ETHIO12.COM

በአዲስ አበባ የጦር መሳሪያ ከአዘዋዋሪዎቹ ጋር ተያዘ

የአዲስ አበባ ፖሊስ የተጠርጣሪዎቹን ስምና ማንነት ይፋ ሳያደርግ እንዳስታወቀው ከሆነ በአዲስ አበባ ሁለት ስፍራዎች ከባድ የሚባል መሳሪያ ሲያዘዋሩ የነበሩ ተጠርጣሪዎችን በቁጥጥር ስር አውሏል።

በቂርቆስ እና በአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ ህገ-ወጥ የጦር መሳሪያ በተሸከርካሪ ጭነው ሲንቀሳቀሱ የነበሩ 3 ግለሰቦች ተይዘው ምርመራ እየተጣራ መሆኑን ነው የአዲስ አበባ ፖሊስ ያስታወቀው። ህገ-ወጥ የጦር መሳሪያው የተያዘው ከትናንት በስቲያ በቂርቆስ ክፍለ ከተማ ወረዳ 7 ልዩ ቦታው ለገሀር ተብሎ ከሚጠራው አካባቢ ነው፡፡

ከሸዋ ሮቢት ተነስቶ መዳረሻውን አዲስ አበባ መሳለሚያ ሊያደርግ የነበረው ኮድ 3 A 21299 አ/አ አይሱዙ ተሽከርካሪ በተሽከርካሪው መፍቻ ማስቀመጫ የብረት ሳጥን በኩል ሻግ በማሰራት ሶስት መትረየሥ ጠብ-መንጃ ከመሰል አንድ ጥይትና ባዶ የጥይት ማስቀመጫ ዝናር ጋር ጭኖ ተገኝቷል፡፡

የብሄራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት ከአዲስ አበባ ፖሊስ ጋር በመቀናጀት ባደረገው ብርቱ ክትትል ህገ-ወጥ የጦር መሳሪያው፣ ተሽከርካሪው እንዲሁም 2 ተጠርጣሪዎችን ይዞ አስፈላጊውን ምርመራ እያጣራ መሆኑን የአዲስ አበባ ፖሊስ ገልጿል፡፡

በተመሳሳይ በአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ ወረዳ 7 ልዩ ቦታው መሳለሚያ እህል በረንዳ ተብሎ በሚጠራው አካባቢ በኮድ 1 34301 አ/አ ላዳ ታክሲ በማዳበሪያ ተፈታቶ የተቀመጠ 1 ኤስኬኤስ ህገ-ወጥ የጦር መሳሪያ ሲያዘዋውር የነበረ አሽከርካሪ ተይዞ ምርመራ እየተጣራ መሆኑን አስታውቋል፡፡

ህገ-ወጥ የጦር መሳሪያ በሀገርና በህዝብ ላይ የሚያደረሰውን ጉዳት በመገንዘብ ህብረተሰቡ አጠራጣሪ ነገሮች ሲመለከት ለህግ አካላት እንዲጠቁም የአዲስ አበባ ፖሊስ ጥሪ አቅርቧል፡፡

Exit mobile version