Site icon ETHIO12.COM

ሰአሊው ዲፕሎማት በኳታሩ አለም ዋንጫ..!!!

ኢትዮጵያ በአለም ዋንጫ ለመሳተፍ ባትታደልም የተለያዩ ኢትዮጵያውያን በኳታሩ አለም ዋንጫ ከጨዋታዎች ባሻገር አገራቸው ትኩረት እንድታገኝ እያደረጉ ነው።

ከእነዚህ ኢትዮጵያውያን መካከል በኳታር ኑሮውን ያደረገው ኢትዮጵያዊው ሰአሊ ተሰማ አስራት አለም ዋንጫው ሲጀመር አንስቶ በጥበብ ስራው የበርካቶችን ትኩረት አግኝቷል፤ በስራዎቹም ኢትዮጵያን እያስተዋወቀ ይገኛል።

ሰአሊው ለኢትዮጵያ የእግር ኳስ አባት፣ የቀድሞው የቅዱስ ጊዮርጊስ ባለውለታ፣ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌድሬሽን የበላይ ጠባቂ እንዲሁም የካፍ ፕሬዝዳንት በመሆን ላገለገሉት ታሪካዊው የስፖርት ሰው አቶ ይድነቃቸው ተሰማ በስማቸው ስታዲየም ሰይማለች፤ አፍሪካዊቷ ሀገር ሞሮኮ።

ለዚህ መታሰቢያ ይሆን ዘንድ በዚህ አለም ዋንጫ ግማሽ ፍጻሜ ደርሳ ታሪክ ስትሰራ ትልቁን ሚና የተጫወተ ኮከቧን ሀኪም ዚያችን ከሳለበት ምስል ስር የይድነቃቸውን ምስል አሳርፎበት ሀገሪቱ ኢትዮጵያን ስላከበረች አመስግኗል፡፡

ከኢትዮጵያውያኑ አንዱ በስነጥበብ ሙያው አስደናቂ የዲፕሎማሲ ስራ በማከናወንና የኳታር የዓለም ዋንጫ መስተንግዶ በማሟሟቅ የተሰካለት ሰዓሊ ተሰማ አስራት ላለፉት 14 ዓመታት በኳታር የኖረ ሲሆን፣ ከስነጥበብ ሙያው ባሻገር በኳታር ኤርዌይስ የቴክኒክ ዲፓርትመንት ውስጥ ይሰራል፡፡

በታዋቂው የኳታር ኢንተርናሽናል አርት ፌስቲቫል (QIAF) ላይ የአፍሪካ ብራንድ አምባሳደር ሲሆን ለ2022 የዓለም ዋንጫ ላይ በበጎ ፈቃደኝነት እንዲያገለግሉ ከተመረጡ ኢትዮጵያውያንም አንዱ ነው፡፡

ሰዓሊ ተሰማ ኳታር 22ኛው የዓለም ዋንጫን እንድታዘጋጅ በፊፋ በ2010 እኤአ ላይ ከተመረጠችበት ጊዜ አንስቶ በስነጥበብ ሙያው የበኩል ድጋፍ እያደረገ ይገኛል። በስነጥበብ ዲፕሎማሲ ባከናወናቸው ተግባራትም በርካታ ሚዲያዎች በዘገባዎቻቸው ተምሳሌት አድርገው በመጥቀስ አድንቀውታል፡፡

በኳታሩ አለም ዋንጫ ከ51 በላይ የስነጥበብ ባለሙያዎች 102 የስዕል ስራዎችን ባቀረቡበት ኤግዚብሽን ላይ የሰአሊ ተሰማ ስዕል በልዩ ጭብጡ አነጋጋሪ ለመሆን እንደቻለ ይታወሳል። በ2021ና በ2022 እኤአ ላይ በተካሄዱት የኳታር ኢንተርናሽናል የአርት ፌስቲቫሎች ዓለም ዋንጫውንና አዘጋጇን ኳታር በሚያስተሳስሩ ጭብጦች የሰራቸው ስዕሎች በኳታር ንጉሳውያን ቤተሰቦች፤ መንግስታቸው፤ የስነጥበብ ተቋማት መሪዎችና የኢትዮጵያ ማህበረሰብም ተደንቀውለታል፡፡

Via – Ahemed Habib

Exit mobile version