Site icon ETHIO12.COM

የኤርትራ መንግሥት በእስራኤል በተፈጠረው ግጭት ሞሳድ ድጋፍ አድርጓል አለ ፤ ተመድ የኤርትራዊያንን በጅምላ መባረር ነቀፈ

የኤርትራ መንግሥት በእስራኤል በባሕል ፌስቲቫል ላይ በተከሰተው ሁከት የተሳተፉት እንደ ሞሳድ ባሉ የደኅንነት ተቋማት የተደገፉ ናቸው ሲል ከሰሰ፤ እስራኤል ኤርትራውያንን በጅምላ ከማባረር እንድትቆጠብ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ጠየቀ። የድርጅቱንም መርህ መጣስ እንደሆነ አመልክቷል።

የፕሬዝዳንት ኢሳያስ አፈርወቂ መንግሥት ይህን ያለው በቅርቡ በእስራኤል መዲና ቴል አቪቭ በኤርትራ መንግሥት እና ተቃዋሚዎች መካከል ከፍተኛ ግጭት ተከስቶ በሰው እና በንብረት ላይ ጉዳት ከደረሰ በኋላ ነው። ከሁከቱ በኋላ የእስራኤል መንግሥት በተለይ የኤርትራ መንግሥትን ደግፈው በአደባባይ ሁከት የተሳተፉትን ጥገኝነት ጠያቂዎች ወደ አገራቸው አባርራለሁ ሲል ዝቷል።

ቅዳሜ ነሐሴ 27/2015 ዓ.ም. በቴል አቪቭ በነበረው ሁከት ኤርትራውያን ጥገኝነት ጠያቂዎች በሁለት ጎራ ተከፍለው ሁከት ፈጥረው በሰው እና በንብረት ላይ ጉዳት ከደረሰ በኋላ የአገሪቱ ጠቅላይ ሚንስትር አፍሪካውያን ስደተኞች በሙሉ ‘በአስቸኳይ’ ከእስራኤል ለማባረር እቅድ እንዲወጣ አዘው ነበር።

የእስራኤል ፖሊስ ሁከቱን ለመቆጣጠር ጥይት፣ አስለቃሽ ጭስ እና የፕላስቲክ ጥይቶችን በመቶዎች በሚቆጠሩ ኤርትራውያን ላይ ለመተኮስ ተገዷል። የባሕል ፌስቲቫሉን የሚቃወሙት ሥነ-ስርዓቱ ለአምባገነኑ የኢሳያስ አፈወርቂ መንግሥት ገንዘብ ማሰባሰቢያ ነው ይላሉ።

የኤርትራ መንግሥት ግን በኢንፎርሜሽን ሚኒስቴር በኩል ትናንት ማክሰኞ ነሐሴ 30/2015 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ “የኤርትራውያንን ብሔራዊ ማንነት የሚያስቀጥሉ ፌስቲቫሎች እንደ ሞሳድ ባሉ የእስራኤል ደኅንነት መሥሪያ ቤት የሚደገፉ ሁከት ፈጣሪዎች እንዲጨናገፍ እየተደረገ ነው” ብሏል።

ባለፉት ጥቂት ሳምንታት በአውሮፓ ከተሞች አና በሌሎች ስፍራዎች “በኤርትራውያን ማኅብረሰብ አባላት የተዘጋጁ ፌስቲቫሎች በተደራጁ ቡድኖች ሲታወኩ እና ንብረት ሲወድም ተመልክተናል” ብሏል የኢንፎርሜሽን ሚንሰቴሩ።

የኤርትራ መንግሥት “የእነዚህ ድርጊቶች ዋነኛ ዓላማ በውጭ አገራት የሚኖሩ ኤርትራውያን ለአስርት ዓመታት የዘለቀውን ማንነታቸው እና አገራዊ ትስስራቸውን ለማጠናከር የሚያደርጉትን ጥረት ማደናቀፍ ነው” ብሏል።

ሚኒስቴሩ የኤርትራ መንግሥት በመቃወም ከመንግሥት ደጋፊዎች ጋር ግጭት ውስጥ የገቡት ኤርትራውያን ጥገኝነት ጠያቂዎች የእስራኤል የደኅንነት ተቋም የሆነው ሞሳድን ጨምሮ በሌሎች የደኅንነት ኤጀንሲ ይደገፋሉ ይበል እንጂ ለዚህ ማስረጃ አላቀረበም።

ከቅርብ ግዜ ወዲህ የኤርትራ የባሕል ፌስቲቫል ዝግጅትን ምክንያት በማድረግ በኤርትራውያን መካከል በአውሮፓ እና አሜሪካ ከተሞች ግጭት ሲፈጠር መመልከት አዲስ ነገር አይደለም።

በዚህ ዓመት ብቻ በእስራኤል ጨምሮ በጀርመን፣ ስዊድን፣ ኖርዌይ እና በካናዳ ብዙዎችን ለጉዳት የዳረገ ግጭት ተከስቷል።

በርካታ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች የኤርትራ መንግሥት በዜጎቹ ላይ መጠነ ሰፊ የሰብዓዊ መብት ጥሰት ይፈጽማል ይላሉ።

በዚህም ምክንያት በኤርትራ ያለውን የፖለቲካ እና የእምነት ነጻነት ጭቆና እንዲሁም የጊዜ ገደብ የሌለውን አስገዳጅ የብሔራዊ አገልግሎት በመሸሽ በርካቶች ኤርትራውያን አገር ጥለው ይሰደዳሉ ሲል የዘገበው ቢቢሲ ነው።

እስራኤል ኤርትራውያንን በጅምላ ከማባረር እንድትቆጠብ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ጠይቋል።

የእስራኤል ባለሥልጣናት በዛቱት መሠረት ኤርትራውያን ጥገኝነት ጠያቂዎችን ከሀገሪቱ የሚያስወጡ ከሆነ፣ “ዓለም አቀፍ ሕግን እንደሚተላለፉ” እና ከፍተኛ ሰብዓዊ ችግር እንደሚያስከትልም ድርጅቱ ማስታወቁን ቲክቫህ አመልክቷል።

በኤርትራ መንግሥት ደጋፊዎች እና በተቃዋሚዎች መካከል፣ ባለፈው ቅዳሜ በቴል አቪቭ – እስራኤል በተፈጠረ ግጭት፣ በርካታ ሰዎች መጎዳታቸውንና ንብረት መውደሙን ተከትሎ፣ የአገሪቱ ባለሥልጣናት፣ በግጭቱ የተሳተፉ ኤርትራውያን ጥገኝነት ጠያቂዎችን ከሀገር እንደሚያስወጧቸው ዝተው ነበር፡፡

የኤርትራን 30ኛ ዓመት የነፃነት ቀን አስመልክቶ፣ በቴል አቪቭ ተዘጋጅቶ በነበረ ክብረ በዓል ላይ፣ የኤርትራ መንግሥት ደጋፊዎች በአንድ ወገንና ተቃዋሚዎች በሌላ ወገን ተሰልፈው በተፈጠረ ኀይል የተቀላቀለበት ግጭት ዐያሌዎች ተጎድተዋል።

የፖሊስ አባላትም ጉዳት እንደደረሰባቸው ለማወቅ ተችሏል፡፡

የተፈጠረው ግጭት እጅግ እንዳሳሰበው የተመድ የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽነር ገልጾ፣ መረጋጋት እንዲኖር እና ሁለቱም ወገኖች ሁኔታውን ከማባባስ እንዲቆጠቡ ጠይቋል።

ባለፈው ሰኔ በወጣ መረጃ፣ 17 ሺሕ 850 ኤርትራውያን ጥገኝነት ጠያቂዎች በእስራኤል እንደሚገኙ ታውቋል።

በግጭቱ 170 ጥገኝነት ጠያቂዎች እና በደርዘን የሚቆጠሩ የእስራኤል ፖሊስ አባላት እንደተጎዱ የስደተኞች ኮሚሽኑ ገልጿል።


Exit mobile version