Site icon ETHIO12.COM

የባቢሌ የዝሆኖች መጠለያ ለኢንቨስተሮች መሰጠቱን የተቃወሙ ሦስት ምሁራን ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ደብዳቤ ጻፉ

“እሳቸው ይሄንን ነገር ሰምተውታል ብዬ አላስብም። ከሰሙ እንደሚያስቆሙት እርግጠኛ ነኝ” 

ከአምስት አስርት ዓመታት በላይ ያስቆጠረው የባቢሌ የዝሆኖች መጠለያ ከፊል ስፍራ ተቆርሶ ለግብርና ኢንቨስተሮች መሰጠቱ ያስቆጣቸው ሦስት ምሁራን ለጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ደብዳቤ ጻፉ።

የባቢሌ ፓርክ ደን ተመንጥሮ ለኢንቨስተሮች መሰጠቱ ከፍተኛ የድርቅ አደጋ እንደሚጋርጥ በመግለጽም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጣልቃ እንዲገቡ ምሁራኑ በደብዳቤያቸው ጠይቀዋል።

በኢትዮጵያ ትልቁ የዝሆኖች መጠለያ የሆነው እና በምሥራቅ ሐረርጌ የሚገኘው የባቢሌ ፓርክ ለኢንቨስተሮቹ መሰጠቱ ለዝሆኖቹ ብቻ ሳይሆን ለሕዝቡም አደጋ መሆኑን ምሁራኑ ይናገራሉ።

ደብዳቤውን የጻፉት በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የብዝኃ ሕይወት ተመራማሪ ዶክተር ሃብቴ ጀቤሳ፣ የአካባቢ ጥበቃ ከፍተኛ ባለሙያ ዶክተር አዳነ ፀጋዬ እና ዶክተር አዲሱ አሰፋ ናቸው።

ፓርኩ የደን ምንጠራ ማካሄድ ከፍተኛ የድርቅ አደጋ ሊያስከስት እንደሚችልም ዶክተር ሃብቴ ያስረዳሉ።

“በፓርኩ ውስጥ ያለው ስፍራ ተጋላጭ አካባቢ ነው። ደን ምንጠራ ማካሄዱ በቅርብ ጊዜ ማገገም አይቻልም። ለበረሃነት፣ ለድርቅ የተጋለጠ ነው። ለዝሆኖቹ ብቻ ሳይሆን ሕዝቡን እጅግ አደገኛ የድርቅ ስጋት ውስጥ ይጥለዋል”ብለዋል።

እየተመነጠረ ያለው ደን በመቶ ዓመታት ውስጥ እንኳን ማገገም እንደማይችል እና የአካባቢ ተጽእኖ ግምገማም እንዳልተደረገበትም ነው ምሁሩ የገለጹት።

በተለይም ኢትዮጵያ ከተጋረጠባት የድርቅ አደጋ ጋር ተያይዞም ችግሩን የበለጠ ያከፋዋል ይላሉ።

በሐረርጌ አካባቢ በድርቅ ምክንያት 80 ሺህ ሕዝብ መፈናቀሉንም ጠቅሰው “በዚህ አካባቢ እንዴት ነው ደን የሚመነጠረው? እጅግ የሚያሳዝን ነው” በማለት በድርጊቱ የተሰማቸውን ሐዘን ለቢቢሲ ገልጸዋል።

ለጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ በዋነኝነት ደብዳቤ ለመጻፍ ያነሳሳቸው አንደኛው ጉዳይ የአረንጓዴ አሻራ በሚል ከሚያደርጓቸው የአካባቢ ጥበቃ ጋር በተያያዘ እንደሆነም ይናገራሉ።

በፓርኩ እየተከናወነ ያለውም ከጠቅላይ ሚኒስትሩ የደን ልማት እና የአካባቢ ጥበቃ ተግባር ጋር “የሚጋጭ ነው” ሲሉም ዶክተር ሃብቴ ያስረዳሉ።

“እሳቸው ይሄንን ነገር ሰምተውታል ብዬ አላስብም። ከሰሙ እንደሚያስቆሙት እርግጠኛ ነኝ” ብለዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ የባቢሌ ፓርክ የደን ምንጠራ ጉዳይ ከሰሙ አቅጣጫ ሰጥተው ያስቆሙታል “በሚል ትልቅ ዕምነት” ደብዳቤ መጻፋቸውንም አስረድተዋል።

በፓርኩ ውስጥ በአሁኑ ወቅት የደን ምንጠራ እየተካሄደ እንደሆነ እና የዱር እንስሳት ጥበቃ ልማት ሠራተኞች (ሬንጀሮች) እንደተባረሩ እንዲሁም መደብደባቸውንም እንደሰሙ ዶክተር ሃብቴ ለቢቢሲ ተናግረዋል።

“እንደሰማነው መከላከያ ነን በሚሉ የመከላከያ መለዮ በለበሱ እና ማንነታቸው በማይታወቁ ሰዎች ተወስደው ተገርፈዋል። ከፓርኩም ተባርረዋል” ብለዋል ዶክተር ሃብቴ ።

ቢቢሲ ከጥቂት ሳምንታት በሰራው ዘገባ ለልማት ተፈቅዶልናል ያሉ ባለሃብቶች ዶዘር አስከትለው በመሄድ ወደ ፓርኩ ለመግባት ሲሞክሩ በዝሆኖቹ መጠለያ ጠባቂዎች በመከልከላቸው ግጭት መፈጠሩን አመልክቶ ነበር።

በዚህም ሳቢያ በተወሰኑ መንግሥት የመደባቸው እና ሕጋዊ የደንብ ልብስ በለበሱ የዱር እንሰሳት ጥበቃ ልማት ሬንጀሮች ላይ ድብደባ እንደተፈጸመባቸው ተናግረዋል።

የኢትዮጵያ ዱር እንሰሳት ጥበቃ ባለሥልጣንም ድርጊቱ ዝሆኖችን ለአደጋ የሚያጋልጥ እና አኗኗራቸውን የሚያናጋ በመሆኑ ከኦሮሚያ ክልል ጋር በመሆን የፓርኩ ደኅንነት ለማስከበር እየሠራ መሆኑን ገልጿል።

ስፋቱ 6980 ካሬ ኪሎ ሜትር የሆነው የባቢሌ የዝሆኖች መጠለያ ውስጥ ለእርሻ ልማት በሚል በባለሃብቶች እየታረሰ ነው የተባለው ቦታ በፓርኩ ሰሜናዊ ክፍል ኤረር ሸለቆ በሚባለው ስፍራ ያለ ነው።

ባለሃብቶች በተለይ ለእርሻ፣ ለከብት ማደለቢያ እና ለንብ እርባታ አካባቢውን ይፈልጉታል። በዋናነትም ስፍራው ከ50 ዓመታት በላይ በመንግሥት እጅ ስለቆየ ጥብቅ እና ለም መሬት ስለሆነ እንዲሁም ወንዝ ዳር በመሆኑ ውሃ በቀላሉ ማግኘት ስለሚችሉ ባለሃብቶች ዐይናቸውን እንደጣሉበት ባለሙያዎች ይናገራሉ።

ቢቢሲ አማርኛ


Exit mobile version