Site icon ETHIO12.COM

[የሽግግር መንግስት] ሊቋቋም ነው !!

ከከፍተኛ ጭቅጭቅ፣ ከከፍተኛ ንትርክ፣ ከከፍተኛ ትንቅንቅ በሁዋላ የብልጽግና የስራ አስፈጻሚ የሽግግር መንግስት እንዲቋቋም መወሰኑ ሾልኮ በወጣ አፈንጋጭ አማካይነት ይፋ ሆኗል። እንደ አፈንጋጩ ገለጻ የሚቋቋመው የሽግግር መንግስት ውስጥ በአገር ውስጥ ያሉም ሆነ በውጭ አገር ያሉ አማጽያን፣ ፖለቲከኞች፣ የዩቲዩብ ሰዎች፣ ፓርቲዎች፣ አስፈላጊ ከሆነ ግለሰቦች እገሌ ከእገሌ ሳይባሉ ይሳተፉበታል። የመንግስት ምስረታው የሚካሄደበት ቀን ሲቆረጥ በተቃዋሚ ፓርቲ ልሳኖችና ዩቲዩቦች፣ የቴሌግራም ቻናሎች ማስታወቂያው እንዲሰራጭ ይደረጋል።

አገር ፍቅር ቲያትር በአንድ ብር ሁለት የህንድና አንድ የአሜሪካ ፊልም በሚታይበት ዘመን የተቃጠለ አራዳ የሚባሉ ፣ ሲኒማ አዲስ ከተማ በሽልንግ ሽንት አናታቸው ላይ እየተሸናባቸው ፊልም ያዩ የነበሩ ቴክሶች፣ አሁን ድረስ ሲኒማ አዳዋ / ሴጣን ቤት አለ የሚሉ/ አያሌው ሙዚቃ ቤት ጎን ባቅላባ በልተው ተክሉ ደስታ ወርቅ በመስኮት ሾፈው የሚመረቅኑ፣ የድላችን ሃውልት ሳይቆም፣ጎንደር በጌ ምድር፣ ጀግጅጋ ጅጅጋ ሲባል ከአገር የወጡ… ዜያድባሬ የሶማሌ መሪ የሚመስላቸው… ተሳታፊ ናቸው።

አሰብ ራስ ገዝ ሲባል ያልነበሩ፣ በአስራ አራት ጠቅላይ ግዛት ሙዚቃ ያደጉ፣ አሁን ድረስ አፈሳ ያለ የሚመስላቸው፣ መፈክር ሲጽፉበት የነበረውን ብሩሽና የቀይ ቀለም ገረወያና ያልጣሉ፣ ስብሰባ ሲጠሩ አሁን ድረስ “ወረቀት ይበተን” የሚሉ፣ አዲስ አበባ ግራጫ ቀለም ትቀባ ሲብላ “ቀይ ቀለም ወይም ሞት” የሚሉ፣ አቃቂ በሰቃ ዘመድ ለመጠየቅ ከፈረንሳይ ሲነሱ ቤተዘመድ፣ ወዳጅ፣ ጓደኛ ተሰናብተው በሽኝት ተላቅሰው ሲለያዩ የነበሩ፣ አውቶቡስ ላይ ሽቅብ ሽቅብ እያላቸው ጤናዳም የሚይዙ፣ የአክፋይ ግድንግድ ድፎ ዳቦ ጸሃይ እንዳይመታው በዣንጥላ ተሸፍኖ ሚስት ተሸክማ፣ ባል ፋሽኮ ቪኖ ወይም እናትና ልጅ ኡዞ ይዘው ሲባዝኑ በሚውሉበትና በሚያመሹበት ዘመን አገራቸውን የተሰናበቱ … አሉበት!!

ፓስታ ለመጀመሪያ ጊዜ አዲስ አበባ ሲገባ ” ፓስታ ገባ ገባ” መዝሙር የዘመሩ፣ ጉለሌ ሳሙና 777 የመጀመሪያ ምርቱን ለገበያ ሲያቀርብ በተርፍላይ አስረው በቁምጣ ተነፋነፍ የምርቱን ብስራት ያስተዋወቁ … የበግ ቆዳ ሶስት ሽልንግ ገዝተው ያተረፉ፣ የዛ ዘመን ባለ ቤልቦልት ለባሾች፣ የዘመኑ ኤልቪሶች፣ በዲናሬ የሾረቱ… በወረቃ አዳር የተስተናገዱ፣ ትኩዬ በዱዲ የጨረገዱ … በዛ ዘመን አገራቸውን የተሰናበቱ ይጋበዛሉ።

ለጥምቀት ሲነፉት የነበረውን አርሞኒካ እንደያዙ ያሉ። ለጥምቀት የገዙትን ሎሚ ሳይወረወሩ ከአገር ወጥተው ሎሚው አሁን ድረስ እጃቸው ላይ የደረቀባቸው፣ ጃንሜዳ ክብ ክብ እየሰሩ ሲያስነኩ የነበሩ፣ ጥምቀት በዓመት ሁለቴ እንዲሆን የሚመኙ … ግንፍሌ ወንዝ ሻወር ወስደው ሲጆልሉ የነበሩ፣ ስታዲየም “ጋሼ ልጄ ነው” በሉ እያሉ ሲገቡ የነበሩ … በዛው ስሜት አሁን ድረስ ያሉ … አንበሳ ግቢ ተቀታጥረው ደስታ ከረሜላ እየላሱ ሲጣበሱና በአንበሳ ድምጽ ሙድ ሲያዙ የነበሩ ከፊት ረድፍ ይቆማሉ።

ያበደው ከህልሙ ነቃ … ህልሙን ለቦሰና ነገረ። “የሽግግር መንግስት ምስረታው እነዚህን ሁሉ ካካተተ ሁሉንም የሚውጥ አዳራሽ እስከሚገነባ ምን ሊሆን ነው?” ስትል የብልህ ጥያቄ አነሳች። መልሳ መጀመሪያ ራሳቸው ሽግግር እንዲያደርጉ አሳብ አቀረበች። ደጎል ስሪያ ሄዷል መስለ የለም። የውሻ ነገር … እናቱ ላይ በደቦ ቂብ ብሎ ያለከልካል። ከውሾች ክፉ ተፈጥሮ ይህ ነው … ያበደው አንዳንዴ ይወሰዳል። ጣቢያ ይቀላቅላል…

ሰላምታዬ ቢዘገይም እንሆኝ። መጀመሪያ ለሞተ ነብስ ይማር። ስድስት ልጆች በትኖ ለሄደ ነብስ አንድዬ ፍርድን ያምጣ። ወንድም ወንድሙን በላ። ልክ ውሻ እናቱ ላይ እንደወጣው … የአንድ ቀበሌ ልጆች ተጨካከኑ … ስድስት ልጆችና በዙሪያው ያሉ ሁሉ ሲያድጉ በምን ስሜት እንደሚያድጉ አሁንም አንድዬ ይወቀው? ህመም ነው። ከቀኝም ከግራም ውጋት ነው። ወደ ሁዋላ እንጂ ወደፊት የለም። “ገደሉት” ያሉ ቤተሰቦች፣ ሚስቶች፣ ልጆች ይህን ታሪክ መዝግቡ!! የነ አማባቸውና ምግባሩም አለ!! የወደፊቱን የሚያውቅ የለም …

እነዚያ በጥንቱ ዘመን ኢትዮጵያን የተሰናበቱ ያስቃሉ። በነሱ ማዘን በራስ መጭከን ነው። አንዱ በሃምሳ ዓመቱ አዲስ አበባ መጣ። ቤተሰቦቹ ወደ መተማ ናቸው። አዲስ አበባ ደርሶ ወደ መተማ ለመሄድ ” ፈራሁ” አለና ካርቱም በረረ። ከካርቱም ወደ መተማ ሄደ። ይህ እውነት ነው …. ያበደው ተስፈነጠረ … አሁን ጥያቄው እነዚህ ተሰብስበው ምን አይነት ሽግግር ይካሄዳል?

“እናንተ የሽግግር መንግስት ናፋቂዎች መጀመሪያ ራሳቸሁ ተሻገሩ” እያለ ጮኸ። አዎ ተቸክለናል። ባለንበት እንደወፍጮ አመድ ለብሰናል። አድርቶብናል። ነትበናል። መጀመሪያ ድሩን መበጣጠስ፣ አመዱን ማራገፍ ግድ ነው። አለያ ጠንቋዩም፣ ባለ እንዳርቢውም፣ ብሄርተኛነት አዋቂ ያደርገው አንዛራጭ መጫወቻ ከመሆን አንድንም። እኛ ሳንሸጋገር እንዴት ሽግግር ይሆናል?

አፍረት … ኢትዮጵያን ሳያይ 50 ዓመት የቆየ፣ አርባ አመት የሞላው፣ ሰላሳ ዓመት የሞላው … እንዴትና በምን አመክንዮ ራሱን ተከላክሎ ከዩቲዩብ ግብር ሰብሳቢዎች ራሱን ይጠብቃል? ገበያውን ከማድመቅና ኪሱን ከመገልበጥ እንዴት ይጠበቃል? ቦሰና አጎቷን ” ዝም ብለህ አታላዝን ናና ተመልከት” ብላለች። “ሰላም ናችሁ?” እያለ ኮሽ ባለ ቁጥር ሲደውል መልሷ ” ናና እየው” ነው።

ኦነግ ዛንዚባር ከትሟል። የኦነግና መንግስት ንግግር ስጋት ፈጥሯል። ስጋቱ እሌቦቹ መንደር ውስጥ ነው። ስንተራመስ የሚቦጠብጡን ኮንትሮባንዲስቶችም ከወዲሁ “ድርድሩ ይፍረስ” እያሉ ስለት እያስገቡ ነው። ለሚከፍሏቸው በጀት አሳድገዋል። ግን የተነቃ መሆኑንን ቦሰና ሰምታለች።

ቦሰና “ይገርማል” ብላ ቀለም የገባው አጎቷ የነገራትን ዘረገፈች። አንድ ሉዓላዊ አገር እንዴት ያለ አንድ የሚታወቅ የዶላር ገቢ አርባ ዓመት ይኖራል። እንዴት ማዕቀቡን ይቋቋማል? እንዴት ተብሎ? ….. አውሮፓና አሜሪካ፣ ካናዳና አውስትራሊያ ዶላር የሚለቅሙትና በኢትዮጵያ ስም ድርጅት ከፍተው ምንዛሬ የሚያከማቹትን ትቶ፣ “መንግስት በውጭ አገር ዶላር መሰብሰብ ጀመረ” ዜና ይሆናል? ምን ጥላቻ ቢኖር እንዴት ሌሎች ይበልጡብናል? ቦሰና . …

የበደው ሁሉንም ገጣጠመ። የመቸከል በሽታ ከቤርተኛነት ጋር ሲዳመር አቅል ያሳጣል። እንደ አዳል በግል ለመነዳት ይዳርጋል። ወገኖቹ ላይ የኢኮኖሚ ሞት ለሚያውጁ ግብር ከፋይ ያደርጋል። …. ያበደው “ንቁ” ይላል። የመከራ አይነት ተፈራርቆብናል። አሁንም ግን የበቃን አይመስልም። ሰላምን እየረግምን ያለነው ምን አምሮን እንደሆነ የገባችሁ ወዲህ በሉን። ሰላም ለሰላም አዋላጆች፣ ትግራይ በርዳለች። አማራን ለማንደድ የተሰማራችሁ ከትህነግ አመድ መሆን ተማሩ!! አሁን ጊዜው የቦሰና ነው። ቦሰና ካናጫት ጉዳዩ ነው። እንክብካቤ ትሻለች። ይገባታል። ጥሪ ስትቀበልም፣ ሳትቀበልም ትታቀፋለች። ደጎል ዛሬ ቤቱ አይገባም። እያደራው ነው !!

Exit mobile version