Site icon ETHIO12.COM

የመኪና ሌቦቹ ተፈረደባቸው

ከጥበቃ ሰራተኞች ጋር በመመሳጠር ሁለት ተሽከርካሪዎችን የሰረቁ እና ወንጀሉን ያስተባበሩ የወንጀል ፈፃሚዎች በፅኑ እስራት ተቀጡ፡፡ የተሰረቁት ተሽከርካሪዎች ሰሌዳቸው ተቀይሮ መገኘታቸውን የአዲስ አበባ ፖሊስ አስታውቋል፡፡

በአራዳ ክፍለ ከተማ ከሚገኘው የአዲስ ብድርና ቁጠባ ተቋም ውስጥ ሁለት የድርጅቱ ተሽከርካሪዎች መጥፋታቸው ለአራዳ ክፍለ ከተማው ፖሊስ መምሪያ መረጃ ይደርሰዋል፡፡

የድርጅቱ የጥበቃ ሰራተኞች ከወንጀል ፈፃሚዎች ጋር በመመሳጠር ሌሊት ተረኛ በነበሩበት ወቅት ሐምሌ 30 ቀን 2013 ዓ/ም የተቋሙን የስምሪት ክፍል ኃላፊ ቢሮ በር በፌሮ ብረት በመገንጠል አይነቱ ቶዮታ ፒካፕ የሰሌዳ ቁጥሩ ኮድ 3A 05319 አ/አ የሆነ ተሽከርካሪ ቁልፍን በመውሰድ እንዲሁም የሰሌዳ ቁጥሩ ኮድ 3A 07587 አ/አ የሆነ ቶዮታ ሚኒባስ ተሽከርካሪ ቁልፍ መኪናው ውስጥ ተሰክቶ በማግኘታቸው ሁለቱንም ተሽከርካሪዎች ሰርቀው ቢሰወሩም የአራዳ ክ/ከተማ ፖሊስ መምሪያና በአዲስ አበባ ፖሊስ ወንጀልና ትራፊክ አደጋ ምርመራ ዘርፍ ባከናወኑት ምርመራ የማስፋት ስራ እና በጠንካራ ክትትል ወንጀል ፈፃሚዎቹን በመያዝ ተሽከርካሪዎቹን ማስመለስ እንደተቻለ ከዚህ ቀደም መዘገባችን ይታወቃል፡፡

ፖሊስ በዚህ የወንጀል ድርጊት ላይ ተሳትፎ ባደረጉ ከ30 በላይ በሚሆኑ ግለሰቦች ላይ የምርመራ መዝገብ በማደራጃት መዝገቦቹን ለሚመለከተው የፍትህ አካል ልኮ ክስ እንዲመሰረትባቸው አድርጓል፡፡ ክስ ከተመሰረተባቸው ወንጀል ፈፃሚዎች መካከል ወንጀሉን በማስተባበርና በዋና ወንጀል ፈፃሚነት የተከሰሱ አዱኛ ቡዙነህ እና መኮንን ሙስጠፋ የተባሉ በ6 ዓመት ፅኑ እስራት መቀጣታቸውን የአዲስ አበባ ፖሊስ አስታውቋል፡፡ የተሰረቁትን ተሽከርካሪዎች በገዙና ባሻሸጡ እንዲሁም በልዩ ልዩ ደረጃ ተሳትፎ በነበራቸው ግለሰቦች ላይ እንደጥፋታቸው ክስ ተመስርቶ ጉዳያቸው በፍርድ ቤት እየታዬ ይገኛል፡፡

Exit mobile version