ETHIO12.COM

የኢቲቪ “ጋዜጠኛ” በአደገኛ ዕፅ ዝውውር በቁጥጥር ሥር ዋለ

የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ በአደገኛ ዕፅ ዝውውር የተጠረጠረውን ጋዜጠኛ በቦሌ ዓለም አቀፍ ኤርፖርት በቁጥጥር ሥር ማዋሉን አስታወቀ፡፡

በአደገኛ ዕፅ ዝውውር የተጠረጠረው ጋዜጠኛ በቁጥጥር ስር ሊውል የቻለው በበረራ ቁጥር ET-600 አውሮፕላን በመሳፈር ከአዲስ አበባ ወደ ዱባይ ዕፁን ለማስተላለፍ ሲል እንደሆነ ተገልጿል፡፡

ከጉዞ በፊት በቦሌ ዓለም አቀፍ ኤርፖርት የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ከኢትዮጵያ ጉምሩክ ኮሚሽን እና ከብሄራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት ጋር በመተባበር ሁልጊዜ በሚያደርገው የሰው አካልና የሻንጣ ፍተሻ በተጠርጣሪው የጉዞ ሻንጣ አካል ውስጥ ተሰርቶ ሊያልፍ የነበረ በዱቄት መልክ የተዘጋጀ 2 ነጥብ 10 ኪሎ ግራም ኮኬይን አደገኛ ዕፅ ከተጠርጣሪው ጋዜጠኛ ጋር ከምሽቱ 2፡40 መያዙን አስታውቋል፡፡

በተጠርጣሪው ላይ ምርመራ ተጠናክሮ የቀጠለ ሲሆን ግለሰቡ ይሰራበት ከነበረው መሥሪያ ቤት ከአራት ወር በፊት በሥነ-ምግር ችግር የተሰናበተ ሲሆን ከዚህ ቀደም ወደ ተለያዩ ሀገራት በሰዎች አማካኝነት አደገኛ ዕፅ ይልክ እንደነበር የፖሊስ የምርመራ ውጤት እንደሚያሳይ ተገልጿል።

አደገኛ ዕፅ ዝውውርን ለመከላከልና ለመቆጣጠር በሚደረገው ክትትል ኅብረተሰቡ የተለመደውን ቀና ትብብር አጠናክሮ እንዲቀጥልና በጉዞ ወቅት ከሦስተኛ ወገን አድርሱልኝ በሚል የሚሰጡ ቁሳቁሶችንና ሻንጣዎችን ይዘት በሚገባ መለየትና የሰዎችን ትክክለኛ ማንነት ማረጋገጥ እንዳለበት ፖሊስ ያሳስባል፡፡

FBC

Exit mobile version