Site icon ETHIO12.COM

እያንዳንዱ ዞን ራሱን የቻለ ክልል ማድረግ ….

“አጠቃላይ መፍትሄ እስኪገኝ ድረስ እያንዳንዱ ዞን ራሱን የቻለ ክልል ከማድረግ የተሻለ የሰላም አማራጭ ያለ አይመስለኝ።”

[ ዶ/ር ታደሰ ብሩ | Jun 2020 … በከፊል የተወሰደ ]

By – Bella Daniel

በሚቀጥሉት ጥቂት ዓመታት የኢትዮጵያን የሀገር ውስጥ ደህንነት በከፍተኛ ሁኔታ የሚወስኑት ትግራይ፣ ደቡብ እና አዲስ አበባ ይሆናሉ።
የደቡብ ክልል ቅራኔ በሲዳማ ራሱን ችሎ ክልል መሆን የሚጠናቀቅ አይሆንም። የሲዳማ ዞን ክልል መሆን ተቀባይነት አግኝቶ ለሌሎች ጥያቄ ላነሱ ዞኖች ይህንን መብት መንፈግ ለተጨማሪ ቅራኔዎች በር መክፈት ነው።
ሶስትና አራት ዞኖችን በግድ አጠጋግቶ መሸንሸን ደግሞ ለበርካታ አዳዲስ ቅራኔዎች ምቹ ሁኔታ መፍጠር ነው። አዳዲሶቹ ቅራኔዎች ከቀድሞዎቹ የባሱ የመሆን እድላቸው ከፍተኛ ነው። በሚቀራረቡ ማኅበረሰቦች መካከል የሚነሱ ቅራኔዎች ይበልጥ አውዳሚ እንደሆኑ ልብ ማለት ይገባል። ደቡብ የፌደራል አወቃቀሩ ችግር ገዝፎ የሚታይበት ክልል ሆኖ መቀጠሉ አይቀርም።

አጠቃላይ መፍትሄ እስኪገኝ ድረስ እያንዳንዱን ዞን ራሱን የቻለ ክልል ከማድረግ የተሻለ የሰላም አማራጭ ያለ አይመስለኝ።

የሃይል ሚዛን 🌀
ወደ ተቃዋሚ ካጋደለ ለውጥ ይቀለበሳል!
“የዶ/ር አቢይ መንግሥት ለለውጥ ኃይሎች ሚዛን ተገቢውን ትኩረት የሚሰጥ ስለመሆኑ በበኩሌ እርግጠኛ መሆን አልቻልኩም።”
[ ዶ/ር ታደሰ ብሩ ]
አንድ ለውጥ ስኬታማ እንዲሆን ከሚያስፈልጉ ነገሮች አንዱ በለውጡ ደጋፊዎች እና በለውጡ ተፃራሪዎች መካከል ያለው የኃይል ሚዛን ነው።
የኃይል ሚዛን ወደ ደጋፊዎች ያደላ ካልሆነ ለውጥ ሊቀለበስ ወይም መስመሩን ሊስት ይችላል። የለውጥ መሪዎች አንዱ ተግባር ይህን የኃይል ሚዛን በአንክሮ መከታተልና የደጋፊዎች ኃይል ብልጫ ያለው መሆኑን ማረጋገጥ፤ ሚዛኑ በተዛባ ወቅት አስፈላጊውን እርምጃ በመውሰድ ማስተካከል ነው። ”ኃይል“ ሲባል የወታደር ወይም የፖሊስ ኃይል ማለት አይደለም። በለውጥ አመራር የኃይል መመዘዘኛዎች በርካታ ቢሆኑም አንዱና ዋነኛው የተከታዮች ጥራትና ብዛት ነው።
የለውጥ ተቃዋሚዎችን ኃይል ለማዳከም ከሚነደፉ ስልቶች አንዱ – ምናባትም ዋኛው የለውጡን ተቃዋሚዎች ንቁ ተከታዮች እንዳይኖሯቸው ማድረግ ነው።
ይህን ተግባራዊ ለማድረግ የሚረዱ በርካታ ስልቶች ሊኖሩ ይችላሉ። ለምሳሌ፤ የለውጥ ተቃዋሚ መሪዎች ንቁ ተከታይ አልባ እንዲሆኑ ተከታዮቻቸውን ማቅረብና የለውጡ ሂደት ሙሉ ተሳታፊ እንዲሆኑ ማድረግ፤ ተቃዋሚ መሪዎችን ለሚከዱ ንቁ ተከታዮች ዋስትና መስጠት፤ በለውጡ ደጋፊዎችና ተቃዋሚዎች መካከል ተጨማሪ ቅራኔዎች እንዳይፈጠሩ ቀዳዳዎችን መድፈን።
የለውጥ ደጋፊዎችን ኃይል ለማጠናከርም እንደዚሁ በርካታ አማራጭ ስልቶች አሉ። ለምሳሌ፤ በለውጥ ደጋፊዎች መካከል “ወፍራም” መተማመን እንዲኖር መጣር፤ ወዳጅነቶች ተቋማዊ መሠረት እንዲኖራቸው ማድረግ፤ የለውጡ ደጋፊዎች የለውጡ ባለቤት እንዲሆኑ ማድረግና ይህን በቃላት ብቻ ሳይሆን በተግባር መፈፀም፤ የለውጡ ደጋፊዎች ኅብረት በየጊዜው እየሰፋ እንዲሄድ ማድረግ።
የዶ/ር አቢይ አህመድ መንግሥት ለለውጥ ኃይሎች ሚዛን ተገቢውን ትኩረት የሚሰጥ ስለመሆኑ በበኩሌ እርግጠኛ መሆን አልቻልኩም።
የለውጡ ተቃዋሚዎች እየደረጁና የልብ ልብ እየተሰማቸው፤ ደጋፊዎቹ ደግሞ ቅር እየተሰኙ፣ ከዚያም አልፎ እያኮረፉ የመጡ ይመስለኛል። ይህ ለዶ/ር አቢይ መንግሥት ብቻ ሳይሆን ለኢትዮጵያም አደጋ ነው ብዬ አስባለሁ፤ የለውጥ ተስፋችንንም የሚያጨልም ውጤት ሊኖረው ይችላል የሚል ስጋት አለኝ።
ከዚህ አንፃር 2 ነጥቦችን ብቻ ለአብነት ያህል ላንሳ፦
1) አንዳንድ የህወሓት መሪዎች በግልፅ መናገር እንደጀመሩት ብአዴንን፣ ኦህዴድን እና ደኢህዴድን የሚተኩላቸው ተባባሪዎች እያገኙ መሆኑ ልብ ሊባል ይገባል።
🎯 ህወሓትን በትግራይ ውስጥም ከትግራይ ውጭም ለማዳከም ተከታዮችን ማሳጣት ይገባል። ለውጡ ለህወሓት ተከታዮች ስጋት መሆን የለበትም፤ እነሱም በለውጡ የሚጠቀሙ መሆኑን ማሳየት እና ራሳቸውን ከህወሓት እንዲነጥሉ ማበረታታት ይገባል። የህወሓት አዳዲስ ተከታዮችን የመመልመያ መንገዶችን መዝጋት ያስፈልጋል።
2) ደቡብ ክልል ላይ የሚሠራ ስትራቴጂያዊ ስህተት የለውጥ መሪዎችን በርካታ ወዳጆችን ሊያሳጣ ይችላል። በለውጥ ወቅት በሚሠራ ስህተት የቅርብ ወዳጅ እንኳን ወደ ጠላትነት ሊቀየር ይችላል።

🎯 ኢፍትሀዊ ውሳኔ ተሰጥቶኛል የሚል ሰፊ የኅብረተሰብ ክፍል የሚፈጠርበት የክልሎች ሽንሸና የዶ/ር አቢይ መንግሥትን በርካታ ደጋፊዎችን ያሳጣል የሚል ከፍተኛ ስጋት አለኝ። ይህ ውሳኔ ከኮቪድ ጋር ”በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ“ በመሆን የክልሉን ከዚያም አልፎ የአገራችንን ሰላም ከፍተኛ አደጋ ላይ ይጥላል የሚል ስጋት አለኝ።

“ፓለቲካችንን ከዘውግ ፓለቲካ ነፃ ማውጣት ካልቻልን የብዙ ሕዝብ እና የአገር መጥፊያ ሊሆን ይችላል።”
ትናንሽ ልዩነቶችን ማጉላት እና የዘውግ ፓለቲካ !

[ ዶ/ር ታደሰ ብሩ ]

የስነልቦና ተመራማሪው ስግመንድ ፍሬይድ “ትናንሽ ልዩነቶንች” በማጉላት ”እኔ ከሌሎች የተለየሁና የተሻልኩ ነኝ“ ማለት እና እነዚህ ትናንሽ ልዩነቶችን በመለጠጥ ቅራኔ ውስጥ መግባት (Narcissism of Minor Differences) ብሎ ጠራው።
Narcissus (ናርሲሰስ) ከራሱ ጋር ፍቅር የያዘው፤ ስለ ራሱ ያለው የተጋነነ እምነት መጥፊያው የሆነ የግሪክ አፈታሪክ ገፀ-ባህሪይ ነው። ናርሲሰስ ሌሎች ሰዎችና አማልዕክት እሱን የመውደድ ግዴታ ያለባቸው ይመስለው ስለነበር ለፍቅር እንኳን ያልተመቸ ገፀ-ባህርይ ነው። በዚህ የአፈታሪክ ገፀ-ባህሪ መነሻነት ከመጠን ያለፈ ራስ ወዳድነት ናርስሲዝም (narcissism) ተባለ።
Narcissism of Minor (Small) Differences ጎልቶ ከሚታይባቸው ቦታዎች ቀዳሚው የዘውግ (ethinic) ፓለቲካ ነው። የዘውግ ፓለቲከኛ የራሱን ዘውግ ከሌላው የሚለየውን ድንበር ለማበጀት፤ የሱ ዘውግ አባላት ከሌሎች የተሻሉ አስተዋይ፣ ቻይ፣ ታታሪ፣ ጀግና፣ ሩህሩህ ሆኖም ያለአግባብ እየተጠቁ ያለ ተበዳዮች አድርጎ ለማቅረብ Narcissism of Minor Differences ይጠቀማል። ጥቂት ምሳሌዎችን ላንሳ

  1. ሁቱና ቲትሲዎች አንድ ቋንቋ ይናገራሉ፤ ሁለቱም ክርስቲያኖች ናቸው። ለዘመናት ሲጋቡ ስለኖሩ የክልሶች ቁጥር ቀላል አይደለም። በቁመትና በቆዳ ፍካታቸው ያለውን ትንሽ ልዩነት በመጠቀም አንድ ሩዋንዳዊ ሁቱ ይሁን ቱትሲ መሆኑ መገመት ቢቻልም መቶ በመቶ እርግጠኛ መሆን አይቻልም። እርግጠኛ ለመሆን ብሔር የሚገልጽ ማስረጃ ያስፈልጋል ወይም ራሱን መጠየቅ ይገባል። በሁለቱ ቡድኖች መካከል የዚህንም ያህል መቀራረብ ቢኖርም እአአ በ1994 በአንድ መቶ ቀናት ውስጥ 800 000 ሰዎችን የፈጀ እልቂት ተፈጽሟል፤ ከዚህ ጦርነት ጋር በተያያዘ እስከ 2003 ድረስ በጠቅላላው 5 ሚሊዮን ያህል ሰው ሕይወቱን አጥቷል።
  2. በቆጵሮስ (Cyprus) ደሴት ውስጥ በሚኖሩ የግሪክ-ቆጽሮሳዊያን እና የቱርክ-ቆጽሮሳዊያን መካከል ያለው መመሳሰል የገረመው የቅራኔዎች ተመራማሪ የደሴቲቱ ነዋሪ የሆነ ረዳቱን “በምንድነው ማን ከየትኛው ወገን እንደሆነ የምትለዩት?” ብሎ ይጠይቀዋል። “ወንድሜ ብዙ ዓመት ስንፋጅ ስለቆየን እንተዋወቃለን፤ አንድ ቆጵሮሳዊ ሲጋራ ሲለኩስ በሚያጨሰው ሲጋራ የማን ወገን እንደሆነ ይታወቃል” አለው።
  3. ሰርቦች፣ ኮራቶች እና ቦስኒያዎች አንድ ቋንቋ ይናገራሉ። በአለባበሳቸው፣ በሙዚቃዎቻቸው፣ በባህል ምግቦቻቸው ጉልህ ልዩነት የለም። በ200 ዓመታት በፊት የነበሩ ቅም አያቶቻቸው በሀይማኖትም ይሁን በባህል ተለያይተው ነበር ይሆናል። በዩጎስላቪያ ጊዜ ለነበሩ ወጣቶች ልዩነቶቹ ከታሪክ ያለፈ ትርጉም አልነበራቸውም። ቀዝቃዛው ጦርነት ሲያበቃ ግን እነዚያ ሊረሱ የደረሱ ልዩነቶች ገዝፈው ለእልቂትና ለዩጎዝላቪያ መበታተን ምክንያት ሆኑ። ሚካኤል ኢግናቴቭ (Michael Ignatieff) አንድ ሰርብ የነገሩትን በጽሁፉ አስቀምጧል “ኮራቶች ከኛ የተሻሉ ይመስላቸዋል፤ ራሳቸውን ምርጥ አውሮፓውያን አድርገው ይመለከታሉ። ግን አንድ ነገር ልንገርህ፣ ሁላችንም የባልካን … ነን”
  4. ሶማሊያ ከአፍሪቃ አገሮች ሁሉ በብዙ ነገሮች የታደለች ናት። 3,333 ኪሜትሮች የባህር ጠረፍ አላት፤ ይህ በአህጉሩ ትልቁ የአንድ አገር የባህር ጠረፍ ነው። የባህር ክልሏ፤ በማዕድንና በአሳ ሀብት የበለፀገ ነው። ዜግነት (citizenship) እና ዘውግ (ethnicity) አንድ የሆነበት ብቸኛ አፍሪካዊት አገር ሶማሊያ ናት። መቶ በመቶ ማለት በሚቻል ሁኔታ ሁሉም የሶማሊያ ዜጋ የእስልምና እምነት ተከታይ ነው። ለጠብ ምክንያት የሌላት አፍሪካዊት አገር ማናት ተብለን ብንጠየቅ በጭንቅላታችን መምጣት ያለባት አገር ሶማሊያ ነች። ምድር ላይ ያለው ሀቅ ግን ሁላችንም የምናውቀው ነው። ለምን ይህ ሊሆን ቻለ? መልሱ Narcissism of Minor Differences ነው። የሶማሊያ ልሂቃን የጎሳ ልዩነትን በመጠን በላይ አግዝፈው ለእልቂት የሚያበቃ ምክንያት አደረጉት። አንድን ሶማሊን በማየት ብቻ ጎሳውን ማወቅ አይቻልም፤ ራሱን መጠየቅ ያስፈልጋል። ታድያ የሞት አደጋ የሚያስከትልበት ቢሆን እንኳን አብዛኛው ሶማሊ ጎሳውን አይደብቅም። ለምን ይህ ሆነ? መልሱ አሁን Narcissism of Minor Differences ነው። በብዙ አገሮች ትርጉም የማይሰጠው ጎሳ ሶማሊያ ውስጥ እጅግ … እጅግ ወሳኝ ነገር ተደረገ።
    ለኔ የንባቦቼ ሁሉ ማጠንጠኛዬ ኢትዮጵያዬ ነች። የኢትዮጵያ “ሶሻሊስት መንግሥት” ከኤርትራና ትግራይ አማጺያን ጋር ባደረገው ውጊያ የተሳተፈ በጊዜው የሶቪየት ኅብረት ወታደራዊ መኮንን የነበረ ዩክሬናዊ በኢትዮጵያ ቆይታው ስለነበረው ጥሩም መጥፎም ትዝታዎች አውርቶኛል። ከመጥፎ ትዝታዎቹ ዋነኛው ጠላትንና ወዳጅን መለየት በማይችልበት ውጊያ መሳተፉ ነው። “በምንም የማይለዩ ሰዎች እርስ በርስ ሲዋጉ አንዱን ወገን ረድቶ የጠቡ አካል መሆን ያሳፍራል፣ ያሳምማል። … ለእኛ የሚሊተሪ ዩኒፎርም የለበሰ እትዮጵያዊ ወዳጅ፤ ቁምጣ የለበሰና ጎፈሬያም ኢትዮጵያዊ ደግሞ ጠላት ነበር፤ ይህ ሁሌ ያሳፍረኛል” ነበር ያለኝ። ይህን ከነገረኝ ጥቂት ዓመታት በኋላ ኢትዮጵያ ውስጥ ገጥሞት የሰቀጠጠው የወንድማማቾች ጦርነት እሱም አገር ተከሰተ። እኔ ደግሞ ዛሬ ያለበት ሁኔታ እሱ በነበረት ወቅት ከነበረው ሁኔታ ጋር እያወዳደርኩ ሊመጣ የሚችለው አደጋ ያስፈራኛል።
    ዛሬ ትናንሽ ልዩነቶችን በማስፋት ሥራ ላይ የተጠመዱ ብዙ ሰዎች አሉን። በአሮሞ፣ በአማራ፣ በትግሬ፣ በጉራጌ … መካከል ስላሉ ልዩነቶች አግዝፈው የሚናገሩና የሚጽፉ፤ በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ እነሱ የኔ የሚሉት ወገን ምርጥነት የሚነግሩን “ምሁራን” መብዛታቸው እጅግ ያሳስበኛል። በአሮሞ ውስጥ በሜጫ፣ በቱለማ፣ በጉጂ፣ በቦረና፣ ፣ በከረዩ .. በአማራ ውስጥ በጎጃም፣ በጎንደር፣ በወሎ፣ በሸዋ ….. በጉራጌ ውስጥ በቸሀ፣ በቀቤና፣ በመስቃን፣ በማረቆ … መካከል ስላሉ ልዩነቶች አግዝፈው የሚናገሩ ሰዎች መብዛት እጅግ ያሳስበኛል።
    ደቡብ ክልል “በክላስተር” “መጠርነፍ” Narcissism of Minor Differences ያባብሳል የሚል ስጋት አለኝ። የዘውግ ፓለቲካን ከ Narcissism of Minor Differences መለየት ከባድ ነው። ፓለቲካችንን ከዘውግ ፓለቲካነት ነፃ ማውጣት ካልቻልን Narcissism of Minor Differences የብዙ ሕዝብና የአገር መጥፊያ ሊሆን ይችላል።
    ማጣቀሻዎች
    Blok, Anton (1998) The Narcissism of Minor Differences. European Journal of Social Theory 1 (1):33-56
    Brubaker, Rogers (2004) Ethnicity Without Groups. Cambridge, Mass.: Harvard University Press
    Ignatieff, Michael (1999) ’Nationalism and the narcissism of minor differences’ in Ronald Beiner, ed,. Theorizing Nationalism. State University of New York Press: 99-102
    Freud, Sigmund (1917) The Taboo of Virginity. Standard Edition, Hogarth Press, London 1953: 11: 191:208
    Freud, Sigmund (1921) Group psychology and the analysis of the ego. Standard Edition, 18 Hogarth Press, London 1953: 18:67-144
    Freud, Sigmund (1930) Civilization and its Discontents. Standard Edition, Hogarth Press, London 1953: 21: 191-208
    Volkan, Vamik D. (1986) The Narcissism of Minor Differences in the Psychological Gap Between Opposing Nations. Psychoanalytic Inquiry, 6:175-191
Exit mobile version