Site icon ETHIO12.COM

ኢትዮጵያ በተራራ የተከበበች መሆኗ ዳመና አዝናቢ ኬሚካልን ወደ አየር ለመልቀቅ ምቹ መሆኑ ተገለጸ

ኢትዮጵያ በተራራ የተከበበች አገር መሆኗ ዳመና አዝናቢ ኬሚካልን ወደ አየር ለመልቀቅ የተሻለ ዕድል እና ምቹ ሁኔታ እንደሚፈጥር የብሔራዊ ሚቲዎሮሎጂ ኤጀንሲ ምክትል ዋና ዳይሬክተር አመለከቱ።

ምክትል ዋና ዳይሬክተሩ አቶ ክንፈ ኃይለማርያም በተለይ ለአዲስ ዘመን እንዳስታወቁት፣ ኢትዮጵያ የመልክአ ምድሯ መለያየት የሚታይባት፤ ተራራማ አካባቢዎች የሚበዙባት መሆኗ ዝናብ አምጪ ኬሚካሎችን ወደ ደመና ልኮ ለማበልጸግ ምቹና ሰፊ ዕድል ይፈጥራል።

አገሪቱ ከቦታ ቦታ የተለያየ የአየር ጸባይ ያላት እንደመሆኗ ፣ አንዳንድ ጊዜ በበልግም አልያም በክረምት በቂ ደመና እያለ ዝናብ የማይዘንብባቸው ጊዜያት አሉ ያሉት አቶ ክንፈ፣ አንዳንዴም ክረምት ሆኖ ዝናቡ በበቂ ሁኔታ ላይገኝ የሚችልበት ሁኔታ ይፈጠራል። በክረምትም ደረቃማ የአየር ሁኔታ የሚፈጠርበት ጊዜ አለ። ቴክኖሎጂው በእነዚህ ወቅቶች ደመናውን ወደ ዝናብ ለመቀየር ከፍተኛ ጠቀሜታ እንዳለው ጠቁመዋል።

እስከ አሁን ቴክኖሎጂውን ከ50 የማያንሱ አገራት ተግባራዊ እያደረጉት እንደሚገኙ ያመለከቱት አቶ ክንፈ፣ ከዚህ አንጻር እኛም ወደዚህ ቴክኖሎጂ ለመግባት ጉዞ መጀመራችን ወሳኝና አስፈላጊ ነው ብለዋል ።«ይህ ቴክኖሎጂ እንደ ታዳጊ አገር ብሎም በምግብ እህል ራስን ለመቻል ጥረት ላይ እንደመሆናችን ጥቅሙ ከፍተኛ ነው፤ ውሃ የብዙ ነገሮች መሠረት ከመሆኑ አንጻር ይህንን ቴክኖሎጂ በማበልጸግና በማሳደግ ለግብርና ሥራ ለመስኖ አቅርቦት እንዲሁም የውሃን ክምችት ለማሳደግ ወሳኝ ነው፤ ለአገራችን ልማትና ብልጽግና የጎላ ሚናን እንደሚጫወት ሃላፊውን ጠቅሶ የዘገበው ኢ ፕ ድ ነው።


Exit mobile version