የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ከንግድ ባንክ 300 ቢሊዮን ብር ዕዳ እንዳለበት ተገለጸ። የዕዳ ጫናውን ለማቃለል የባንክ ወልዱም ጭምር ተፅእኖ እያሳደረ መሆኑም ተመልክቷል። የኢትዮጵያ ኤልክትሪክ ኃይል የዕዳ ጫናን ለማቃለል ትኩረት ሰጥቶ መስራት እንዳለበት ሪፖርቱ የቀረበለት ፓርላማ አሳስቧል።
ዜና ፓርላማ እንዳለው የኢትዮጵያ ኤልክትሪክ ኃይል ያለበትን የዕዳ ጫናን ለማቃለል ትኩረት ሰጥቶ መስራት እንዳለበት በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግስት ልማት ድርጅቶች ቋሚ ኮሚቴ አመልክቷል።
የመንግስት ልማት ድርጅቶች ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ፤ የኢትዮጵያ ኤልክትሪክ ኃይል የ9 ወራት የስራ አፈፃጸም ሪፖርት ባዳመጠበት ወቅት የተቋሙ የብድር ጫና በጣም ከፍተኛ መሆኑን ተመልክቷል፡፡
የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ የተከበሩ ፕሮፌሰር መሐመድ አብዶ የኢትዮጵያ ኤልክትሪክ ኃይል ለሀገር ዕድገት እያበረከተ ያለው አስተዋጽኦ በጣም ከፍተኛ መሆኑን ጠቁመው፤ ካለበት የዕዳ ጫና ለመውጣት የታሪፍ ማሻሻያዎችን የውጭ የሃይል ሽያጭ አቅሞችን በማጠናከር እና የውስጥ ገቢን በመሳደግ ለዕዳ ቅነሳው ትኩረት ሰጥቶ መስራት እንዳለበት አሳስበዋል፡፡
ሰብሳቢው አያይዘውም፤ በሁሉም አካባቢዎች ፍትሃዊ የሆነ የኃይል አቅርቦትና ስርጭት መኖር እንዳለበት እና በህብረተሰቡ ዘንድ የሚነሱ ቅሬታዎችን መፍታት እንደሚገባ ጠቁመዋል፡፡
የቋሚ ኮሚቴው ምክትል ሰብሳቢ የተከበሩ ስለሽ ኮሬ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ተቋሙ በዘጠኝ ወራት አፈጻጸሙ 94 በመቶ ኃይል ማመንጨት እና መጠቀም መቻሉ እንዲሁም ለጎረቤት ሃገራት የሚደረገውን የኃይል አቅርቦት ሽያጭ የሚበረታታ ተግባር መሆኑን ገልጸዋል፡፡
ከተቋማት ጋር ያለውን ቅንጅታዊ አሰራር በማጠናከር ሌሎች የኃይል አማራጮችን በማመንጨት እና በመጠቀም የተቋሙን አቅም በማሳደግ በዘርፉ ብዙ ስራዎችን መስራት እንደሚገባ ምክትል ሰብሳቢው አመላክተዋል፡፡
ተቋሙ በተለያዩ አካባቢዎች ያሉ ንብረቶችን ከስርቆት እና ከብክነት ለመከላከል ፤ የጾታ ስብጥር እና ከክልሎች ጋር ያሉበትን ከፍተቶች ለማረም ትኩረት ሰጥቶ መስራት እንደሚጠበቅበት የቋሚ ኮሚቴው አባላት አስገንዝበዋል፡፡
የኢትዮጵያ ኤልክትሪክ ኃይል ዋና ሥራ አስፈፃሚ ኢንጂነር አሸብር ባልቻ ተቋሙ አስተማማኝ እና ዘላቂ የኤሌክትሪክ ኃይል ለማቅረብ የአፍሪካ የኃይል አቅርቦት ማዕከል ለመሆን ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑን አስረድተዋል፡፡
ተቋሙ ህዳሴ ግድብን ጨምሮ ለብዙ የመንግስት ፕሮጀክቶች የኃይል አቅርቦት እያከናወነ ቢሆንም ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ 300 ቢሊዮን ብር ብድር እንዳለበት እና የዕዳ ጫናውን ለማቃለል የባንክ ወልዱም ጭምር ተፅእኖ እያሳደረ መሆኑ አስረድተዋል፡፡
በቀጣይ ተቋሙ ከጅቡቲ፣ ከኬኒያ እና ከሱዳን በተጨማሪ ለታንዛኒያ እና ደቡብ አፍሪካ ኤሌክትሪክ ኃይል በማቅረብ የዕዳ ጫናውን ለመቀነስ የውጭ ምንዛሬ ለማግኘት በዕቅድ መያዙን ዋና ሥራ አስፈፃሚው አስረድተዋል፡፡
በተቋሙ ውስጥ የሴቶች ተሳትፎ 15 በመቶ እንደነበር እና አሁን ላይ 17 በመቶ ማሳደግ መቻሉን ገልፀዋል።
በተቋሙ የንብረት ስርቆት እና ዝርፊያ ጋር በተያያዘ ብዙ የግንዛቤ ስራ ቢሰራም ለውጥ እንዳልመጣ እና በቀጣይ በአካባቢው ያሉ የመንግስት የፀጥታ አካላት ለጉዳዩ ትኩረት ሰጥተው በመስራት የመንግስት እና የህዝብ ሃብትን መጠበቅ እንዳለባቸው አመላክተዋል፡፡
የኢትዮጵያ ኤልክትሪክ ኃይል የዕቅድና ክትትል ሥራ አስፈፃሚ አቶ አንዱዓለም ሲአ የኃይል አቅርቦትና ፍትሃዊነት ጋር በተያያዘ ያለውን ችግር ለመፍታት ከዓለም ባንክ በሚገኘው የብድር ገንዝብ የህዝብ ቁጥርን እና አሰፋፈርን መሰረት ባደረገ መልኩ በቀጣይ ትኩረት ሰጥተው እንደሚሰሩ ገልጸዋል፡፡
ተመጣጣኝ የኃይል ሽያጭ ታሪፍ አለመኖር፤ ውጭ ምንዛሬ እጥረት፤ የንብረት ስርቆት እና የካሳ ክፍያ ጋር በተያያዘ ችግሮች መኖራቸውን አቶ አንዱዓለም ለቋሚ ኮሚቴው አስረድተው እልባት እንዲያገኝ ብትኩረት ይሠራል ብለዋል፡፡