Site icon ETHIO12.COM

የአሰብ ኮሪደር የመንገድ ግንባታ ፕሮጀክት በመጪው ሐምሌ ይጠናቀቃል

ኢትዮጵያን በአሰብ በኩል ከኤርትራ ጋር የሚያገናኘው የሜሎዶኒ መገንጠያ-ማንዳ-ቡሬ የመንገድ ግንባታ ፕሮጀክት በጥሩ አፈፃፀም ላይ እንደሆነ ተገለጸ፡፡

የመንገድ ግንባታው 71 ኪሎ ሜትር ርዝመት ያለውና በመንግስት በተመደበ ሁለት ቢሊዮን ብር በጀት በአስፋልት ኮንክሪት እና በሲሚንቶ ኮንክሪት ንጣፍ ደረጃ እየተገነባ እንደሚገኝ ተጠቁሟል፡፡

መንገዱ በገጠር 10 ሜትር እና በቀበሌ ከተሞች ደግሞ 21 ነጥብ 5 ሜትር ስፋት እንዲኖረው ተደርጎ በመገንባት ላይ መሆኑም ተጠቅሷል፡፡

የግብዓት እጥረት፣ በአካባቢው በነበረ የጸጥታ ችግር እና በኢትዮ ኤርትራ ጦርነት ወቅት ተቀብረው ያልመከኑ ፈንጂዎች መኖር በግንባታ ሂደቱ ላይ ተፅዕኖ ቢያሳድሩም ችግሮችን በመቋቋም ግንባታው በተፋጠነ ሁኔታ እየተካሄደ መሆኑን ከኢትዮጵያ መንገዶች አስተዳደር የተገኘው መረጃ አመላክቷል፡፡

መንገዱ ተገንብቶ ሲጠናቀቅ የሀገራዊ እና ቀጣናዊ ትስስሩ ጥረቱን ከማፋጠን ባሻገር የአካባቢው ነዋሪዎች የትምህርት፣ የጤና እንዲሁም መሰል ግልጋሎቶችን መዳረስ አስተዋፅኦ እንደሚኖረው ተገልጿል፡፡ 

የአሰብ ኮሪደር የመንገድ ግንባታ ፕሮጀክት የሚካሄደው ሻንዶንግ ሉሽያዎ ግሩፕ ካምፓኒ ሊሚትድ በተባለ የውጭ ሀገር የሥራ ተቋራጭ ሲሆን ግንባታው በመጪው ሐምሌ ወር  2016 ዓ.ም ይጠናቀቃል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
ዘገባው የአሚኮ ነው

Exit mobile version