Site icon ETHIO12.COM

ጋሻው መርሻ – ባንዳዎችን አስጠነቀቁ

ወረራ ተፈፅሞብናል። ይህን ወረራ በተመለከተ ያለው አቋም አንድ እና አንድ ብቻ ነው። ህዝባችንን አስተባብረን ከተዋጊው የኢትዮጵያ ሰራዊት ጋር በተናበበ መልኩ መመከት። ይህን ማድረግ ከተወረረ ህዝብ የሚጠበቅ ትንሹ ስራ ነው። ድንበር ተሻግረን ለመውረር አልሞከርንም። ድንበራችን ጥሶ የገባው ራሱ ወራሪው ኃይል ነው። ስለሆነም ይህን ወራሪ ኃይል መመከት እና ማሳፈር የሚገባ ነው።

በመንግስት ተቃዋሚነት ስም ለጠላት የመንገድ መሪነት ሚና መወሰድ ባንዳነት ነው። በነገራችን ላይ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የኢትዮጵያን ኃይሎች ማጣጣል እና ለወያኔ ማቃጠር እንደ ትልቅ ብቃት እየተቆጠረ ነው። ይህን የመሰለ የባንዳ ስራ አደብ ማስያዝ የሚጠበቅ ነው። ሐገር ችግር ላይ በሆነችበት ወቅት ከሐገር ጋር መሰለፍ በህግም በሞራልም ግዴታ ነው። ሰው እንዴት ከሐገሩ በተቃራኒ ይሰለፋል በፈጣሪ። በአጭሩ ከሐገሩ በተቃራኒ መሰለፉን እንደ ኩራት የሚቆጥረውን የከተማ አውደልዳይ አደብ ማስገዛት ያሻል።

የአማራ ህዝብ ወቅት እየጠበቀ ሲያቆስለው የሚኖረውን ኃይል በራሱ መከላከል በሚችልበት አግባብ መደራጀት ይኖርበታል። ራስ በቅ መሆን የዚህች ዓለም ገዥ ህግ ነው። ደካማ ከሆንክ ማንም እረግጦህ የሚያልፍ የሜዳ ላይ ሳር ትሆናለህ። ስለዚህ ከብረት በጠነከረ አንድነት ለህልውናህ ተሰለፍ። “ጦርነቱ አይመለከትህም” የሚሉ ትጥቅ አስፈቺዎችን አታዳምጣቸው። እነሱ ከአንተ ወገን አይደሉምና።

ህዝባችን እንደ ከዚህ ቀደሙ:-

  1. ወጣቱ ኃይል ተዋጊውን ኃይል በገፍ መቀላቀል አለበት። መሰልጠን፣ ዘመናዊ መሳሪያ መታጠቅ ይገባዋል። ወታደርነት ልዩ ክብር ሙያ መሆኑን ማወቅ ይገባል።
  2. የንግዱ ማህበረሰብ እንደ ከዚህ ቀደሙ ኃብት ንብረቱን ማዋጣት ይኖርበታል። ወራሪው ኃይል በደረሰባቸው ከተሞች ሁሉ ኃብት ንብረት ይዘርፋል፣ ያወድማል። ስለሆነም ኃብት ንብረትን ለማዳን ኃብትና ንብረት ቀድሞ ለተዋጊው ኃይል እገዛ ማዋጣት የተገባ ነው።
  3. ሌሎች ክልሎች ወረራውን ለመቀልበስ ርብርብ ማድረግ ይጠበቅባቸዋል። ይኸ ውጊያ በአፋር እና በአማራ ክልሎች በኩል እየተደረገ ያለው በአጋጣሚ ጎረቤት ስለሆኑ መሆኑን አውቆ ይህን ሐገር አፍራሽ ቡድን ለመደምሰስ የሚደረገውን ትግል በሚጠበቅባቸው ልክ ማገዝ ይገባቸዋል።
  4. የፌድራሉ መንግስት የትኛውንም አይነት ህጋዊ መሳሪያ ተጠቅሞ ህዝባዊ ማዕበሉን መግታት አለበት። በማዕበል መልክ የመጣን ኃይል ቦታ በለቀክለት ቁጥር ህዝባችን ላይ እንደ ግሪሳ እንዲሰፍር እያደረከው መሆኑን ማወቅ የተገባ ነው። ህዝባችን ከዚህ ቀደም የከፈለው በቂው ነው። ሌላ ዙር ተጨማሪ ወረራን ማስተናገድ አይችልም። የዚህን ወረራ ስፋት እና የጉዳት መጠን መቀነስ ይገባል። በዚህ ቡድን ላይ የማያዳግም እርምጃ ወስዶ በህግ ስር ማዋል የተገባ ነው። በየጊዜው መቁሰል አይገባንም።
  5. ዲያስፖራው ምዕራባዊያን ተፅዕኗቸውን ያቆሙ ዘንድ በተባበረ መልክ ስራ መስራት ይገባዋል። ለተቃውሞ ፖለቲካም ቢሆን ሐገር መኖር አለባት።

መንግስት እና ሐገረ መንግስት ለየቅል ናቸው። ሐገሬ ጋር በመቆሜ ሁሌም እኮራለሁ። መንግስትን በመቃወም ስም ሐገራችሁን የምታቆስሉ ሰዎች ፈጣሪ ይማራችሁ።>>
ጋሻው መርሻ
የአብን ስራ አስፈፃሚ

Exit mobile version