከሩ ያሉት። ዛሬ ካስተኳሾች ጋር በርካታ የወሬ ሸቃጮችም በቁጥጥር ስር ውለዋል።ከምር! ሁሉም ነገር በስርዓት ተይዟል፣ በወሬ ተኩስ ከተማ አይገባም! ደግሞ እነሱ ትንኝ ናቸው እንደ ሳይታዩ ገቡ፣ ገቡ፣ ገቡ፣ የሚባለው?


የጀርመን ድምጽ ሬዲዮ የከተማዋን ከንቲባ አነጋግሮ የአሳቸውን ሃሳብ ወደሁዋላ በማድረግ ” አንድ ነዋሪ ነገሩኝ” ሲል ደሴ አቅራቢያ ውጊያ መኖሩን መዘገቡን ተከትሎ ከደሴ ያነጋገርናቸው ” ከርቀት ተኩስ መስማት የተለመደ ነው” ሲሉ አስታወቁ። ከዚህ በፊት የጀርመን ድምጽ ኩታ በር ሳትያዝ በማህበራዊ ገጹ ላይ ብቻ አድርጎ ዜና ማስተላለፉ ይታወሳል።

“የደሴ ከተማ ምክትል ከንቲባ አቶ ሠዒድ የሱፍ በከተማዪቱ አቅራቢያ የተኩስ ድምጽ የሚሰማ ቢሆንም፤ከተማው ላይ ጠላት እንዳሰበው የተረበሸ ነገር የለም» በማህበራዊ ገጹ ያሰፈረው የጀርመን ድምጽ፣ ሌላ የከተማ ነዋሪ ጠቅሶ ውጊያው በቅርብ ረቀት ደሴ ዩኒቨርስቲ አካባቢ እንደሆነ አመልክቷል። ይህንን ጣያቄ ግን ለከንቲባው አላነሳላቸውም። ያነጋገርናቸው እንዳሉት የተኩስ ድምጽ እንደ መሰንበቻው ሁሉ መኖሩን አስታውቀው የተለየ አዲስ ነገር እንደሌለ ተናግረዋል። አዲሱ ጉዳይ ሰፊ ቁጥር ያለው የጎንደርና ጎጃም ፋኖ፣ መከላከያ ሰራዊትና ልዩ ሃይል መስፋት ወደ ደሴ መግባቱ እንደሆነ ገልጸዋል።

ከንቲባው “የደሴ ከተማ ነጋዴዎች መደበኛ የንግድ ስራቸውን እያከናወኑ ለጽጥታ ሃይሎች የሚጠበቅባቸውን ድጋፍ እያደረጉ ናቸው” ማለታቸው ተመልክቷል። ዜናው በሌላ በኩል ከውስጥ ወሽቆ ያስነበበው ቢኖር በደሴ ከባድ መሳሪያ ክሩቅ ተተኩሶ ሰላዊ ዜጎችን መጉዳቱን ነው።

በትናንትናው ዕለት ምንነቱ ያልታወቀ ከባድ ጦር መሣሪያ ባደረሰው ጉዳት አንድ ሰው ላይ ከባድ ሁለት ሰዎች ላይ ቀላል በአጠቃላይ ሦስት ሰዎች ላይ የመቁሰል አደጋ መድረሱንም አቶ ሠዒድ ገልጠዋል። የከባድ ጦር መሣሪያ ጥቃቱ ትናንት የተሞከረው ከሰሜን ወሎ ዞን ተፈናቅለው የመጡ የኅብረተሰብ ክፍሎች አርፈውበት በነበረው መጠለያ አቅራቢያ ነውም ብለዋል። ዓላማውም መጠለያው ላይ ጉዳት ማድረስ ነበር ሲሉ አክለዋል።

ደሴ ከተማ አስተዳደር መናፈሻ ክፍለ-ከተማ ነዋሪ የሆኑት አቶ ይመር ሐሠን በበኩላቸው፦ ትናንት እና ከትናንት በስትያ በከባድ ጦር መሣሪያው ሁለት ሰዎች መሞታቸውን ለዶይቸ ቬለ ተናግረዋል። ከትናንትና ወዲያ ገራዶ የሚባለው አካባቢ ትናንት ደግሞ ዘጠኝ ሰአት አካባቢ ላይ «እኔ በር ላይ ከባድ መሣሪያ ወድቆ የአንድ ንፁሃን ሰው ሕይወት ጠፍቷል» ሲሉም አክለዋል። ከመኖሪያ ቤታቸው አቅራቢያ ያሉት የባሕር ዛፎች ፍንጣሪውን ቢቀንሱትም መኖሪያ ቤታቸው እና ሱቃቸው ላይ እንዲሁም የጎረቤቶቻቸው መኖሪያ ቤቶች ላይ ጉዳት ደርሷል ብለዋል። መኖሪያ ቤታቸው አቅራቢያ ትናንት ሕይወቱ ያለፈው ወጣትም መርሳ ከሚባል አካባቢ ተፈናቅሎ የመጣ መሆኑን ገልጠዋል። በተጨማሪም በትናንቱ ጥቃት ሌላ አንዲት ሴት ቆስላ ሐኪም ቤት በሕክምና ላይ እንደምትገኝ የጀርመን ድምጽ ዘግቧል።


የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት በበኩሉ ይህንን የሚከተለውን ዘግቧል። በአሸባሪ ቡድኑ የሀሰት ወሬ ሳይሸበሩ መደበኛ የንግድ ስራቸውን እያከናወኑ መሆናቸውን፤ ይልቁንምን ለአገር ክብርና አንድነት እየታገሉ ላሉ የጸጥታ ኃይሎች የሚጠበቅባቸውን ድጋፍ እያደረጉ መሆኑን የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት ዘገቢዎች በከተማዋ ተዘዋውረው ያነጋገራቸው የደሴ ከተማ ነጋዴዎች ተናገሩ።
በአትክልት ንግድ ስራ ተሰማርተው ያገኘናቸው አቶ ታደሰ አያሌው፤ “እኛ በአሸባሪ ቡድን የሀሰት ወሬ የትውልድ ቦታችንን ለቀን የትም አንሄድም። ይልቁንም እየነገድን ለመከላከያ ሰራዊት፣ ለአማራ ልዩ ሃይል እና ለመላው የጸጥታ አካሉ የሚጠበቅብንን እያደረግን እየሰራን እየደገፍን ነው” ብለዋል።
ግንባር ድረስ ለምዝመት ፍላጎት ቢኖረኝም እየነገዱ ለስራዊቱ ስንቅ ማቀበል አንዱ የትግል አካል በመሆኑ እየሰራሁ ድጋፍ እያደረኩ ነው ሲሉ ተናግረዋል።
ወጣቱ የመከላከያ የኋላ ደጀን በመሆን ስንቅና ትጥቅ በማቅረብ ግንባር እንደሚገኝ የገለጹት አስተያየት ሰጪው፤ በህዝቡ ዘንድ እየታየ ያለው ወኔ አሸባሪውን በአጭር ጊዜ በመደምሰስ ኢትዮጵያ ወደቀድሞው ሰላሟ እና አንድነቷ መመለስ ያስችላል ብሏል።
የአትክልትና ፍራፍሬ ነጋዴዋ ወይዘሮ አሰበወርቅ ይማም በበኩላቸው፤ “የሀሰቱን ወሬ ለምደነዋል፣ እኛ ጠንክረን በመስራት የኢትዮጵያን አንድነት እና ሰላም ለማረጋገጥ የበኩላችንን ሃላፊነት መወጣት አለብን” ብለዋል።
“ሞት የትም ቦታ ይሞታል፣ ትልቁ ክብር በተወለዱበት ስፍራ ታግሎ መሞት ነው። እኛ የደሴ ከተማ ነጋዴዎች የሽብር ቡድኑን መታገል እንጂ የትም መሸሽ አንፈልግም”ብለዋል።
ሌላኛው በልብስ ንግድ ስራ ተሰማርቶ በስራ ላይ ያገኘነው አቶ መልካሙ ሁንያለው በበኩሉ፣ እኛ ተረጋግተን እየሰራን ነው። ቦታችን ትተን መቸም ቢሆን አንሸሽም። ለእናት አገራችን ከገንዘብ እስከ ህይወት መስዋእትነት ለመክፈል ዝግጁ ነን ሲል አስተያየቱን ገልጿል።
በሞገስ ተስፋ (ደሴ)


Exit mobile version