Site icon ETHIO12.COM

ዐቃቤ ህግ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ተገን በማድረግ የሙስና ወንጀል በፈፀሙ የፖሊስ አባላት ላይ ክስ መሰረተ

ዐቃቤ ህግ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ተገን በማድረግ የሙስና ወንጀል በፈፀሙ ሶስት የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን አባላት ላይ ክስ መሰረተ

ዐቃቤ ህግ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ተገን በማድረግ ስልጣንን አላግባብ በመገልገል የሙስና ወንጀል የፈፀሙ ሶስት የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን አባላት ላይ ክስ መስርቷል ።

የዐቃቤ ህግ የክስ መዝገብ እንደሚያስረዳው 1ኛ ተከሳሽ ኮንስታብል ተሰማ መለሰ በዲስፕሊን ጥፋት ከስራ የተሰናበተ 2ኛ ተከሳሽ ዋ/ሳጅን ፈንቴ ፈይሳ የፖሊስ መኪና ሾፌር 3ኛ ተከሳሽ ረ/ሳጅን ተስፋዬ በላይ የፖሊስ መኪና ተወርዋሪ ሲሆኑ የወንጀል ህግ አንቀፅ 32(1)(ሀ) ፣ (ለ) እና የሙስና ወንጀሎችን ለመደንገግ የወጣውን አዋጅ ቁጥር 881/2007 አንቀፅ 9(2)ስር የተመለከቱትን ድንጋጌዎች በመተላለፍ የሙስና ወንጀል ፈጽመዋል ሲል ነው ክስ ሊመሰርትባቸው የቻለው፡፡

ዐቃቤ ሕግ በክሱ ተከሳሾች የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ተገን በማድረግ ተገቢ ያልሆነ ብልጽግና ለማግኘት በማሰብና በጥቅም በመመሳጠር ህዳር 03/2014 ዓ/ም ከጠዋቱ ከ12፡30 እስከ 1፡00 ባለው ጊዜ ውስጥ በኮልፌ ቀራንዩ ክፍለ ከተማ ኪዳነ ምህረት ቤተክርስቲያን አካባቢ የሰሌዳ ቁጥር 0228 በሆነችና 2ኛ ተከሳሽ በሚያሽከረክራት የፖሊስ መኪና የግል ተበዳይ አቶ ዘሪሁን ሀይሉ ወደሚኖርበት መኖሪያ ቤት በመሄድ 1ኛ ተከሳሽ የፖሊስ አባል በመምሰል 2ኛ እና 3ኛ ተከሳሾች ደግሞ የፖሊስ አባልነታቸውን ሽፋን በማድረግ ምርመራ የማከናወንና የግል ተበዳይን የመያዝ የስራ ድርሻ ሳይኖራቸው እና ምንም አይነት ትዕዛዝ ሳይሰጣቸው 2ኛ ተከሳሽ የግል ተበዳይን “በወቅታዊ ጉዳይ ትፈለጋለህ” በማለት 1ኛ እና 3ኛ ተከሳሾች ወደ ግል ተበዳይ መኪና በመግባት 1ኛ ተከሳሽ ተበዳይን ያለምንም ጥያቄ 6 ወር ትታሰራለህ እኛ እንድንተባበርህ ከፈለክ ሁለት መቶ ሺ ብር ስጠን ብለው በመጠየቅና በመጨረሻም በአንድ መቶ ሃያ ሺ ብር እንዲሰጣቸው ተስማምተው ስልሳ ሺ ብሩን 1ኛ ተከሳሽ ወደሚጠቀምበት በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በሞባይል ባንኪንግ ገቢ እንዲያርግ በማድረግ እና አስር ሺ ብር በጥሬው በ1ኛ ተከሳሽ አማካኝነት ተቀብለው ከተከፋፈሉ በኋላ ቀሪውን ገንዘብ ሊቀበሉ ሲሉ በማህበረሰቡና በህግ አስከባሪ አካላት የተያዙ በመሆኑ ሀገሪቱ ካለችበት ወቅታዊ የጦርነት ሁኔታ አንፃር ተከሳሾች ከሚጠቅባቸው የዜግነት፣ ህገመንግስታዊ እና ሙያዊ ግዴታ ተቃራኒ በሆነ መንገድ ከሀገር ጥቅም ይልቅ የግል ጥቅምን በማስቀደም በፈፀሙት ስልጣንን አላግባብ መገልገል የሙስና ወንጀል በፍትህ ሚኒስቴር የሙስና ወንጀሎች ዐቃቤ ህግ ክስ ተመስርቶባቸዋል።

በዛሬው ዕለትም ተከሳሾች በፌዴራሉ ከፍተኛ ፍ/ቤት ልደታ ምደብ 4ኛ የሙስና ወንጀሎች ችሎት ቀርበው ክሱ እንዲደርሳቸው ተደርጓል።

በዚህም መሰረት ፍርድ ቤቱ ተከሳሾች ከተከላካይ ጠቦቆችቻው ጋር ተመካከረው በክሱ ላይ የክስ መቃወሚያ ካላቸውም ይህን ለመጠባበቅ ለታህሳስ 26/2014 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል።

ዐቃቤ ህግ ከዚህ በፊት ታህሳስ 04/2014 ዓ.ም ተመሳሳይ ወንጀል በፈፀሙ አራት የፌደራል ፖሊስ አባላት ላይ ክስ መስርቶ ተከሳሾች ባቀረቡት የክስ መቃወሚያ ላይ መልስ በመስጠት የችሎቱን ብይን ለመስማት ተለዋጭ ቀጠሮ መሰጠቱ የሚታወስ ነው።

Exit mobile version