Site icon ETHIO12.COM

ወልቃይት: ቢመረንም ለመዋጥና ራሳችንን ለመመልከት እንሞክር

ዶ/ር አብይ አህመድ በተለያዩ መድረኮች ወልቃይት የበጌምድር አማራ መሆኑን በማያሻማ መንገድ በጠራ አገላለፅ ባረጋገጠበት መንገድ (የጠቅላይ ሚኒስትሩ ንግግር ፊርማ ነው)፤ ወልቃይት በአማራ ክልል መንግስት ስር እየተዳደረ ባለበት ሁኔታ፤ ወልቃይትን አብይ አህመድ ለወያኔ አሳልፎ ሊሰጥ ስለሆነ አማራ ከመከዳትህ በፊት ተነስ የሚሉ የግጭት ነጋዴዎች ድምፅ ማሰማት ሳይሆን ለእነሱ ጆሮ የሚሰጠው ሰው ቁጥር በዚህ ደረጃ መጠኑ መጨመሩ የሚያስደንቅና የሚያሳስብም ነው። እርግጥ ነው ጉዳዩ የማንም ሳይሆን የራሱ የመንግስት የPR ችግር የፈጠረው ነው።

ዶ/ር አብይ አህመድ ለአማራ እንቆረቆራለን ወይም እንታገላለን ከሚሉት በላይ በወልቃይት ጉዳይ የሕዝቡን የዓመታት ጥያቄና ትግል እውቅና ሰጥቶ ወልቃይት የበጌምድር አማራ መሆኑን የጠራ አቋሙን በአደባባይ አረጋግጦ ለሕዝቡ ጥያቄ የራቀ ሳይሆን መቅረቡን ያስመሰከረበትን ጉዳይ ጠላት ወያኔ ግን ወልቃይት እንዳይመለስ ወይም ለወያኔ ተላልፎ እንዲሰጥ አብይ እየሰራ እንደሆነ አድርጎ መንጋ የሚያደናግርበት ወይም በመንጋ እንዲከሰስ ዕድል የፈጠረበት ሁኔታ የጠላትን ጥንካሬ ሳይሆን የራሱ የመንግስት የመረጃ አሰጣጥ የሕዝብ ግንኙነት ድክመትን የሚያሳይ ነው።

የመላው አማራ ሕዝብ ከዳር እስከ ዳር በነቂስ ወጥቶ ወልቃይትን ብሎ ብዙ መከራና ግፍን የተቀበለበትን ጥያቄና ትግል ከሆነው አንዱ የወልቃይት ጉዳይ በዚህ ሰዓት በእጁ መዳፍ ይገኛል።

ስለወልቃይት በሕግ የቀሪውን ጉዳይ የማረጋገጥ ስራ በአማራ ክልል መንግስት እና የአማራ ኤሊት ነኝ በሚለው አካል ትክሻ ላይ የሚወድቅ ይሆናል። አብይ አህመድ እስካሁን ከተናገረው ወይም ካደረገው በላይ በዚህ ዙሪያ የሚጠበቅበት ግዴታ እንዳለበት በበኩሌ በፍፁም አይሰማኝም። ወልቃይት የበጌምድር አማራ ነው ከማለት በላይና በአማራ ክልል መንግስት ስር እንዲተዳደር ከማድረግ፣ ለቀጣይ ሂደቱን ነገሮችን ከማመቻቸት ያለፈ ከእሱ የሚጠበቅበት ነገር የለም። ከዛ ውጭ አብይ አህመድ መንደር ለመንደር ወይም ከክልል ክልል እየዞረ የወልቃይትን ጉዳይ ወረቀት ይዞ ሊያስፈፀም አይችልም። ፖስተኛም አይደለም። ማንም እጅና እግሩን አጣጥፎ ተጎልቶ ጊዜውን የሚቆጥር አብይ አህመድ ሁሉንም ነገር ፈትፍቶ እንዲያጎርሰው የሚፈልግ የጠባቂነት መንፈስ የተጠናወተው ሁሉ እጁ ላይ የገባውን ወልቃይትን ሊነጥቁኝ ነው ወይም ተላልፎ ሊሰጥብኝ እያለ ሲነፋረቅ ቢታይ ድክመቱን ከማሳየት ነውሩን ከመግለጥ ያለፈ ትርጉም ያለው ነገር ማሳየት አይችልም።

እርግጥ ነው በሰሜን ሕብረት በስመ የአቢሲኒያ አሻራን የደቡቡ ሐይል ሊንደውና ሊያጠፋው ነው በሚል የወያኔ አጀንዳን በማራገብ ከወያኔ ጋር አብረን ከቆምን ባርጌኒግ ፓወራችን ይጨምራል አብይ አህመድንም ከስልጣኑ ማስወገድ ይቻላል እያለ የሚንቀሳቀስ አካል መልሶ በመሃል የወልቃይት ጉዳይን አስመልክቶ በተቆርቋሪነት ለመንቀሳቀስ ሲሞክር መታየቱ ተጠባቂ እንጅ አዲስ ነገር አይሆንም። በዚህ ማዕቀፍ ውስጥ የሚንቀሳቀሱ ጥላቻ የወለዳቸው በስሜት ፈረስ የሚጋልቡ የወያኔ የማደጎ ልጆች ለአላማቸው መሳካት እንደፈለጉ ሲገለባበጡ ሚግ 23 የሚያስንቁ ናቸው። በቀጣይ በየት በኩል ተገልብጠው ሊከሰቱ እንደሚችሉ መገመትም አይቻልም።

እነዚህ አካላት ዶ/ር አብይ አህመድን እንደ አንድ የሕወሓት ስራ አስፈፃሚ እኩል ነጥለው እያብጠለጠሉ ከስልጣኑ እናስወግደዋለን ብለው እየተንቀሳቀሱ መልሰው የአማራ ጥያቄ እየተመለሰ አይደለም ሲሉ፤ ወልቃይት በአብይ አህመድ ተላልፎ ሊሰጥ ነው የሚል ጩኸትም ሲያሰሙ መመልከት የሚያረጋግጥልን ጉዳይ የሞራል ቫልዩና መርህ አልባ መሆናቸውን ነው።

በመጨረሻም

ለአማራ ሕዝብ እንቆረቆራለን የምንል ሰዎች ቅድሚያ እራሳችንን እንመልከት። ከዛም ከራሳችን ጋር ሆነን የራሳችንን አጀንዳ ቀርፀን ለአማራ ሕዝብ ሁለንተናዊ ጥቅም መረጋገጥ ደፋ ቀና ለማለት ሙከራ እናድርግ። አለበለዚያ በተመለደው በጠላት አጀንዳ በስማ በለው ስንወራጭ፣ አካኪ ዘራፍ እያልን ስንፏልል፣ ውለን ብናነጋ በውጤቱ ከአንዱም ሳንሆን እንደዳከርንና አረፋችንን እንደደፈቅን አወዳደቃችንን አበላሽተን ከመውደቅ ከፍ ያለ ድል ልንነሳው የምንችለው ጠላት አይኖረንም። ከጅምሩ የተከተልነው መስመር በእኛ የተነደፈ ወይም በእኛ የቀየሰ መንገድ አይደለምና። ስለሆነም የጠላት አጀንዳን ተሸክመን በጠላት መንገድ እየተመላለስን ጠላትን ለማሸነፍ ማሰብ የሞኝነታችንን ጥግና የአወዳደቃችንን ሁኔታ ከማሳየት ያለፈ አሸናፊነታችን አያረጋግጥም።

ቶማስ ጀጃው ሞላ

Exit mobile version