Site icon ETHIO12.COM

አሮጌውን ወይን በአዲስ አቁማዳ ! የኖርንበት ፣ የቸከ የሰለቸ የፖለቲካ …

የኢትዮጵያ ታሪክ የእርስ በእርስ ጦርነት civil war & strife ነው። ይሄንን ያደፈ ጉድለታችንን ማስተካከል የምንችለው መሀከለኛውን መንገድ የያዙ ስብስቦችን በማብዛት ነው። ችግሩ በእኛ ሀገር ፖለቲካ መሀከሉን መንገድ ልትይዝ ስትሞክር የሚወረወርብህ ፍላጻ መብዛቱ ነው። ለዚህ ጥሩ ምሳሌ ኢዜማ ነው። ህወሃትም ፣ የኦሮሞ ብሄረተኜችም ፣ በቅርብ የተፈለፈሉት የአማራ ብሄረተኞችም ለፓርቲው ያላቸውን ጥላቻ ማየት በቂ ነው። ፍርሃታቸው ይገባናል በስሜት ያሰባሰቡትን ደጋፊ ከማንም በላይ በሀሳብ ሊበትንባቸው የሚችለው የመሀከሉ መንገድ እንደሆነ ጠንቅቀው ሰለሚረዱ ነው።

በእኛ ሀገር ፖለቲካ ፣ ማህበራዊ ህይወት ፣ ተሰባስቦ መስራት ወዘተ ውስጥ አንዱ ቋሚ ልማድ አሮጌውን ልማድ ፣ ትናንት የሄድንበትን መንገድ ቀለም ቀብቶ ፣ ” በአዲስ ማኔጅመንት ስራ ጀምረናል ” አስለፍፎ ‘ አዲስ ‘ ሆኖ መምጣት የተለመደ ነው። ፈረንጅ reinventing the wheel እንዲል – የተፈለሰፈን ዳግም መፈልሰፍ። መአህድ የነበረው መኢአድ ሆኖ ይመጣል ባመቱ ፣ አንድ መንፈቅ ከርሞ ሰማያዊ ነኝ ይልሃል ትዕግስቱ ካለህ ኢዜማ ውስጥ ታገኘዋለህ ለጥቆም በሰበር ያስነግርና ሌላ ‘ አዲስ ‘ ፓርቲ ውስጥ።

እዚህ ከፓርቲ ፓርቲ እንደ ጦጣ የመዝለል ልማድ ውስጥ አንዱ constant ክስና ዘለፋ ነው። በፊት በፊት ክሱ መሪው አምባገነን ሆነብን ነበር አሁን ሂሳብ የሚደፋው ” በብሄሬ ተጠቃሁ ” ነው። ስልጤው ኑሪ ሙደሲር ጉራጌው ብርሃኑ ኢዜማ ውስጥ ያደረሰበትን የብሄር ጥቃት ሰላሳ ገጽ ክስ ለማንበብ እራሴን እያዘጋጀሁ አለሁ ።

ታሪክ ዛሬ ይጀምራል :

የዘመናችን ፖለቲካ አብይ መፈክር ” ታሪክ ዛሬ ይጀምራል ” የሚል ሳይሆን አይቀርም። ትናንትን ለማየት ያን ያህል ፈቃደኝነቱም ችሎታውም ያለን አይመስልም። የትግል አጋርህን ፣ ብዙ የደከምክበትን ፓርቲ በአደባባይ ጥንብ እርኩሱን ማውጣት ዛሬ የተጀመረ የሚመስላቸው ጥቂት አይባሉም። ትናንት በአደባባይ ስማቸው በሀሰት የጠለሽ ሰዎች ከራሳቸው lived experience አይማሩም። ቀን የሞላ ሲመስላቸው እንርሱም ነውረኛውን ልማድ በደማቅ ይሄዱበታል።

በአንድ ፓርቲ ውስጥ የነበሩ ሰዎች ቀን ጠብቆ መባላት ዛሬ አልተጀመረም። ድንቅ ፣ አዲስ ክህሎትም አይደለም። የኢህአፓ ሰዎች አመራሮቻቸውን እነ ጌታቸው ማሩን በሀሳብ ስለተለያቸው ብቻ ገድለው ፣ ቆዳውን ገፈው ጥለውታል። ብርሃነ መስቀል ረዳም እንደ አምላክ ያዩት በነበሩት ተከታዮቹ ተሳዷል። በዩቱይብ ሰበር ፣ በየሚዲያው እየዞሩ ” ብርሃኑ ነጋ ይሰቀል ” ብሎ ማስጮህ አዲስ ፈጠራ አይደለም የኖረው የፖለቲካችን ልማድ ነው። አዲስ ግኘት ይሆን የነበረው ከኖረው መጥፎ ልማድ የተለየ ነገር ተይዞ ቢመጣ ነበር።

ፓርቲ እንደ ዣንጥላ

ፖለቲካ ፓርቲ አንድ ወጥ ሀሳብ ( homogeneous ideas ) ያሏቸው ሰዎች መሰባሰቢያ አይደለም። ፖለቲካ ፓርቲ በቁልፍ ሀሰቦች ላይ ስምምነት ያላቸው የራሳቸው ህሳቤ ያላቸው ሰዎች መሰባሰቢያ ጥላ umbrella of ideas ነው። በፖለቲካ ፓርቲ ውስጥ spectrum of ideas አሉ። የእንግሊዙ ሌበር ፓርቲ የጨሱ ኮሚኒስቶች ፣ ግራ አክራሪዎችና centrist leftists መሰባሰቢያ ነው ። አባላቱ እንኳን በመንግስት በፐርቲያቸውም አቋሞች ላይ የተለያየ ህሳቤ ያራምዳሉ ነገር ግን በወቅቱ በአብላጫ ድምጽ የሸነፈው አመራርን ደግፈው የፓርቲውን ስራ ያስኬዳሉ ።

የቀድሞው ሌበር ፓርቲ መሪ Jermy Corbyn የጨሰ ሶሻሊስት ነው። ስልጣን ስይዝ መብራት ፣ ውሃን ፣ ባቡር ወዘተ ወሳኝ ኢንፍራስትራክቸሮችን ወደ መንግስት ባለቤትነት አዞራለሁ ሲል ይዝት ነበር። Centrist labours ይህንን የፖሊሲ አቋም አይደግፉም ነገር ግን ከፓርቲያቸው ለቀው አልሄዱም መጪውን የፓርቲ ምርጫ በትዕግስት ጠበቁ እንጂ።

እኛ ሀገር ስትመጣ ጉዳዩ ሌላ ነው። ከፓርቲ ፓርቲ እንደ ፌንጣ ለመዝለል ጥቂት ምክንያት አልያም መቶ የዲያስፖራ ዶላር በቂ ነው።

የመሀሉን መንገድ እና ፈተናው

ኢዜማ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ብዙ አዲስ ነገሮች ይዞ መጥቷል። ከኖረው የመጠፋፋት ፣ የጠላትነት ፖለቲካ መውጫውን አግኝቶ መሀከለኛውን መንገድ ይዟል። ይሄ ትልቅ ዕመርታ ነው ። ኢዜማ በዚህ አቋሙ ” በመኤሶናዊነት ” ተከሶበታል። የመኤሶንን ታሪክ እና የመሪዎቹን አርቆ አሳባነት ዘግይተን ያነበብን ሰዎች ይሄን ክስ እንደ ሽልማት ከመውሰድ የተሻለ ምርጫ አላገኘንም።

የኢትዮጵያ ታሪክ የእርስ በእርስ ጦርነት civil war & strife ነው። ይሄንን ያደፈ ጉድለታችንን ማስተካከል የምንችለው መሀከለኛውን መንገድ የያዙ ስብስቦችን በማብዛት ነው። ችግሩ በእኛ ሀገር ፖለቲካ መሀከሉን መንገድ ልትይዝ ስትሞክር የሚወረወርብህ ፍላጻ መብዛቱ ነው። ለዚህ ጥሩ ምሳሌ ኢዜማ ነው። ህወሃትም ፣ የኦሮሞ ብሄረተኜችም ፣ በቅርብ የተፈለፈሉት የአማራ ብሄረተኞችም ለፓርቲው ያላቸውን ጥላቻ ማየት በቂ ነው። ፍርሃታቸው ይገባናል በስሜት ያሰባሰቡትን ደጋፊ ከማንም በላይ በሀሳብ ሊበትንባቸው የሚችለው የመሀከሉ መንገድ እንደሆነ ጠንቅቀው ሰለሚረዱ ነው።

ኢዜማ ላይ የሚነሱ ክሶች

ከኢዜማ ለቀቅን ያሉት ሰዎችም ይሁኑ ሌሎች ከሚያነሷቸው ክሶች ዋንኛው ፓርቲው ለብልጽግና ፓርቲ እጅግ ቀረበ የሚለው ነው። ከኢዜማ ከሳሾች ብዙዎቹ ግን እጅግ ጽንፍ ከወጡ የብሄር ፓርቲዎች ጋር አንሶላ የሚጋፈፉ ናቸው። ( ዝርዝር ውስጥ አንገባም ማን ከእነ ማን ጋር እንደሚውል ራሱ ያውቃል)

የእንዲህ አይነቱ ክስ መነሻ የኢትዮጵያ ችግሮች መፍትሄው አልፋና ኦሜጋ እኔ ዘንድ ነው ያለው ከሚል አጉል ራስን የማተለቅ grandiose ዕይታ ነው የሚመነጨው። በሳይኮሎጂ family systems theory የሚባል እይታ አለ። dysfunctional የሆነን ቤተሰብ ሁሉንም የቤተሰብ አባላት በቅጡ ካልመረመርክና ካላገዝክ የተሻለ መንገድ ልታሲዘው አትችልም። ኢትዮጵያ one big dysfunctional family ነች ስህተቱን ሁሉ ወይ ብልጽግና አልያም ህወሃት ላይ ለጥፈህ መፍትሄ ልታመጣ/ ልታገኝ አትችልም። ኢዜማ ይህንን የተረዳ ፓርቲ አድርጌ እቆጥረዋለሁ – ለዚያም መሰለኝ ፓርቲው ከይዋጣልን ይልቅ የእንቀራረብ ፣ እንነጋገር ስትራቴጂን የመረጠው።

እናጠቃለው

ጥሁፋችንን እናጠቃለው። በሀገራችን አንድ የቆየ ብሂል አለ ሲትዮይቱ ቤቷን አቃጥላ የምትጨፍርበት። ይሄ ስነልቦና የብዙ ፖለቲከኞቻችን psyche ሳይሆን አይቀርም። ከመአህድ ጀምሮ ከፓርቲ በወጡ ቁጥር ከበሮ የሚደልቁ ሰዎች አውቃለሁ። ኢሳትን ያህል የህዝብ ተቋም ያፈረሱ ሰዎች በዝምታ ከተቋሙ አልራቁም አታሞና ከበሮ እየደለቁ እንጂ። በዚህ ሰሞን ከኢዜማ የተለዩት ሰዎችም አታሞ ይደልቁ ይዘዋል። የሚደልቁት አታሞ ምናልባት አዲስ ይሆናል ሰዎቹ ያልገባቸው አታሞ ድለቃው ፣ ሰበሩ ፣ ከሚዲያ ሚዲያ መዞሩ ምንም አዲስ ነገር የለውም። ያው የኖርንበት ፣ የቸከ የሰለቸ የፖለቲካ ባህል ውላጅ ነው።

Samson Michailovich ፌስ ቡክ የተወሰደ

ፎቶ ዝግጀት ክፍሉ

Exit mobile version