Site icon ETHIO12.COM

የፍፃሜዉ ጦርነት በወልቃይት-ጠገዴ ምድር!

ወያኔንና መሰሎቹን ፈረስ አድርገዉ አገራችንን ለማወክ እየሰሩ ያሉ የዉጭ ጠላቶቻችን እጃቸዉ ይቆረጣል። ከዚህም በላይ ወያኔ ሳይወድ በግድ በተሸናፊነት ስሜት ሁኖ ወደ ድርድር ይመጣል። መጨረሻ ላይ ይህ ሁኔታ በሂደት ወያኔን ከትግራይ ህዝብ ጫንቃ እስከወዳኛዉ ለማዉረድ እድል ይሰጣል። በአንፃሩ በዚህ የፍፃሜ ጦርነት ወያኔ ድል ካገኘ ነገሮች ሁሉ የተገላቢጦሽ ይሆናሉ። መጨረሻዉም የኢትዮጵያን መፍረስ ማስከተሉ አይቀርም።

በቹቹ አለባቸው ( አስተያየት)

በወያኔና በኢትዮጵያ ህዝብ/መንግስት መካከል እየተካሄደ ያለዉ ጦርነት በታሰበዉ የድርድር መንገድ ቢቋጭ የብዙዎቻችን ምኞት ነዉ። በዚህ በኩል በተለይም መንግስት እየወሰዳቸዉ ያሉ እርምጃዎች ችግሩን በሰላም ለመፍታት ፍላጎቱ እንዳለዉ መገንዘብ አይከብድም።

ይሁን እንጅ በተደጋጋሚ እንደምለዉ ይህ ጦርነት በሰላም የመቋጨት እድሉ እጅግ ጠባብ ነዉ። ይሄ ንን ጉዳይ ከወያኔ ባህሪና ወቅታዊ እንቅስቃሴዉ ተነስቶ ለመበየን ከባድ አይሆንም። ሁላችንም እንደምናዉቀዉ ዛሬ ላይ በትግራይ በተለይም ከ6ኛ ክፍል በላይ የሆኑ ት/ቤቶች ዝግ ናቸዉ። ይህ ማለት በ100 ሽህ የሚቆጠሩ ወጣቶች ተዋጊ ሁነዋል ማለት ነዉ። እዚህ ቁጥር ላይ በጉልምስና ዕድሜ ላይ የሚገኘዉን ትግራዋይ ቁጥር ደምሩበት። በድምሩ ሲታይ ወያኔ ገሚሱን የትግራይ ህዝብ ለጦርነት አሰልፎታል ማለት ነዉ።

አገራችን ኢትዮጵያ እና መንግስቷ የገባንበትን የርስበርስ ጦርነት በሰላማዊ መንገድ ለመቋጨት ብዙ እርቀት ተጉዘዉ እያለ፣ ወያኔ በዚህ ልክ ተዋጊ ጦር የሚያዘጋጀዉ ለምንድን ነዉ? የሚለዉ ጥያቄ ትኩረት ያስፈልገዋል። በተደጋጋሚ እንደምንለዉ ወያኔ ይህ ጦርነት በድርድር ይፈታል ብሎ አያምንም። ወያኔ ለድርድር ዝግጁ ነኝ የ ሚለዉ ለጊዜ መግዧና ለዲፕሎማሲ ፐርፐዝ ነዉ።

አሁን ጥያቄዉ ወያኔ ጦርነት እንደገና መለኮሱ የማይቀር ከሆነ የጦርነቱ ባህሪና አቅጣጫ ምን ሊሆን ይችላል? የሚለዉ ነዉ። የወያኔን የጦርነት ፍላጎት በዉል ለመረመረ ሰዉ የወያኔ ዋነኛ ፍላጎት አዲስ አበባ ዘልቆ የመንግስትን ስልጣን መቆጣጠር አይደለም። ይህ ማለት በለስ ከቀናዉ አያደርገዉም ማለት አይደለም። ይልቁንስ እኔ እንደማምነዉ የወያኔ ዋነኛ ግብ የሚሌን ወደብ መስመርና የወልቃይትን ኮሪደር በመቆጣጠር መንግስትን አሰገድዶ ፍላጎቱን ማስፈፀም ነዉ።

ወያኔ ባለፈዉ አመት የሚሌን እና የአዲስን ግንባር ሞክሮታል። አልተሳካለትም። ይልቁንስ የሚሌና አዲስ ግንባር ወያኔን ከባድ ዋጋ አሰከፍሎታል። ስለሆነም ይሄን ግንባር ዳግም ይሞክረዋል ተብሎ ብዙም አይጠበቅም። ይሄን የማያደርገዉ ፍላጎቱ ስለሌለዉ አይደለም። ይልቁንስ ዛሬ ላይ ሰራዊታችን የሚገኝበት አሰፈሪ ቁመና ማወቁ ብቻ ሳይሆን የወሎ ህዝብና ፋኖ እንዲሁም የአፋር አናብስቶች በትላንቱ ቁመናቸዉ ላይ እንዳልሆኑ ወያኔ በደንብ ስለሚገባዉ ነዉ። ከዚህም በላይ ወያኔ ይሄን ግንባር ዳግም የመዳፈር ጉዳይ ቢሞክር፤ በመጀመሪያዉ ዙር ወረራ በፈፀመዉ ግፍ ምክንያት ሊበቀለዉ የሚፈልግ አሰፍስፎ የሚጠብቅ ህዝብና ፋኖ እንደተፈጠረ ጠንቅቆ ስለሚያቅ ወያኔን የወሎና አፋር ግንባርን መዳፈር እጅግ ያስፈራዋል።

አንዳንድ መረጃዎች እንደሚጠቁሙት ወያኔ በወሎና አፋር ግንባር የከፈልነዉን ዋጋ በጎንደርና ወልቃይት ግንባር አድርገነዉ ቢሆን ኖሮ ድል ይቀናን ነበር ብሎ መገምገሙን ሰምተናል። በርግጥ ወያኔ ወደ መሀል ወሎና ሽዋ እንዲሁም ሚሌ ግንባር ዘልቆ የገባዉ ይሄን የጎንደር ግንባር ሞክሮት አልሳካለት ካለ በሁዋላ ስለመሆኑ ልብ ማለት ይገባል። ያም ሆኖ ከመጀመርያዉ ሽንፈት በሁዋላም ቢሆን ሀይሉን አጠናክሮ እንደገና በጎንደር/ወልቃይት ግንባር አለመዝመቱ ወያኔን ቁጭት ላይ እንደጣለዉ መገንዘብ ይቻላል።

እዚህ ላይ አንድ ነገር ልብ ማለት ይገባል። ጀ/ታደሰ ወረደ በአንድ ወቅት እንደነገረን፣ በረሀ እያሉ ሰራዊታቸዉን በተለያዩ አቅጣጫ አሰማርተዉ ለመዋጋት መሞከራቸዉ ስህተት እንደነበር ገምግመዋል። በመሆኑም ተንቤን በረሀ ላይ የመከላከያ ሀይላችንን ያጠቁት ሁሉንም ተዋጊያቸዉን በአንድ ግንባር ብቻ እንዲሰለፍ በማድረግ ነበር። ይህ ሁሉን ወታደራዊ አቅም ከህዝባዊ ማዕበል ጋር አዋህዶ በአንድ አቅጣጫ ብቻ ማሰለፍ መቻል፣ ለወያኔ ምን ያክል አቅም ጥሮለት እንዳለፈ ልንዘነጋዉ አይገባም። ወያኔ ይሄንን መንገድ በጎንደር ግንባር አለመድገሙን ነዉ እንደስህተት የገመገመዉ።

አሁን ነገሮች ሁሉ ግልፅ ሁነዋል። በብዙ መመዘኛዎች ካየነዉ ወያኔ ጦርነቱን እንደገና መጀመሩ አይቀርም። በዚህ ጉዳይ ማመንታት አይገባም። ከቀጣዩ አይቀሬ ጦርነት አንፃር ወያኔ ለማዛባት ያክል በወሎና አፋር ግንባሮች እንዲሁም በሽራሮ ግንባር ከኤርትራ ጋር የተወሰነ ሰራዊት ክፍሎችን በማሰለፍ መለስተኛ ጦርነቶችን እያካሄደ ዋነኛ ሀይሉንና ወሳኙን ጦርነት ግን በጎንደር ግንባር(ደባርቅና ወልቃይት፤ ምዕራብ ጎንደር ዞን) ማድረጉ አይቀርም። ወያኔ ይሄንን የማድረግ ፍላጎት እንዳለዉ ከአጠቃላይ ፍላጎቱና አሁናዊ ከሚያደርጋቸዉ እንቅስቃሴወቹ ተነስቶ ለመተንበይና ለመረዳት አይከብድም።

ከጦርነት ስልት አንፃር አሁንም ወያኔ ህዝባዊ ማዕበልን እንደሚጠቀም ጥርጥር የለዉም። በዚህ ሂደትም የታጠቀም ሆነ ያልታጠቀ ብቻ ጠጠር መወርወር የሚችል ሁሉም ወንድና ሴት ትግራዋይ መሰለፉ አይቀሬ ነዉ። በተለይም በጎንደር/ በወልቃይት ግንባር። ወያኔ ይሄንን ግንባር ሰብሮ ኢትዮጵያን አፍርሶ የትግራይን ሪፐብሊክ ለማወጅ በሂደትም አማራን በተለይም ደግሞ በቅርብ የሚያገኛቸዉን የጎንደር አካባቢወች በማዉደም የጦርነቱ ፍፃሜ እንዲሆን ይፈልጋል።

ወያኔ ይሄን የጎንደር/ወልቃይት ግንባር መሰበር ከቻለ በአሸናፊነት ስሜት ሁኖ ወደ ድርድር ለመምጣት ብዙም አይቸገርም። ይሄም ማለት ወያኔ የጦርነቱ ፍፃሜ እንዲሆን የሚፈልገዉ ወልቃይትን ከተቆጣጠረ በሁዋላ በድርድርም ሆነ በጦርነት በሚያገኘዉ ድል ላይ ተመስርቶ የትግራይን ሪፐብሊክ በማወጅ ስለመሆኑ መጠራጠር አይገባም። የነ እራያና ሌሎቹም አካባቢወች ወያኔ ወልቃይትን ከተቆጣጠረ በሁዋላ ብዙ አይከብዱትም። ሲጠቃለል በወያኔ ቤት ወልቃይት ላይ የሚካሄድ ጦርነት የፍፃሜ ጦርነት እንደሆነ ታምኖበት የሚካሄድ ጦርነት ነዉ።

አሁን ጥያቄዉ የኢትዮጵያ መንግስትና በተለይም ግንባር ላይ ያለዉ የአማራ ህዝብ ይሄንን አይቀሬ ወረራ፣ የወያኔ የጦርነት ስልትና አቅጣጫ ተገንዝበዉ ምን ያክል በቂ ዝግጅት አድርገዋል የሚለዉ ነዉ። በዚህ በኩል ሁላችንም በአንድ ነገር የምንስማማ ይመስለኛል፣ ይሄዉም የሀገራችን መከላከያ ሰራዊት ቁመናዉ በሁለንተናዊ መስኩ እድገት ስለማሳየቱ። ይሄንን ወያኔ ሳይቀር ያዉቀዋል። ወያኔ ወደዚህኛዉ ዙር ጦርነት ሲገባ የመከላከያችንን ቁመና ሳይገመግም አይደለም።

ይሁን እንጅ ምንም ያክል ሰራዊታችን ቁመናዉ በከፍተኛ ደረጃ ቢገኝም፣ ከጠላት አንፃር የሚገጥመዉ ሀይል በህዝባዊ ማዕበል ታጅቦ ነዉና ሁሉን ነገር ለሰራዊታችን ሰጥተን ልንዘናጋ አይገባም። ሰራዊታችን ከትግራይ እየተጠቃ በወጣበት ጊዜ አንድ የጦር መሪ ስላጋጠመዉ የህዝብ ማዕበልና አሰቸጋሪነት “ለካስ ሰዉ መግደልም ይሰለቻል” ሲል ያወራኝ ነገር ዛሬም አረሳዉም። ስለዚህ ሰራዊታችን ምንም ያክል ቢጠነክር የሚገጥመዉ ጠላት በህዝባዊ ማዕበል ታጅቦ ነዉና ይሄንን ታሳቢ ያደረገ ዝግጅት ማድረግ እጅግ አስፈላጊ ነዉ።

ሰለዚህ ወያኔ የሚከፍተዉ ቀጣዩ ጦርነት በህዝባዊ ማዕበል የሚታጀብ መሆኑ ላይ ከተግባባን ዘንዳ፣ ሰራዊታችንን የሚያግዝ ህዝባዊ ማዕበል ማዘጋጀት ደግሞ ከስቪል አሰተዳደሩ የሚጠበቅ ይሆናል። በዚህ በኩል በተለይም ግንባር ላይ ተጥዶ የሚገኘዉ የአማራ ክልል መንግስት ትልቁን ድርሻ መዉሰዱ አይቀርም። ስለሆነም የአብክመ መንግስት ምንም እንኳን ለጊዜዉ እንደ ወያኔ ት/ቤቶችን ዘግቶ ሁሉንም ወጣት ወደ ጦር ግንባር ለማሰለፍ የሚገደድበት ሁኔታ ላይ ባይሆንም፣ ከዚህ ዉጭ የሆነዉን ማናቸዉም አቅሙ ለዉጊያ የደረሰ እና ጥራቱን የጠበቀ ሀይል ለጦርነት ማዘገጀት ይኖርበታል። ይህ ዝግጅት ያልታጠቀዉን ወጣትም ማካተት አለበት። በዚህ ልክ ካልተዘጋጀን የወያኔ አመጣጥ ለፍፃሜ በመሆኑ እንቸገራለን። ወልቃይት ላይ የፍፃሜዉን ጦርነት ለማጠናቀቅ ይቻል ዘንድ፣ ከመከላከያ ሰራዊታችን ጎን የሚሰለፍ ግዙፍ፣የሰለጠነና ጥራት ያለዉ ህዝባዊ ማዕበል ማዘጋጀት ይገባል። ይሄን ለማድረግ ግዜ ያለ አይመስለኝም። በርግጥ የተጀማመሩ ስራዎች ይኖራሉ።

ለማጠቃለል ያክል ወልቃይት ለኢትዮጵያ ህዝብና መንግስት እንዲሁም ለወያኔ የህልዉና ጥያቄ ሁናለች። ወልቃይት ለሁለቱም ወገኖች ለምን የህልዉና ጉዳይ እንደሆነች ካሁን በፊት ተመላልሸበታለሁ። ወልቃይት በወያኔ እጅ ገባች ማለት ኢትዮጵያ ፈረሰች ማለት ሲሆን፣ በአንፃሩ ለወያኔ ደግሞ በኢትዮጵያ ፍርስራሽ ላይ አዲሷን የትግራይ ሪፐብሊክ እንዲፈጥር እድል መሰጠት ማለት ነዉ። በመሆኑም ሁለቱም ወገኖች ለህልዉናቸዉ ሲሉ ወልቃይት ላይ የፍፃሜዉን ጦርነት ለማድረግ ይገደዳሉ። በዚህ ወልቃይት ላይ በሚካሄድ የፍፃሜ ጦርነት አሸናፊ የሆነ ሀይል አላማዉን በቀላሉ ማሳካት ይቻለዋል።

አትዮጵያና መንግስቷ ይሄንን የፍፃሜ ጦርነት በድል ከተወጡ፣ የኢትዮጵያን ቀጣይነት ያረጋግጣሉ፣በወያኔ አምሳል ተፈጥረዉ በየአቅጣጫዉ አገራችንን የሚያምሱ ሀይሎች በያሉበት በቀላሉ ይሟሽሻሉ። ወያኔንና መሰሎቹን ፈረስ አድርገዉ አገራችንን ለማወክ እየሰሩ ያሉ የዉጭ ጠላቶቻችን እጃቸዉ ይቆረጣል። ከዚህም በላይ ወያኔ ሳይወድ በግድ በተሸናፊነት ስሜት ሁኖ ወደ ድርድር ይመጣል። መጨረሻ ላይ ይህ ሁኔታ በሂደት ወያኔን ከትግራይ ህዝብ ጫንቃ እስከወዳኛዉ ለማዉረድ እድል ይሰጣል። በአንፃሩ በዚህ የፍፃሜ ጦርነት ወያኔ ድል ካገኘ ነገሮች ሁሉ የተገላቢጦሽ ይሆናሉ። መጨረሻዉም የኢትዮጵያን መፍረስ ማስከተሉ አይቀርም።

ስለዚህ ኢትዮጵያን ለማፅናት ይሄንን የፍፃሜ ጦርነት በድል መወጣት የግድ ነዉ። ይሄ እንዲሆን ደግሞ የመከላከያ ሰራዊታችን ዝግጅትና እቅድ እንዳለ ሆኖ፣ ከሰራዊታችን ጎን ተሰልፎ የወያኔን ህዝባዊ ማዕበል የሚመክት ፀረ-ህዝባዊ ማዕበል የሆነ ግዙፍ እና ጥራት ያለዉ ህዝባዊ ማዕበል ማዘገጀት የግድ ይለናል። ሌላ ምርጫ የለንም።

Exit mobile version