Site icon ETHIO12.COM

እንቡዝ

እንቡዝ ሰው የሚሠራውንና የሚናገረውን በጤነኛ አእምሮ መረዳት አይቻልም። ጤነኛ አእምሮ በተጠየቅ፣ በሞራል ሕግ፣ በመረጃ፣ በማስረጃ፣ በሐሳብ ሙግት፣ ወዘተ. ነው የሚረዳው። እንቡዝ ጋ ይህ ሁሉ የለም። መቅበዝበዝ፣ መስከርና ማበድ አንድ ላይ ሆነው የሚፈጥሩት ሰብእና ነው።

በገድለ ተክለ ሃይማኖት የምናገኘው ሞተለሚ የተባለው የዳሞት ንጉሥ ለ25 ዓመታት እንቡዝ ሆኖ መኖሩን ይነግረናል። እንቡዝ የሚለውን ኪዳነ ወልድ ክፍሌ ሲተረጉሙት፦ በቁሙ ልቡ የጠፋ፣ የተነበዘ፣ ነባዛ፣ ንብዝ፣ ቅብዝብዝ፣ ሰካር፣ እብድ፡፡ ሰብእ እንቡዛን፡፡ ብእሲት እንብዝት፡፡ እንቡዛነ ልብ ወድንቅዋነ እዝን (ኢሳ፳፭፡ ፭፡፡ ፶፬፡ ፮፡፡ መጽ፡ ምስ) ይሉታል። “ቅብዝብዝ ሰካር፣ እብድ” በሚሉት ነው አለቃ ለመበየን የሞከሩት።

ፕሮፌሰር ጌታቸው ኃይሌ የአቡነ ተክለ ሃይማኖትን ታሪክ በጻፉ ጊዜ ሁሉ “እንቡዝ” የሚለውን “Insane” ብለው ነው የሚተረጉሙት። ኦክስፎርድ የእንግሊዝኛ መዝገበ ቃላት “Insane” የሚለውን ሲፈታ “in a state of mind which prevents normal perception, behaviour, or social interaction; seriously mentally ill.”
ይላል።

ሞተለሚ እንቡዝ ከሆነ በኋላ ያደረገው ነገር ይሄንን ትርጉም ያጠናክረዋል። ሥራው ያገኘውን ሁሉ ማጥፋት ነበር። ዓለም ልትጠፋ የሚገባት፣ ነገር ግን በደካሞች ምክንያት ሳትጠፋ የቀረች ትመስለው ነበር።

እንቡዝን ለመግለጥ አለቃ ኪዳነ ወልድ የተጠቀሙባቸውን ቃላት መመርመር የተሻለ ነገሩን ያሳየናል። መቅበዝበዝ – የመንፈስ አለመረጋጋት ነው። ይሄንን መጀመሪያ የተጠቀመው ቃየል ነው። ቃየል ወንድሙን በግፍ ከገደለ በኋላ መንፈሱ ያልተረጋጋ በመሆኑ ቅብዝብዝ ነበር። ወያኔም ገና ከጅምሩ መንገዱ የቃየል ነበር። ሰካር የአእምሮ መናወዝ ነው። በተጠጣ አስካሪ ነገር የሚመጣ ነው። ወያኔ ጎሰኝነት የሚባል አስካሪ መጠጥ ወስዷል። እብደት የልቡና መናወጽ ነው። ሥነ ልቡናዊ በሽታ ነው።

እንቡዝ ሰው የሚሠራውንና የሚናገረውን በጤነኛ አእምሮ መረዳት አይቻልም። ጤነኛ አእምሮ በተጠየቅ፣ በሞራል ሕግ፣ በመረጃ፣ በማስረጃ፣ በሐሳብ ሙግት፣ ወዘተ. ነው የሚረዳው። እንቡዝ ጋ ይህ ሁሉ የለም። መቅበዝበዝ፣ መስከርና ማበድ አንድ ላይ ሆነው የሚፈጥሩት ሰብእና ነው።

ወያኔ እንቡዝ ስለሆነ ለጤነኛ ሰው የሚሰጡ ነገሮች አይስማሙትም። የሚናገረውና የሚሠራው ከሰብእና ውጭ የሆነው በንብዘቱ ምክንያት ነው። ለምን አደረገ? ብትሉ ንዴቱ እናንተን ያሳምማችኋል እንጂ ወያኔ አይሰማውም። ያንን ሁሉ ጥፋት ሠርቶ፣ ያንን ሁሉ ወጣት አስፈጅቶ ፈገግ ይላል። ለምን ቢሉ? እንቡዝሰ እንቡዝ ውእቱ። እንቡዝ ምን ብታደርጉት እንቡዝ ነው።

By Daniel kebret

Exit mobile version