Site icon ETHIO12.COM

በቻይና ሄሮይን አሲዛ ናዝራዊት አበራን ያሳሰረችው ስምረት ካህሳይ ተሰወረች – ዛሬ ተፈረደባት

ናዝራዊት አበራ በቻይና ሀገር ያለአግባብ ከዕፅ ዝውውር ጋር በተያያዘ እንድትከሰስና ለእስራት እንድትዳረግ ያረገቻት ጓደኛዋ ላይ የቅጣት ዉሳኔ ተላለፈባት

ስምረት ካህሳይ አንተሀቡ የተባለቸው ተከሳሽ የወንጀል ህግ አንቀፅ 32(1)(ሐ) እና 525(1)(ለ) ስር የተመለከተውን በመተላለፍ ተከሳሽ ልዩ ፍቃድ ሳይኖራት ህዳር 2011 ዓ.ም ወደ ሀገር ያስገባችውን 5 / አምስት / በሻምፖ እቃ የታሸገ ኮኬን ዕፅ ተበዳይ ናዝራዊት አበራ የተባለች ጓደኛዋን ወደ ቻይና ሀገር አብረን እንሂድ ብላ በማግባባት ቪዛ እና የአየር ትኬት ካስጨረሰች በኋላ ታህሳስ 11/2011 ዓ.ም ለናዝራዊት አበራ የሂውማን ሄር ማጠቢያ ነው ቻይና ውሰጅልኝ ብላ ከላከቻት በኋላ እርሷግን የአባቷን ሞት ምክንያት በማድረግ ትቀራለች፡፡

ተበዳይ ናዝራዊት አበራም ቻይና ሀገር ደርሳ አውሮፕላን ማረፊያ በተደረገባት ፍተሻ የያዘችው 5 /አምስት ሻምፖ መሰል 5 ኪ.ግ የሚመዝን የኮኬን ዕፅ መሆኑ ተደርሶበት ለእስር አንድትዳረግ ያደረገች በመሆኑ ተከሳሽ ሁኔታውን ያልተገነዘበችን ሰው በመጠቀም በፈፀመችው መርዛማ ወይም የናርኮቲክና ሳይኮትሮፒክ እፆችን ወደ ውጭ ሀገር መላክ ወይም ማዘዋወር ወንጀል በዐቃቤ ህግ ክስ ተመስርቶባታል፡፡

በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ወንጀል ችሎት ተከሳሽ ቀርባና ክሱ ተነቦላት “በዐቃቤ ህግ የተመሰረተብኝን ክስ ተረድቸዋለሁ በተመሰረተብኝ ክስ ግን ጥፋተኛ አይደለሁም ምክንያቱም ለጓደኛዬ ለናዝራዊት አበራ የሰጠኋት የኮኬን ዕፅ ሳይሆን የፀጉር መታጠቢያ ሻምፖ ነው በዚህም ጥፋተኛ አይደለሁም” ስትል የእምነት ክህደት ቃሏን ሰጥታለች።

ዐቃቤ ህግ በበኩሉ የተከሳሽን ጥፋተኝነት የሚያስረዱ 8 (ስምንት) የሰው፣ ከኢ.ፌ.ዲ.ሪ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴርና ከኢሜግሬሽን ዜግነትና የወሳኝ ኩነት ኤጄንሲ የተገኙ ዝርዝር የሰነድ ማስረጃዎችን በማቅረብ ያሰማ ሲሆን ይህ ስጋት የገባት ስምረት ካህሳይም የማስረጃውን ሁኔታ ጥፋተኝነቷን በጉልህ ማሳየቱን ስትረዳ የሚቀጥለውን ቀጠሮ በመፍራት ከቅጣት እንደማታመልጥ ሲገባት ለጊዜው ተሰውራለች።

በከሳሽ ዐቃቤ ህግና በተከሳሽ ስምረት ካህሳይ መካከል የተደረገውን ክርክር ሲያዳምጥ የቆየው የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ወንጀል ችሎትም ዐቃቤ ህግ ባቀረበው ክስ እና ማስረጃ መሰረት ተከሳሽ ጥፋተኛ መሆኗ በበቂ ሁኔታ የተረጋገጠ በመሆኑ በተከሳሽ ስምረት ካህሳይ ላይ የጥፋተኝነት ፍርድ በመሰጠት የካቲት 25/2014 ዓ/ም በዋለው ችሎት ተከሳሽ በ15 ዓመት እስራትና በ1 መቶ ሺህ ብር የገንዘብ ቅጣት እንድትቀጣ ወስኗል፡፡

የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ኢሚግሬሽን ዜግነት የወሳኝ ኩነት ኤጄንሲ ተከሳሽ ስምረት ካህሳይን ወደ ውጭ ሀገር ስትወጣ ወይም ወደ ሀገር ውስጥ ስትገባ ተከታትሎ በመድረስ ለፌደራል ፖሊስ አሳልፎ እንዲሰጥና የፌደራል ፖሊስም ተከሳሿን አፈላልጎ ለማረሚያ ቤት እንዲያስረክብ ትዕዛዝ በመስጠት መዝገቡን ዘግቷል።

ማስታወሻ፡- ተከሳሽ ስምረት ካህሳይ ያለችበትን የሚያውቅ ማንኛውም ሰው ከፍትህ ጎን በመቆም ለፌዴራል ፖሊስ ጥቆማ እንደያደርግ እያሳሰብን ሳምራዊት አበራን በማስመልከት የፍትህ ሚኒስትር በህግ ጉዳዮች አለምአቀፍ ትብብር ዳይሬክቶሬት ሳምራዊትን ጨምሮ በሁለት በቻይና ማረሚያ ቤቶች የሚገኙ ኢትዮጵያውያን የአሳልፎ መስጠት ጥያቄ አቅርቦ ምላሹን በመጠባበቅ ላይ ይገኛል

Exit mobile version