Site icon ETHIO12.COM

መንግስት ከስድስት ዓለም አቀፍ ድርጅቶች ጋር በመተባበር በትግራይ ክልል የሚሰጠው ሁሉን አቀፍ ድጋፍ ተጠናክሮ መቀጠሉ ተገለፀ


በትግራይ ክልል ድጋፍ ከሚደረግላቸው 92 ወረዳዎች አለም አቀፍ ድርጅቶች 86 ከመቶውን ወረዳዎች በራሳቸው እየተንቀሳቀሱ ሽፋን መስጠት መቀጠላቸውን ገልፀዋል።

ይህ ተገለፀው በዩናይትድ ኪንግደም የዓለም አቀፍ የፖሊሲ ጥናትና ምርምር ቻታም ሀውስ ከለንደን የኢትዮጵያ ኤምባሲ ጋር በመተባበር ባዘጋጀው የዌብነር ውይይት ላይ ነው።

በመድረኩ ዓለም አቀፍ የሰብአዊ ድጋፍ ሰጪ ድርጅት ስራ አስፈጻሚዎች ፣በሰብአዊ መብት ላይ ሚሰሩ ዓለም አቀፍ ተቋማት ፣በዩናይትድ ኪንግደም መንግስት አፍሪካ ተኮር የልማት ድርጅት ሃላፊዎች ፣ አለም አቀፍ የመገናኛ ብዙሃን ፣ አለም አቀፍ የግጭትና ቀውስ ትንተና ባለሙያዎች እና አፍሪካ ላይ ትኩረት አድርገው የሚሰሩ ተቋማት ተሳትፈዋል።

በዌብነር ውይይቱ ላይ የተገኙት የብሔራዊ የአደጋ ሥጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን ኮሚሽነር አቶ ምትኩ ካሳ በሰጡት ማብራርያ በትግራይ ክልል የህግ ማስከበር እርምጃው መጠናቀቅን ተከትሎ በተደረገው የመጀመሪያ ዙር ለ 4.5 ሚሊዮን ዜጎች የምግብ ና ምግብ ነክ ያልሆኑ ድጋፎች መደረግ ተችሏል።

በሁለተኛው ዙርም ለ 2.7 ሚለዮን ዜጎች በተመሳሳይ ድጋፉ መቀጠሉንም ኮሚሽነር ምትኩ ገልፀዋል ፡፡ ከዚህ ድጋፍ ውስጥ 70 ከመቶው ከመንግስት 30 በመቶው በዓለም አቀፍ ድርጅቶች የተሸፈነ ነው ፡፡ እየተደረገ ላለው ሰብአዊ ድጋፍ መንግስት ከ 3.7 ቢሊዮን ብር በላይ ወጪ ማውጣቱን ተናግረዋል ፡፡

ኮሚሽነር ምትኩ በአሁኑ ወቅት በትግራይ ክልል ድጋፍ ከሚደረግላቸው 92 ወረዳዎች አለም አቀፍ ድርጅቶች 86 ከመቶውን ወረዳዎች በራሳቸው እየተንቀሳቀሱ ሽፋን መስጠት መቀጠላቸውን ገልፀዋል።

ከዚህ በፊት ፍቃድ ማግኘት የሚጠይቀው ሂደት አሁን ሙሉ በሙሉ ለሰላም ሚንሰቴር በማሳወቅ ብቻ እርዳታ ሰጪዎችም ሆነ መገናኛ ብዙሃን ወደክልሉ እንደሚገቡ አረጋግጠዋል ፡፡

በአሁኑ ወቅት በመቀሌ ማዕከል በማቋቋም ማንኛውም እርዳታ በቅርበት ለወረዳዎች እንዲዳረስ እየተደረገ መሆኑን ኮሚሽነር ምትኩ አስተውቀዋል።

በጤና ሚንስቴር በእርዳታ የተሰጡ የህክምና መሳሪያዎች መድሃኒቶች እና አምቡላንሶች ከክልሉ ጤና ቢሮ ጋር በመተባበር በየወረዳው የተንቀሳቀሽ ህክምና ማዕከል አቋቁመው አስፈላጊውን ድጋፍ እተደረገ መሆኑንም ተናግረዋል ፡፡

መንግስትና አለም አቀፍ እርዳታ ሰጪ ድርጅቶች በገቡት የማስተባበርና የሰብአዊ እርዳታን የማቅረብ ውል መሰረት ከፍተኛ ትኩረት ሊሰጥ የሚገባቸው ከ 5 አመት በታች ለሆኑ ህፃናት እና ለነፍሰ ጡር ሴቶች የሚደረገው የአልሚ ምግብ ድጋፍ ተጠናክሮ እንዲቀርብ ለእርዳታ ሰጪዎች ጥሪ አቅርበዋል ፡፡

የተፈናቀሉ ዜጎችንም አለም አቀፍ መርሁ በሚጠይቀው መሰረት መልሶ የማቋቋም ስራው ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ተናግረዋል ፡፡

በህወሃት የወደሙ የኢኮኖሚና የማህበራዊ መሰረተ ልማቶች መልሶ የመገንባት ስራም እንደሚጀመር ተናግረዋል ፡፡

ለሰብአዊ እርዳታ የሚሆኑ መንገዶች እና አማራጮችን በሙሉ መንግስት ክፍት አድርጎ ዓለም አቀፍ ተራድኦ ድርጅቶችንም እያስተናገደ እንደሚገኝ ያስረዱት ኮሚሽነር ምትኩ የመከላከያ ሰራዊትም የተሽከርካሪ እጀባ እና የጸጥታ ጥበቃ በማድረግ ለሰብአዊ ድጋፊ አስተዋጽኦ እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል።

ተቀማጭነታቸው በኢትዮጵያ የሆኑት የተመድ ቋሚ ተጠሪና የሰብአዊ ድጋፍ አስተባባሪ ካትሪን ቦሴ በበኩላቸው ያጋጠሙት ችግሮች ፈታኝ ቢሆኑም ከመንግስት ጋር ተባብሮ በመስራት ፈተናዎቹን ማለፍ እንደሚቻል አስረድተዋል፡፡

የድንበር የለሽ ሃኪሞች ዳይሬክተር ጀነራል ኦሊቨር በህን በበኩላቸው ችግሮች ቢኖሩም መንግስት ለአለም አቀፍ ተራድኦ ድርጅቶች ወደ ክልሉ በፈለጉት ጊዜ እንዲገቡ የፈቀደ መሆኑ ሊመሰገን እንደሚገባው ተናግረዋል።

የእርዳታ አቅርቦቱ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ጥሪ አቅርበዋል ፡፡

ምንጭ ፦በለንደን የኢትዮጵያ ኤምባሲ EBC

Exit mobile version