Site icon ETHIO12.COM

አርባ አምስት የወርቅ ኮንትሮባንድ አስተላላፊ የውጭ አገር ዜጎች ተያዙ

አርባ አምስት የውጭ ዜጎች በሕገወጥ መንገድ ወርቅ ሲያዘዋውሩ በቁጥጥር ስር ውለው ጉዳያቸው በፌዴራል እና በክልሉ መንግሥት ምርመራ ቡድን እየታየ ነው ሲሆን ሌሎች አምስት አጭበርባሪ የተባሉ ደግ ሞ ጉዳያቸው በክልሉ በፍርድ ቤትና በአስተዳደራዊ መንገድ መታየቱ ተገለጸ። የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል የማዕድን ሀብት ልማት ቢሮ እንዳለው ክልሉ ውስጥ ሰላም ቢሰፍንም ፈቃድ ከወሰዱት አልሚዎች ውስጥ ወደ ስራ የገቡት ሃያ ናቸው።

የቢሮው ሃላፊ አቶ ካሚል አሕመድ ለአዲስ ዘመን እንዳስታወቁት የእምነበረድና የድንጋይ ከሰል ምርት ፍቃድ ከወሰዱ ከ250 በላይ አልሚዎች 20 ያክሉ ብቻ ወደ ሥራ መግባታቸውን፣ ሌሎች ሥራ ውስጥ ለመግባት ፍላጎት ቢኖራቸውም መግባት አልቻሉም። ሥራ ውስጥ መግባት ያልቻሉበት ዋና ምክንያት በፀጥታ ስጋት ሲሆን ይህም ከክልሉ ውጪ ባሉ መንገዶች ላይ የሚፈጠር እንደሆነ አመልክተዋል። ከክልሉ ውጭ ባሉ መንገዶች ችግር የሚፈጥሩትን ቦታዎች ግን ለይተው አላስታወቁም። ክልሉ ከሁሉም በላይ በተለይ ከአማራና ከኦሮሚያ ክልል ጋር በስፋት የሚገናኝ እንደሆእ ይታወቃል።

የመጡበት አካባቢ በውል ሳይጠቀስ 45 የውጭ አገራት ዜጎች ሕገወጥ የወርቅ ሲያዘዋውሩ ተገኝተው በቁጥጥር ስር መዋላቸውን የቢሮ ሃላፊው ገልጸው፣ ቁጥጥሩ በፌደራል ፖሊስና በክልሉ ፖሊስ አማካይነት ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ሃላፊው ተናገረዋል። ወርቅ ለብሄራዊ ባንክ ለማቅረብ ተስማምተው አንድ ጊዜ ኮቲያቸው የባንኩን ደጅ ረግጦ የማይውቁትን የመለየት ስራም እየተጠናቀቀ መሆኑን አመልክተዋል። መንግስት በቤኒሻንጉል ብቻ ሳይሆን በመላው አገሪቱ ኮንትሮባንድን ለመግታት መከላከያም ተሳታፊ እንደሚሆን በቅርቡ ማስታወቁ አይዘነጋም።

 አዲስ አበባ፡- በክልሉ በማዕድን ልማት ለመሰማራት ፈቃድ ከወሰዱ ከ250 በላይ አልሚዎች መካከል ወደ ሥራ የገቡት 20 ብቻ እንደሆኑ የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል የማዕድን ሀብት ልማት ቢሮ አስታወቀ። በክልሉ በሕገ ወጥ መንገድ ወርቅ ሲያዘዋውሩ የተገኙ 45 የውጭ አገራት ዜጎች በቁጥጥር ስር ውለዋል።

የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ማዕድን ሀብት ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ካሚል አሕመድ ለኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት እንደገለጹት፤ በክልሉ ካሉት ማዕድናት የወርቅ ምርት ቀዳሚ ሲሆን የድንጋይ ከሰልና እብነበረድም በክልሉ ካሉ እምቅ የማዕድን ሀብቶች መካከል ተጠቃሽ ነው።

ክልሉ ካለው የማዕድን ሀብት አንጻር የሚፈለገውን ጥቅም እያገኘ እንዳልሆነ የገለጹት ቢሮ ኃላፊው፤ መንግሥት ወርቅ ወደ ብሔራዊ ባንክ እንዲገባ 35 በመቶ ማበረታቻ ቢሰጥም በሚፈለገው ልክ አልገባም ብለዋል። በዚህ አመት የተገኘው የወርቅ ገቢ ከባለፈው አመት ጋር ሲነጻጸር ዝቅተኛ ነው፤ ወርቅ አምርተው በቀጥታ ባንክ እንደሚያስገቡ ውል ወስደው ወደ ሥራ የገቡት ከ200 በላይ የሚሆኑ ፈቃድ የተሰጣቸው የወርቅ አዘዋዋሪዎች አሉ ሲሉም አክለዋል፤ ከእነዚህ ውስጥ ከ50 በላይ የሚሆኑት ወርቅ ለማስገባት ባንክ ቤት ገብተው እንደማያውቁ ገልጸዋል።

እንደ አቶ ካሚል ገለጻ፤ በክለልሉ በወርቅ ማምረትና አዘዋዋሪነት ፈቃድ ከተሰጣቸው ውስጥ የትኞቹ ወደ ባንክ አስገቡ፣ የትኞቹስ አላስገቡም የሚል የልየታ ሥራ በመሥራት ወደ ባንክ ባላስገቡት አካላት በፈቃድ አስተዳደር መመሪያ ደንቡ መሠረት እርምጃ መውሰድ ተጀምሯል። ሥራ ውስጥ ያልገቡትንም በቀጣይ ወደ ሥራ ለማስገባት ቢሮው ከሚመለከታቸው የመንግሥት አካላት ጋር በመቀናጀት እየተሠራ ነው።

ሕገ ወጥ የወርቅ ዝውውሩ በጌጥ መልክና ሌሎች ስውር ዘዴዎችን በመጠቀም የሚከናወን ነው ያሉት አቶ ካሚል፤ ሕገ ወጥ ዝውውር በመደረጉ በወርቅ ምርት ላይ የተገኘው ገቢ ዝቅተኛ ሆኗል። የቁጥጥር ሥርዓቱም በልኩ አልነበረም። ስለዚህ አሁን ላይ በወርቅ ምርት ላይ የገቡ አልሚዎችን ቁጥጥር ማጠናከር አንዱ እርምጃ ነው። በተጨማሪም በተለያዩ ኬላዎች፣ ከክልሉ ፖሊስ፣ ልዩ ኃይል፤ ፌዴራል ፖሊስ ጋር በመቀናጀት በሕገወጥ መንገድ የሚካሄደው ሕገ ወጥ የወርቅ ዝውውር መቆጣጠር ላይ ቀጣይ ትኩረት የተሰጠው እርምጃ መሆኑን ተናግረዋል።

በክልሉ አሁን ላይ አንጻራዊ ሰላም እንዳለ የገለጹት ቢሮ ኃላፊው፤ ፈተናው በወርቅ አዘዋዋሪዎችና አምራቾች ላይ ወደ ባንክ ከሚያስገቡ ይልቅ በሕገ ወጥ መንገድ የተሻለ ገቢ ስለሚያገኙ ለቁጥጥር አንዱ ፈታኝ የሆነ ጉዳይ ነው። ሕገ ወጥ ነጋዴዎችን ለማግኘት መቸገር፣ አየር መንገድም የፍተሻ ማሽን እንዳይለየው የሚያስችል ኬሚካል እየቀቡ የሚያዘዋውሩ ስላሉና ወርቅ በባህሪው ትንሽ ስለሆነ ለመቆጣጠር አዳጋች አድርጎታል ብለዋል።

አቶ ካሚል 45 የውጭ ዜጎች በሕገወጥ መንገድ ወርቅ ሲያዘዋውሩ በቁጥጥር ስር ውለው ጉዳያቸው በፌዴራል እና በክልሉ መንግሥት ምርመራ ቡድን እየታየ ነው። ሌሎች 5 ሰዎች ጉዳያቸው በፍርድ ቤትና በአስተዳደራዊ መንገድ ታይቷል ነው ያሉት።

የእምነበረድና የድንጋይ ከሰል ምርት ፍቃድ ከወሰዱ ከ250 በላይ አልሚዎች 20 ያክሉ ብቻ ወደ ሥራ መግባታቸውን የጠቆሙት ቢሮ ኃላፊው፤ ሌሎች ሥራ ውስጥ ለመግባት ፍላጎት ቢኖራቸውም መግባት አልቻሉም። ሥራ ውስጥ መግባት ያልቻሉበት ዋና ምክንያት በፀጥታ ስጋት ሲሆን ይህም ከክልሉ ውጪ ባሉ መንገዶች ላይ የሚፈጠር ነው። በክልሉ ግን ጠረፋማ አካባቢዎች ካልሆነ በስተቀር አብዛኛው አካባቢ ላይ ምንም ዓይነት የፀጥታ ችግር ባለመኖሩ ማሠራት የሚችል ሁኔታ ተፈጥሯል ብለዋል።

ባለፉት ወራት በማዕድን ዘርፍ በልዩ አነስተኛ የወርቅ ማህበራት፣ በእምነበረድና በድንጋይ ከሰል ሥራ ለ2 ሺህ 250 ወጣቶች የሥራ ዕድል ለመፍጠር ታቅዶ ለ1ሺህ 765 ዜጎች የሥራ ዕድል መፈጠሩን ገልጸዋል።

ሞገስ ተስፋ

Exit mobile version