Site icon ETHIO12.COM

በሳምንት ሶስት ቀናት በኦሮሚያ ባለስልጣኖች የህዝብ ጥያቄ አድምጠው ምላሽ እንዲሰጡ ታዘዘ፤ተቆጣጣሪ ግብረሃይል ይመደባል

የኦሮሚያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት በየደረጃው ያሉ አመራሮች በሣምንት ለሦስት ቀናት ማለትም ሰኞ፣ ረቡዕ እና አርብ የህዝቡን ጥያቄ እንዲያዳምጡ እና የሚጠበቅባቸውን አገልግሎት በአግባቡ እንዲሰጡ ውሳኔ ማሳለፉ ተገለጸ፡፡

የኦሮሚያ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት በመግለጫው÷ ህዝቡ አገልግሎት የሚያገኘው ለምኖ ሳይሆን እኛ አመራሮች የህዝቡ አገልጋይ ሆነን ስለተወከልን እና የአገልግሎት ጥያቄውን የመመለስ ሃላፊነት ስላለብን ነው ብሏል፡፡

ስለሆነም ማንኛውም አመራር በሚቀርብለት ጥያቄ መሠረት አገልግሎት ለመስጠት መሥራት ይጠበቅበታል ነው ያለው፡፡

መግለጫው ÷ የኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት በህዝብ የተወከለው ለህዝብ ቃል በገባው መሠረት የሕዝቡን ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ማኅበራዊ ጥያቄዎች ለመመለስ በመሆኑ ለተወከለበት ሥልጣን ሃላፊነት ወስዶ ይሰራልም ብሏል፡፡

እውነተኛ ዲሞክራሲያዊ ስርዓት ለመገንባት፣ ፍትሃዊ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ እና ሁሉንም ማኅበረሰብ ያሳተፈ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን እውን ለማድረግ ክልሉ እንደሚሰራም መግለጫው አመላክቷል፡፡

ባለፉት ሦስት ዓመታትም የተጀመሩትን ኢኮኖሚያዊ፣ ማኅበራዊ እና ፖለቲካዊ ለውጦች እንዲሁም የታለሙትን እቅዶች ለማጠናከርና በአጭር ጊዜ የኅብረተሰቡን ተጠቃሚነት ለማሳደግም ከአመራሮች ብዙ እንደሚጠበቅ ተመልክቷል፡፡

በኦሮሚያ ክልል የመንግስት አገልግሎት ሰጪ ተቋማት የህዝቡን የእድገት ደረጃ የሚመጥን አገልግሎት በመስጠት በኩል ሰፊ ክፍተት እንዳለባቸው መገምገሙንም መግለጫው ጠቆሞ፥ በቀጣይ የህዝቡን ቅሬታ ለመፍታት ወስኖ ለመስራት ቃል መግባቱንም መግለጫው አመላክቷል፡፡

መንግስት የህዝብ አገልጋይ እንደመሆኑ መጠን ፣ ከመንግስት እምነት ወስደው የህዝብ አገልጋይ የሆኑ አንዳንድ አመራሮችና ባለሙያዎች ለአገልግሎት ፈላጊው ህዝብ ትልቅ መሰናክል ሆነው መቆየታቸውንም መገምገሙን ክልላዊ መንግስቱ በመግለጫው ጠቅሷል።

በቀጣይም በሁሉም የመንግስት ቅርንጫፎች የአገልግሎት አሰጣጥ ችግሮችን የሚከታተሉ የግብረ ሃይል ኮሚቴዎች ከዞኖችና ከተማዎች ተውጣጥተው ተቋቁመው ወደ ሥራ እንደሚገቡም ነው ያሳወቀው፡፡

በዚህም መሰረት ከክልል እስከ ወረዳ ያሉ አመራሮችም ዘወትር ሰኞ፣ ረቡዕ እና አርብ በቢሯቸው ተገኝተው የህዝቡን ጥያቄ ማዳመጥና ተገቢውን አገልግሎት መስጠት እንደሚጠበቅባቸው ተወስኗል።

ውሳኔው ተግባራዊ እንዲሆን የህዝባችን ተሳትፎ ወሳኝ በመሆኑ መመሪያውን የሚጥሱ አመራሮችን ህዝቡ እንዲያጋልጥ ጥሪ ማቅረቡን የክልሉ ኮሙኒኬሽን ቢሮ አሳውቋል፡፡

Exit mobile version