Site icon ETHIO12.COM

ያልተነቀለው ሰንኮፍ – ዩሪ ቢስሜኖቭ እንዳለው፣ እኛም እንዳየነው…

ዩሪ ቢስሜኖቭን ጠቅሰን ስንመረመር፣ መጀመሪያ የምንለው ” ምን ያልሆነና ያልተሞከረ ነገር አለ?” ነው። ትህነግ የሚባለው እርመኛ ቡድን ትውልድ ላይ የተከለው፣ ሚዲያና የሚዲያ ተምቾችን ፈልፍሎ እንዴት የዜጎችን እረፍት እየነሳ እንዳለ ስናይ ዩሪ ቢስሜኖቭ ትክክሉን እንደነገረን ይገባናል። ለካ ትህነግ ትውልድ ያላሽቅ የነበረው ለዚህ ነው ብለን በቁጭት ብንጠይቅም ዛሬም ድረስ ትህነግ የተተከለባቸው ማህበራዊ አውዶችና አግሽቦ የሰራቸው እቃዎቹ …

በተፈራ መንግስቱ – ነጻ አስተያየት – አገር አማን መጽሄት


ምን ያልሆነ ነገር አለ? ምን ያልተሞከረ ነገር አለ? ተሞክረው የከሸፉና ሊሞከሩ አቅድ የተያዘላቸውን ሁሉ በረጋ ስሜት መመርመር አንደሚገባ፣ መመርመር ብቻ ሳይሆን መርመሮ አቋቋምንና አቋቋምን ማስተካከል የወቅቱ ጥያቄ አንደሆነ የሚያመላክቱ ድምጾች….
ደረጃውን ቢቀያይርም የተገንጣይ ስሙን ለግማሽ ምእተ አመት ሙጢኝ ብሎ የያዘው አሸባሪው ትህነግ “ በልክህ ኑር” ሲባል፣ ወደ መቀለ አየሸሸ የገነባው አገርን በፈጠራ ዜና የሚያናውጥ የሳይበር ጦር ነበር።

“ዲጂታል ወያኔ” ብሎ የተከለው ይህ የቅጥፈት ጭፍራ የተሳካ ወረርሽኝ ማካሄድ የቻለው ደግሞ ኢትዮጵያ ላይ ከተጫነባት በሁዋላ ሌሎች የተከተሉትን አንድን አገር አንበርክኮ የመግዛት አራት ስልቶችን መርሁ አድርጎ ስለመሆኑ ሂደቱን ያጠኑ ይገልጻሉ። ስልቶቹ ደረጃ በደረጃ ሆነዋል። ግን ተርፈናል። ዩሪ ቢስሜኖቭ ይተርካል።

ዩሪ ቢስሜኖቭ በቀደመችው ሶቪየት ህብረት ኬጂቢን ሲያገለግል የነበረ፣ በጋዜጠኛናት የሰራ ሰው ነው። አሱ አንደሚለው አንድን አገር አንበርክኮ ለመግዛት ትውልድን ማላሸቅ፣ ትውልዱን አላሽቆ አውነትን እንዳይቀበል ማድረግ፣ በተቋማት ውስጥ የላሸቁትን በመመደብ ማንኮታኮት መበተን፣ ኢኮኖሚውን ማናጋት፣ ቀውስ መፍጠር፣ በቀውስ ወስጥ ማህበራዊ እረፍት መንሳት፣ ይህ ሁሉ ከሆነ በሁዋላ ኖርማላይዜሽን ወይም አረጋጊ መስሎ ወደ ቤተመንግስት መሮጥ።
ትህነግ የሚባለው ቡድን ኢትዮጵያን አምበርክኮ ለመግዛት የሄደባቸውን መንገዶችና ካፈገፈገ በሁዋላ አየተከተላቸው ያለውን አግባቦች ከላይ በተቀመጠው አውድ ማየት አግባብ የሚሆነው አቋምንና አቋቋምን በመለየት፣ የሚረጨውን ሁሉ አንዳለ ከመቀበል ይልቅ ለማበጠርና በወንፊት ለመንፋት እንደሆነ ምክራቸውን በማስርጃ የሚያቀርቡ ይናገራሉ። ለማሳያ የተበተነቸውን የቀድሞ ሃያል አገር ያነሳሉ፤

ለሶቪየት ኅብረት መፈራረስና ለኮሙኒዝም እንደ ርዕዮት መወገድ የአንበሳውን ድርሻ የሚወስዱት የሮማ ካቶሊክ ርዕሳነ ሊቀጳጳስ ዮሐንስ ጳውሎ ዳግማዊ፣ የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ሮናልድ ሬጋንና የዚያን ወቅት የሶቪየት ኅብረት መሪ ሚኻኤል ጎርባቼቭ ነበሩ።
ይህንን ጉዳይ በተለይ የሮም ካቶሊክ ቤ/ክ ውስጥ አዋቂና የቀድሞው ኢየሱሳዊ አባል ዶ/ር ማላኪ ማርቲን (Malachi Martin) The Keys of This Blood: Pope John Paul II Versus Russia and the West for Control of the New World Order በሚለው መጽሐፋቸው በግልጽ የጻፉበት ነው። የዓለምን የኃይል ሚዛን በመቆጣጠር ዓለምአቀፋዊ ተፎካካሪዎቹ የሚሄዱበት መንገድና ይህንን ለማስፈጸም የሚጓጓበትን ርቀት መጽሐፉ ድንቅ በሆነ መንገድ ያስረዳል።

በመጽሐፉ የመጀመሪያ ገጾች ምሑሩ ያስቀመጡት ድንቅ አገላለጽ አለ። እንዲህ ይላል፤ “ወደድንም ጠላንም፤ ተዘጋጀንም አልተዘጋጀንም ሁላችንም ሁሉን አቀፍና ከማንም ቁጥጥር ውጪ በሆነ ዓለምአቀፋዊ የሦስትዮሽ ፉክክር ውስጥ ነን”። እንደ መጽሐፉ ትንታኔ ይህ ፉክክር በዓለማችን ላይ አንድ ወጥ የሆነ ሥርዓት ለመመሥረትና ዓለምን በዚያ ለማስተዳደር የሚደረግ እንደሆነ ያብራራል።

ፉክክሩ ከማንም ቁጥጥር ውጪ የሆነው ውጤቱ የእያንዳንዱ ሰው የግልና የዜግነት ሕይወት፣ የቤተሰብን፣ የሥራ፣ የንግድና የገንዘብ፣ የትምህርት፣ የሃይማኖትና የባሕል፣ እንዲሁም ብዙውን ጊዜ በቀላሉ የምንወስደውን የአገራትን እና የዜጎችን ብሔራዊ ማንነት ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ፣ ሥርነቀልና እጅግ ኃያል በሆነ መልኩ ለዘላለም የሚቀይር እንደሆነ ጸሐፊው ያትታሉ። እኔ በዚህ ፉክክር ምኔም አይነካም የሚል ግለሰብም ሆነ አገር እንደማይኖር ከገለጹ በኋላ አገራዊና ግለሰባዊ ሕይወታችን እንደማይመለስ ሆኖ እንደሚቀየር በሰፊው ያስረዳሉ።

በመጽሐፉ እንደተገለጸውና እኛም በሕይወታችን እንደታዘብነው ለሶቪየት ኅብረት መፍረስ ሁለቱ ኃያላን ትልቁን ሚና ቢጫወቱም የራሷ አገር መሪ በከፍተኛ ሁኔታ ትልቅ አስተዋጽዖ እንዳደረጉ እንረዳለን። የዚያኔዋ ሶቪየት በሯን እንድትከፍተና የአሜሪካ ትልልቅ ኩባንያዎች ወደ ሶቪየት እንዲገቡ ጎርባቼቭ ፈቀዱ። በቀጣይም ምዕራባውያን ለሶቪየት ተሃድሶ ያሰቡ በሚመስል መልኩ አንድ ታላቅ ሃሳብ ቀረበ። የወቅቱ የጣሊያን ጠቅላይ ሚኒስትር የነበሩት ቺሪያኮ ደ ሚታ “ለሶቪየት ኅብረት የማርሻል ፕላን” በማለት የሰየሙት ዕቅድ ይፋ ሲሆን በአሜሪካና በሶቪየት መካከል ፈጣን የዲፕሎማቲክ ግንኙነቶች መካሄድ ቀጠሉ። በአገር ውስጥ “ፔሬስትሮካ (ዳግም ግንባታ)” እና “ግላስኖስት (ግልጽነት)” በሚሉ መርሕዎች ጎርባቼቭ የሶቪየትን አንጥሏ አስኪታይ ድረስ ደጃፎች ሁሉ ለምዕራቡ አገራት በረገዱ።
በቀጣይ በአሜሪካና በአገራቸው መካከል የተፈረመው ስምምነት አደረጉ። General Agreement on Contacts, Exchanges and Scientific Technical Education and Other Fields የሚለው ስምምነት በሁለቱ አገራት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች አቅራቢነት በሬጋንና ጎርባቼቭ መካከል ሲፈረም ስምምነቱ የሚያስከትለው ለውጥ በብዙዎች በውል የተገመተ አይመስልም ነበር። ከላይ በተጠቀሰው መጽሐፍ ላይ በዝርዝር እንደተብራራው ይህ ስምምነት የማይገመቱ በርካታ ዝርዝር ሃሳቦችን የያዘ ነበር።

ለአብነት ያህልም ሦስተኛው አንቀጽ በሁለቱ አገራት መካከል በሳይንስ፣ በቴክኖሎጂ፣ በሰብዓዊ ትምህርትና በማኅበራዊ ጥናቶች ዙሪያ ትብብር እንደሚኖር ይገልጻል። ጠለቅ እያለ ሲሄድ ግን በሶቪየት ኅብረትና በአሜሪካ ትምህርት ቤቶች ጥቅም ላይ የሚውሉት የመማሪያ መጻህፍት ላይ ጥናት እንደሚካሄድ ያብራራል። በሌላ አነጋገር በአሜሪካ የአንደኛ ደረጃ ተማሪና በሶቪየት ኅብረት የአንደኛ ደረጃ ተማሪ ምንም ልዩነት በሌላቸው መጽሐፍት አንድ ዓይነት ትምህርት፤ አንድ ዓይነት ታሪክ አንዲማሩ የሚያደርግ ነበር።የዚህ ስምምነት ፍጻሜው ግን የራሺያ ልጆች የአሜሪካንን ታሪክ እንዲማሩ ያደረገ እንደሆነ አሁን ላይ ለመገንዘብ አያዳግትም።

እንደዚህ ባለ የረቀቀ ሥልት የወቅቱ ልዕለ ኃያል ታላቋ የሶቪየት ኅብረት ከፈረሰች በኋላ ከቫቲካን ጋር የዓለምን የኃይል ሚዛን የምትቆጣጠረው አሜሪካ ብቻ ሆነች። ከሶቪየት መፍረስ በኋላ የሥልጣን መንበሩን የተረከቡትና የቀድሞውን የሶቪየትን ገናና ክብር በመመለስ ከፍተኛ ተጋድሎ ያደረጉት ቭላድሚር ፑቲን ለሶቪየት መፍረስ ተጠያቂ የሚያደርጉት ጎርባቼቭን ነው። ስለ ሶቪየት መፈራረስ ፑቲን ሲናገሩ “የ20ኛው ክፍለዘመን ታላቁ የጂኦ-ፖለቲካዊ ውድመት” በማለት ነው የሚጠቅሱት።

ይህንን የፑቲን አባባልና ሥራቸውን በቅርብ የሚከታተሉ ምዕራባውያን ተንታኞች “ጎርባቼቭ የቀየረውን ነገር ሁሉ ፑቲን መመለስ ነው የሚፈልገው” በማለት ይከሷቸዋል። አንድ ታሪክ ጠገብ የሆነን አገር ለማፍረስና በምዕራባውያን የሚዘወር መንግሥት ለመመሥረት ምዕራባውያን ጠላት ሆነው አይደለም የሚቀርቡት። ከማንም በላይ ለአገሩ ዜጎች አዛኝና ተቆርቋሪ፣ ለሚደርሰው በደል (እውነተኛ ለሆነውም ሆነ ላልሆነው) ከተበዳዩ በላይ የሚያዝኑ ክንፍ ዓልባ መላዕክት በመሆን እና ካስፈለገም “ማርሻል ፕላን” እስከማውጣት በሚደርስ “ሐዘኔታ” ነው።
ይህንን ረቂቅ ዕቅድ የማይረዳ ወይም የምሥጢር ደጋፊያቸው የሆኑ መሪ የአገሩን በር ወለል አድርጎ በመክፈት በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ የጥፋት ዕቅዱ ተባባሪ ይሆናል። አንድ አገር እንዴት መፍረስ እንደምትችል ጥናት ያደረጉ ከሚያቀርቧቸው ሃሳቦች መካከል በአሁኑ ጊዜ እየሠራ የምናየው አንዱ ጥፋቱን ከውጪ ማቀነባበር ሳይሆን ከውስጥ በራሱ ማኅበረሰብ ማድረግ ውጤታማ ብቻ ሳይሆን ቀላልም እንደሆነ ይገባል ጎርባቼቭን ማየቱ በቂ ነው።

የጦር ሠራዊት አሠማርቶ፣ ሳንጃ ወድሮ፣ ጦር ሰብቆ፣ በርካታ ወጪ አውጥቶ አንድን አገር ማፍረሱ ውድመትን የቀላቀለና ወጪ የሚያስከትል የማፍረስ ዘመቻ ነው። ከዚህ ይልቅ ግን ሌላው ቀላል ተብሎ የሚጠቀሰው ከውጭ ሳይሆን ከውስጥ የማፍረስ ዘመቻ ነው። ለዚህም ተግባራዊነት ዋናው መንገድ አንድ ማኅበረሰብ የተዋቀረበትን ዓውዶች ነጥሎ መለየት ቀዳሚው ሥራ ሲሆን፣ አንዲፈርስ የተበየነበትን ማኅበረሰብ “የሥበት ማዕከላት” በሚባሉት ጉዳዮች፣ ኣውዶች፣ ግንኙነቶች፣ አስከ አመነት ተቋማትና ወሳኝ መዋቅሮች በመዝለቅ ውጤታማ ሥራ መሥራት በቀጣይ የሚተገበር ይሆናል።

ይህ መርዛማ አካሄድ ሲተገበር ከላይ በተዘረዘሩት አግባቦች የማኅበረሰቡን አስተሳሰብ በተለያዩ ሥልቶች ከተቻለ መቆጣጠር፣ ካልተቻለ መስለብና ማፈራረስ ቀዳሚው ነው። ይህ የዜጎችን አስተሳሰብ የሚቀርጽና የሚቀይር ሲሆን በቀጣይ ጉዳዩን በፈለጉት አቅጣጫ ለመምራትና ለመቆጣጠር አመቺ መንገድ የሚፈጥር ይሆናል።

ሌሎቹ የሥበት ማዕከላት ዜጎች ለእውነት ያላቸው አስተሳሰብ፣ የቀጣዩ ትውልድ ሁኔታ፣ የአገሪቱ የፖለቲካ ፍልስፍና፣ ኢኮኖሚና በዋንኛነት የዜጎች ብሔራዊ ስሜት (ናሽናሊዝም) በዋናነት የሚጠቀሱ ናቸው። እነዚህን በተፈለገ አቅጣጫ ለመቆጣጠርና ወደተፈለገ አቅጣጫ ወስዶ ለሚፈለገው ግብ ለማዘጋጀትና አንድን አገር ለማፍረስ ዋንኛው የማድረጊያ ወይም መተግበሪያ ዘዴ ሚዲያ እንደሆነ ይጠቀሳል። ባለንበት ዘመን ደግሞ ማኅበራዊ ሚዲያ በዋናነት የዚህ መሰሉ እቅድ ማከናወኛ ኣውድ ነው። ይህን በወጉ በኣገራችን አይተነዋል። አያየነው ነው። ሚዲያን በመጠቀም አንድን ማኅበረሰቡ ዕውር ማድረግ ይቻላል። የተሠሩና ድንቅ የሆኑትን ነገሮች ሕዝቡ እንዳያይ፣ድንቅ ጉዳዮችን፣ ተስፋ ሰጪ ግኝቶችን ከማየት ይልቅ በሌሎች ጉዳዮች ላይ ትኩረት እንዲደርግ በሥፋት መሥራት አንዱና ዋንኛ የዘመቻው አካሄድ ነው።

Alula Yohannes, [05/08/2022 18:08]
ማህበረሰብ እወነቱን አንዳይረዳ ኣንዱ የማሳወሪያ መንገድ ቀለም መቀባት ነው። ቅቡን ለዚህ አላማ በተገዙ ወይም በተቋቋሙ ማካይነት ሚዲያው መታየት የሚገባው እንዳይታይ ተደርጎ ይሰራበታል። በተቃራኒው ሊታይ፣ ሊገኑና ህዝብ ተስፋ ሊሰንቅባቸው የሚገቡ ጉዳዮች መታየት በሌለበት አንዲተካ ይደረጋል። በቅጥፈት ቅብ የተቀባውና አውነተኛውን ጉዳይ አንዲጸፍን የተደረገው የሃሰት ድራማ በተጠቀሱት ሚዲያዎች ጎልቶ ይወጣል። አነዚህ የተዛቡ መረጃዎች አውነቱ ላይ አንዲናኙ ተደርጎ በስፋት ሲሰራጩ ህዝብ ኣቋሙ አንዲዛባ ይሆናል።
ይህ ቀለም የመቀባት ሥራ ዓይን ያወጣ ውሸት እውነት ሆኖ ተቀባይነት እንዲያገኝ ከማድረግ ባሻገር ሲደጋገም የማይናወጥ እውነት ሆኖ ይቀመጣል። በውጤቱም ሕዝብ ከመንግሥት የሚመጡ መረጃዎችን ቢያንስ በጥርጣሬ ካልሆነም በደምሳሳው ማንኛውም የመንግሥት መረጃ ውሸት ነው ብሎ እንዲቀበል እስከማሳመን የሚያደርስ ይሆናል። ይህ ኣካሄድ የገባቸውና ዘመቻውን ለማክሽፍ የሚሰሩትን ነክሶ በመያዝ በልዩ የጥላቻ ዘመቻ ማጥቃት ሌላው የዘመቻው ልዩ ትኩረት ነው።

ኢትዮጵያ ጠንካራ ኅብረብሔራዊ አገር ልዩ ባሕል፣ ልዩ ቋንቋ፣ ልዩ አኗኗር፣ ብዙ ሺህ ዘመናትን የተሻገረ ልዩ ታሪክ ያላት ነች። በተለይ ባሕልና ቋንቋ አንድን አገር ጠንካራና ገናና በማድረግ በኩል የሚጫወተው ሚና እጅግ ታላቅ ነው። በተደጋጋሚ ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ሲነገር እንደሚሰማውና ላለፉት 30 ዓመታት አንዴም እንኳ በሚዲያም ሆነ በመንግሥት ባለሥልጣን ሲነገር ያልተሰማው አገራችን የራሷ ፊደል ያላት የአፍሪካ ብቸኛዋ አገር ነች።

ይህ ለሕዝቧ ኩራት ቢሆንም ዓለምን በአንድ ለመቆጣጠር ለሚፈልጉ ደግሞ የዓላማቸው ዕንቅፋት ነው። ሶቪየት ኅብረት ልዩ በሆነ በራሷ ቋንቋ የምትደዳደር ልዕለኃያል እንደነበረች ልብ ይሏል። ይህ የኢትዮጵያ ቋንቋ መኩሪያና መመኪያ መሆን ሲገባው ባለፉት 30 ዓመታት የመጨቆኛ መሣሪያ ተደርጎ ብዙ ግፍ የተፈጸመበት ያለምክንያት አልነበረም። የአገሪቱን ብሔረሰቦች ፍላጎት በሚያሟላ መልኩ እንደተፈለገ ሊሻሻልና ሊስተካከል ሲገባው ከዚያ ይልቅ የተመረጠው የባዕድ ቋንቋ ነበር። ይህም በአዋጅ ጸድቆና በሕግ ተደንግጎ በሥራ ላይ በመዋል አንድን አገር ለማዳከምና ለማፍረስ ከሚተገበሩ ዓይነተኛው መሣሪያ ሆኖ አገልግሏል።
ይህ በተለይ በአንድ ታሪካዊ አገር ውስጥ የሚኖረውን የባሕልና የኑሮ ትሥሥር በማክሸፍ ትልቅ ሚና የሚጫወት ሲሆን በህዝብ መካከልም ባይተዋርነትን በመፍጠር የባሕል ትሥሥርንና ውኅደትን እንዲሁም ማኅበረሰብ የሚመሠረትበትን ድርና ማግ የሚያጠፋ ምርጥ ሥልት ነው። ከሦስት ዐሥርተ ዓመታት በኋላ እንደ ባቢሎን ግንበኞች ሰዎች ተነጋግረን የማንግባባ የሆነው ያለምክንያት አይደለም።

የኬጂቢ ሰላይ የነበረውና በኋላም ወደ ካናዳ የከዳው ዩሪ ቤዝሜኖቭ አንድን አገር ለማንበርከክ አራት ተከታታይና ተመጋጋቢ እቅዶች እንደሚያስፈልጉ የተናገረውንና በመግቢያው የተነሳውን አሳብ ማባላልላት ግድ የሚለው ለዚህ ነው። ዩሪ የማንበርከኪያው ማስፈሸሚያ ቀዳሚውና ዋንኛው መሳሪያ ሞራል የማላሸቅ ሒደት እንደሆነ ይስረዳል። ራሱም የሠለጠነ ፕሮፓጋንዲስት ስለነበር ስለዚህ ቀዳሚ ተግባር ሲናገር ይህ ትውልድን የማላሸቁ ሂደት ቀስ ተብሎ የሚከናወን ከ15 እስከ 20 ዓመታት የሚወስድ የረጅም ጊዜ ሒደት ነው ይላል። በእነዚህ ዓመታት ውስጥ አንድን ትውልድ ካላሸቁ በሁዋላ በምትኩ አዲሱን በሚፈለገው መንገድ ቀርጾ ማውጣት ይቫላል።

የሞራል መላሸቅ የደረሰበት ማኅበረሰብ ውስጥ የሚፈጠረው ትውልድ እውነት ቢነገረው የማይቀበል፣ አለመቀበል ብቻ ሳይሆን እውነታው በዓይን በሚታይና በእጅ በሚዳሰስ መልኩ ቢቀርብለትም በፍጹም የማይቀበል ድንዙዝ ይሆናል። በዚህ መልኩ ሞራሉ ላሽቆ የተሠራ ኅሊና ቢስ ትውልድ በየመንግሥት መዋቅሩ፣ በየትምህርት ፖሊሲ አውጪ ተቋም፣ በፋይናንስ፣ በኢኮኖሚ፣ በድህንነት፣ በማኅበራዊ ወዘተ ዘርፎች በመሠማራት የአገሪቱን ቁልፍ ቦታዎች እንዲይዝ ይደረጋል። ከዚያ በኋላ አንድትፈርስ የምትፈለገዋን አገር ለማፍረስ ብዙ ልፋት አይጠይቅም በማለት ዩሪ ቤዝሜኖቭ ያስረዳል።

ይህ ሁሉ ከሆነ በሁዋላ ቀጣዩ ተግባር ሞራሉ የላሸቀ አገር ሕዝብ ውስጥ የሚገኘውን የአገር መከላከያ ሃይል ማፈራረስ፣ የውጭ ግንኙነት መነቃቀል፣ ኢኮኖሚ ማናጋት፣ መሠረተ ልማት ማውደም፣ ህዝብ የተረጋጋ ህይወት አንዳይኖር ሁከት ማምረት፣ ግጭቶችን ማስፋፋትና ህዝብ ማህበራዊ እረፍት አንዲያጣ ማድረግ። ዩሪ አንደሚለው ይህን ለማከናወን የሚፈርሱት ተቋማት ጥንካሬ ቢለያይም ሂደቱ ከሁለት እስከ አምስት ዓመታት የሚፈጅ ሊሆን ይችላል ።

በሦሰተኛው ደረጃ የሚሰራው ከላይ የተቀነባበሩት ሁሉ ተግባራዊ ከሆኑ በሁዋላ አንዳች ቀውስ መፍጠር የሂደቱን ፍጻሜ ያፋጥናል። እንደ ዩሪ አገላለጽ ይህ ወደሚፈለገው ግብ የሚያደርሰው ቀውስ በጥቂት ሳምታት ውስጥ የሚተገበር ነው ።ከዛም የመጨረሻው ማረጋጋት ይሆናል።

አንግዲህ ዛሬ በንጹሃን ደም የሚቆመረው ፖለቲካ፣ የተናበበው የሚዲያ ዘመቻ፣ የቀውሱ የመጨረሻ ክፍል አመላካች ለመሆኑ በየደረጃ አገራችን ላይ የተፈጸመውን በማስላት መረዳት ግድ ነው። አላሽቀውናል። የላሸቁ ተቋማት ተለጣጥፈው አንዲላሽቁ ተደርገው በተሰሩ ተመርተዋል። የጸጥታ ተቋሞቻችን ፈርሰዋል።መከላከያችን አንዲወድም ተደርጓል። ኢኮኖሚው አንዲሰበር ሆኗል። በሃይማኖት ተቋማት ሳይቀር የላሸቁ ገብተው አንተበውናል። በየስፍራው ሞትን በየአይነቱ፣ ስደትን በየፈርጁ፣ ሃዘንን በፈረቃ አከናንበውናል። በስተመጨረሻ ዩሪ አንዳለው ኖርማላይዝ ወይም አረጋጊ ሆነው ለመምጣት ከገዟቸውና ከራሳቸው ሚዲያዎች ጋር ሆነው በደም ጀልባ ጉዞ መጀመራቸውን አየወተወቱ ነው። “የአይጥ ምስክር ዲንቢጥ አንዲሉ” አራጅና አሳራጅ ከእርድ ከተረፉት በላይ “ አመኑን” አያሉ ነው።

Exit mobile version