Site icon ETHIO12.COM

የአማራን ክልል በትግራይ በኩል ስጋት እንደማይገጥመው መተማመኛ ይፈልጋል

ብዙ ጊዜ ሚዛናዊ መረጃዎችን በማቅረብ የሚታወቀው ጌታቸው ሽፈራው “ዛሬም ውይይቶች እየተደረጉ ነው” ሲል በስሜትና ነገሮችን አውድ ለማሳት በሚያመች መልኩ መረጃ ለሚያሰራጩ ምክር ከለገሰበትና አግባብነት ያለውን የህዝብና የአማራ ልዩ ሃይል ጥያቄ በዝርዝር ካሰፈረበት ጽሁፍ ለመረዳት ተችሏል።

“የአማራ ልዩ ኃይል ገና ትጥቅ አልፈታም፣ ትጥቅ አስፈች ፕሮፖጋንዳዎችም አይጠቅሙም! ” በማለት “የአማራ ልዩ ኃይል ተበተነ፣ ጫካ ገባ” እያሉ  ፕሮፖጋንዳ የሚሰሩ ክልሉንም ሆነ ህዝቡን እንደማይጠቅሙ አመልክቷል።

“የአማራ ልዩ ኃይል ህጋዊ ካምፕ አለው። ጫካም አይገባም። ይህ ታስቦበትም ሆነ ባለማወቅ የሚደረግ ፕሮፖጋንዳ ጠላት አማራ ክልል ላይ ሊፈፅም ለሚፈልገው ጥፋት በር ከፋች ስለሆነ መቆም አለበት፣እየሆነ ያለው እንዲህ ነው” ሲል በዝርዝር ነጥቦቹን አስቀምጧል።

1) የፀጥታ ኃይሉም ሆነ ህዝብ አማራ ስጋት ስላለበት ቅድመ ሁኔታዎች ይሟሉ ብሏል። አሸባሪዎች ትጥቅ ይፍቱ ብሏል። በአማራ ህዝብ ላይ የሚደረገው ማፈናቀልና ማሳደድ ዋስትና አላገኘም። ሌሎች ቅድመ ሁኔታዎች ተቀምጠዋል። ይህ የህዝብም የልዩ ኃይሉም አቋም ነው።

2) ዛሬ ውይይቶች እየተደረጉ ነው። ልዩ ኃይሉ አቋሙን አሳውቋል። የህዝብ አቋም ግልፅ ነው። ቅድመ ሁኔታዎች ይሟሉ ተብሏል። ቅድመ ሁኔታዎች በደንብ ይታወቃሉ።

3) በዚሁ አጋጣሚ ልዩ ኃይሉንና ህዝብን ወደ ስሜት አስገብተው አማራ ክልል ላይ ጦርነት ማስጀመር የሚፈልጉ የፌደራል ፀጥታ ኃይል አካላት መኖራቸው ታውቋል። ዝም ብለው ስለጋቱት ያን እያመጣ አማራው ላይ ለመሞከር የሚጥር የክልሉ ክርፍፍ መአት ነው። ይህ በእሳት መጫወት እንደሆነ መታወቅ ይገባዋል።

4) የአማራ ህዝብ የሚጠብቀኝ ልዩ ኃይሉ ነው ብሏል። ይህ የህዝብ ፍላጎት ነው። አሸባሪን ትጥቅ ሳያስፈቱ አማራ ክልል ላይ ችግር ለመፍጠር የሚደረገው ሂደት መቆም አለበት።

5) የአማራ ልዩ ኃይል የአገር ዳር ድንበር እየጠበቀ ያለ፣ ሰራዊቱን ከጥቃት ያዳነ፣ ከወገኑ ጋር ሆኖ ወረራ የመከተ ኃይል ነው። ትህነግ ትጥቅ ባልፈታበት የአማራ ልዩ ኃይል ወደ መከላከያም፣ ወደ አድማ በታኝም፣ ወደ ፖሊስም ልትገባ ነው ብትለው አታሳምነውም። ህዝብም ፈቃደኛ አይደለም።

ነጥቦቹን ዘርዝሮ “በሌላ በኩል የአማራ ልዩ ኃይል ወደ ጫካ የሚበተን ኃይል አይደለም። አላማ አለው፣ ዕዝ አለው። ጥርት ያለ ጥያቄ አቅርቧል። ያን ጥያቄ መመለስ ነው የሚያዋጣው” ሲል ምክረ አሳቡን ዘንዝሯል።

መንግስትም ሆነ የክልሉ አስተዳደር ሁሉንም አስተያየት ግምት ውስጥ በማስገባት፣ ሕዝብን በማድመጥ፣ በቅርብ በተካሄደ ተደጋጋሚ ወረራ የደረሰውን ጉዳትና የዛን ጉዳት አተቃላይ ጠባሳ በማስላት ጥንቃቄ የተሞላው አካሄድ ሊከተሉ ይገባል። ህዝብ ሁሌም ትክክል ነው።

Exit mobile version