Site icon ETHIO12.COM

«የሰብአዊነት ዘበኛ ፍትህ ነው» ዶ/ር በድሉ ዋቅጅራ

መንግስት ያደረገውን ይቅርታና ምህረት (የክስ ማቋረጥ ብለው የፍትህ ሚኒስትሩ አስተካክለውታል) ጉዳይ፤
(

ይህንን ጽሁፍ የዛሬ ሁለት አመት ገደማ ዴስትኒ ኢትዮጵያ በሚባል ያላፈራ ሀገራዊ ውይይት ላይ ስሳተፍ፣ ካናዳዊው የውይይቱ አስተናባሪ በነገሩን ቁም ነገር ልጀምር፡፡ ሰውየው በሜክሲኮ ባካሄዱት ውይይት ላይ የሀገሪቱ ፕሬዚዳት ተሳታፊ ነበሩ፡፡ ታዲያ የመጀመሪያው ቀን አዳራሽ ሲገቡ የሀገሪቱን ዋና ተቃዋሚ ድርጅት መሪ በመመልከታቸው አዳራሹን ጥለው ይመጣሉ፡፡ ሰውየውም ይከተላቸውና፣
‹‹ምነው? ተመለሱ?›› ይጠይቃቸዋል፡፡
‹‹ያንን ሰውዬ ታውቀዋለህ?›› በቁጣ ፕሬዚዳንቱ፡፡
‹‹አዎ፡፡››
‹‹አምስት ጊዜ የመግደል ሙከራ አድርጎብኛል፡፡ ከዚህ ሰውዬ ጋር ለምንድነው የምነጋገረው?››
‹‹ስድስተኛውን የመግደል ሙከራ ለማስቀረት፡፡›› ብሎ ይመልስላቸዋል፡፡
ወደ አዳራሹ ይመለሳሉ፡፡ ከውይይቱ መጨረሻ ፕሬዚዳንቱ አምስት ጊዜ የመግደል ሙከራ ያደረገባቸውን ሰው ምክትላቸው አድርገው ሜክሲኮን መምራት ጀመሩ፡፡

በዚህ እውነት የጀመርኩትበት ምክንያት ግልጽ ይመስለኛል፡፡ ኢትዮጵያ አገር አቀፍ የእርቅና የምክክር ኮሚሽን ስታቋቁም ውጤታማ ይሆን ዘንድ የፖለቲካ ፓርቲ መሪዎችና የፖለቲካ እስረኞች ከእስር ተለቀው ተሳታፊ እንዲሆኑ፣ ማንኛውም ፖለቲካዊና ሀገራዊ አስተሳሰብ ለምክክር እንደሚቀርብ የሚጠበቅ ነው፡፡ ከዚህ አንጻር በጁሀር መሀመድና በእስክንድር ነጋ መዝገብ የተከሰሱ ተጠርጣሪዎች መፈታት የሚጠበቅ ነው፡፡ ሀሳባቸውን ወደድነውም ጠላነውም፣ የምክክር ጉባኤው ውጤት አዎንታዊም ሆነ አሉታዊ ተሳትፏቸው የሚጠበቅ ነው፡፡

በመከላከያ ሰራዊታችንን በክህደት የጨፈጨፉና በጦር ሜዳ በከባድ መስዋእትነት የተማረኩትን እነ ስብሀት ከእስር መፈታት፣ የፍትህ ሚንስትሩ በምክንያትነት ያቀረቡት ‹‹ሰብአዊነት››ና የጤንነት ሁኔታ ግን፣ በእኔ አመለካከት ትረጉም የለሽና በሰብአዊነት ላይ ማሾፍ ነው፡፡ በሁለተኛው የአለም ጦርነት ወንጀል የፈጸሙ ወንጀለኞች ከግማሽ ምእተ አመት በኋላ፣ በ80 እና 90 አመታቸው በተሰደዱበት ሀገር፣ ሞታቸውን ከሚሚያጣጥሩበት አልጋ እየታደኑ ፍትህ ፊት የሚቀርቡት ስለሰብአዊነት ሲባል ነው፡፡ የሰብአዊነት ዘበኛ ፍትህ ነው፡፡ በሰብአዊነት ላይ በሰራው ወንጀል በአሸባሪነት የተከሰሰውን ትህነግ መስርተው እዚህ ያደረሱትን እነስብሀት ነጋን በሰብአዊነት ስም ከፍትህ ከለላ መስጠት ይቅርና ሰብአዊነትን ከስማቸው ጋር በአዎታዊ ትርጉሙ አያይዞ መጥራት በሰብአዊነት ላይ ከማሾፍ የዘለለ ትርጉም ሊኖረው ይችላል የሚል ግምት የለኝም፡፡

በመሆኑም፣ የነስብሀት መፈታት ከምንግዜውም በላይ እንደችቦ በአንድነት ታስሮ፣ እንደብረት ጠንክሮ በቆመበት በዚህ ወቅት፣ ኢትዮጵያዊ የሚከፋፍልና ከወዲሁ ሀገራዊ የምክክር ሸንጎው ላይ ሊያጠላ የሚችል በመሆኑ፣ መንግስት ውሳኔውን ደግሞ ሊያጤነውና ጠንካራ ማብራሪያ ሊሰጥበት ይገባል፡፡

Exit mobile version