ETHIO12.COM

እንጀራን ኢንዱስትራላይዝ የሚያደርግና በሀገሪቱ የመጀመሪያ የሆነው ማዕከል ተመረቀ

ሚያዝያ 23/2015 (ዋልታ) በቀን 288 ሺሕ እንጀራ የሚጋገርበትና እንጀራን ኢንዱስትራላይዝ የሚያደርግና በሀገሪቱ የመጀመሪያ የሆነው ማዕከል ተመረቀ፡፡

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ በማኅበራዊ ትስስር ገፃቸው ማዕከሉን ገንብተን ከመላው የሀገራችን ከተሞች ከመጡ ከንቲባዎች ጋር በመሆን መርቀናል ብለዋል፡፡

እንጀራን ኢንዱስትራላይዝ በማድረግ በሃገራችን የመጀመሪያ የሆነው ለሚ እንጀራ ማዕከል የእናቶችን ድካም የሚያቀልና እንጀራን ከፍ ባለ ደረጃ ማምረት የሚያስችል ማዕከል ሲሆን ከፈተናዎቻችን በላይ ሆነን የማይቻል የሚመስለውን የመቻላችን ማሳያ ነው ሲሉም አክለዋል::

በየቦታው ያለንን አቅም፣ ገንዘብ እና እውቀት በማስተባበር የነዋሪዎችን ሸክም የሚያቀሉ ፕሮጀክቶችን በመንደፍ እየተገበርን ሲሆን የእንጀራ ማዕከሉ ከ2000 እናቶች በተጨማሪ በተለያዩ የስራ መስኮች ለ1000 ነዋሪዎች በጠቅላላው 3000 ለሚሆኑ ወገኖች የስራ እድል የሚፈጥር ነውም ብለዋል፡፡

በዚህ የእናቶችን ሸክም በዘላቂነት በሚያቀልለው ታላቅ ስራ ላይ ያገዙን ልበቀና ባለሃብቶችን በተለይም ኦቪድ ግሩፕ 170 ሚሊዮን፣ ሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ 75 ሚሊዮን፣ መድህን ድርጅት 20 ሚሊዮን ብር፣ መታሰቢያ ታደሰ ኮንስትራክሽን 500 ዘመናዊ ምጣዶችን በማቅረብ እንዲሁም የታፑ ምግቦች በማማከር ላደረጉት አስተዋጽዖ በእናቶቹ ስም አመሰግናለሁ ሲሉም ገልጸዋል፡፡

WWCC

Exit mobile version