Site icon ETHIO12.COM

ከአራት ወረዳዎች በስተቀር የሽግግር ፍትህ ግብዓቶች ማሰባሰቢያ ውይይት በመላው አገሪቱ ተካሄደ

“የሽግግር ፍትህ ፖሊሲ አማራጭ ማእቀፎች ዙሪያ በመላዉ አገሪቱ ሲካሄድ የነበረዉ የህዝብ ዉይይት ተጠናቀቀ፤ አራት ወረዳዎች በጸጥታ ምክንያት ውይይቱ አለማከሄዱ ገዝፎ ዜና የሆነበት ዜና በአገሪቱ የሚዲያውን ጨለምተኛነት የሚያሳይ በሽታ ነው” የህግ ባለሙያዎች አስተያየት ሰጥተዋል።

በኦሮሚያ ክልል ደምቢ ዶሎና ያቤሎ፣ በአማራ ክልል ሰቆጣና ደብረ ማርቆስ ብቻ ውይይት እንዳልተደረገ ተመልክቷል። ወልቃይትና ሁመራ ምክክር ለማካሄድ የሚከለክል የጸጥታ ችግር ባይኖርም ውይይቱ አልተካሄደም። ውይይቱ ያልተካሄደው በተጠቀሱት አካባቢዎች ካለው ወቅታዊው የአስተዳድር ሁኔታ አንጻር ለጥንቃቄ ነው። “አንድን ቡድን አሳትፈዋል፤ ሌላውን አግልለዋል” የሚል ቅሬታ እንዳይነሳ በሚል ፍርሃቻ ውይይቶቹ መስረዛቸውን እንደሰሙ የሚገልጹት የህግ ባለሙያዎች ” በዚህ ደረጃ የዚህን ታላቅ አገራዊ አጀንዳ አንሸዋሮ ማቅረብ በኢትዮጵያ የሚዲያውን ተያይዞ ወደ ገደል መውረድ አመላካች ነው” ሲሉ ገልሰውታል።

የፍትህ ሚኒስትር በድረገጹ እንዳለው ብሄራዊ የሽግግር ፍትህ ፖሊሲ የባለሙያዎች ቡድን ከተዋቀረበት እለት አንስቶ ሲያከናዉናቸዉ የቆዩ ተግባራትን አስመልክቶ በሰጋዜጠኞች መግለጫ በአማራጭ ሀሳቦች ዙሪያ በመላዉ የአገሪቱ አካባቢዎች ሲያካሂድ የነበረዉ የህዝብ ዉይይት መጠናቀቁን ይፋ አድርጓል፡፡

በኢትዮጵያ የሽግግር ፍትህ ፖሊሲ ማእቀፍ መዘርጋት አስፈላጊነት ታምኖበት ሁሉን አቀፍ አካታችና ተመጋጋቢ የሆነ ፖሊሲ ለማዘጋጀት ባለፉት ወራቶች የግብአት ማሰባሰቢያ የዉይይት መድረኮች ሲካሄድ መቆየቱን የገለፁት የቡድኑ አባል ዶክተር ማርሸት ታደሰ በኢትዮጵያ ካለዉ አሁናዊ ሁኔታና አዉድ ጋር በተያያዘ ወቅታዊ ነዉ ወይ በሚል የሚነሱ ጉዳዮች መኖራቸዉን ጠቁመዉ ቡድኑ አሁን እያከናወነ ያለዉ ተግባር ለትግበራው የሚያስፈልጉ መደላድሎችን መፍጠር መሆኑን በማንሳት ከወቅታዊነት ጋር በተያያዘም የባለሙያዎች ቡድኑ በአገሪቱ ያሉ ግጭቶችን ለመፍታትም ሀቅንና እርቅን በማመቻቸትና ተጠያቂነትን በማስፈን መፍትሄ በማፈላለግ በኩል ሰላምን የመፍጠሪያ አንድ አማራጭ አድርጎ እንደሚቆጥረዉ ገልጸዋል፡፡

ነገር ግን ወደትግበራ ሲገባ አንፃራዊ ሰላም እንደሚያስፈልግ በመጠቆም አገሪቱ ዉስጥ የሚስተዋሉ እነዚህ ችግሮች ካልተፈቱ አስቸጋሪ ሊሆን እንደሚችል ያላቸዉን ስጋት አስቀምጠዋል፡፡

የሽግግር ፍትህ ፖሊሲ ቡድን አስተባባሪ ዶክተር ታደሰ ካሳ በበኩላቸዉ ፖሊሲዉ ብሄራዊ የአገር መሪነትና ባለቤትነት ባረጋገጠ መልኩ የተቃኘ መሆኑንና የሚቀርቡ ምርጫዎች ሁሉ እንደ አገር ህዝብ ተስፋ የሚያደርገዉን ነገር የሚወስኑ መሆናቸዉን በመግለፅ የምክክር ሂደቱም ቅድመ ፖሊሲ ከመቅረፅ ጀምሮ ሪፖርት መጻፍና ረቂቅ ማሰናዳትና እንዲሁም ከሚመለከታቸዉ ባለድርሻ አካላት ጋር ተወያይቶና ሰነዱን አዘጋጅቶ መላክን እንደሚያካትት አብራርተዋል፡፡

የሽግግር ፍትህ ፖሊሲዉ ዝግጅት በአገራችን የህግና የፖሊሲ አወጣጥ ታሪክ ያልተለመደና አዲስ ነገርን ይዞ የመጣ ነዉ ያሉት አሰተባባሪዉ ከላይ ወደታች የነበረዉን የፖሊሲ አወጣጥ በማስቀረት ከታች ወደላይ አሰራርን የተከተለና ለህዝቡ ሰፊ እድል የሰጠ ሲሆን በዚህም በመንግስት በኩል አገርና ህዝብ የሚፈልጉትን ነገር አንጥሮ ለመለየት እድል የሰጠ፣ህብረተሰቡ በትግበራዉ ላይ የሚኖረዉን ቁርጠኝነት የተሻለ ለማድረግና ወሳኝ የሆኑ የአካታችነት፣የግልፀኝነት፣የገለልተኝነትና ሌሎች መርሆዎችን በተሻለ መልኩ ለመተግበር እድል ይሰጣልም ብለዋል፡፡

በእስካሁኑ ሂደትም በአዲስ አበባ፣ በ12 ክልሎችና በድሬድዋ ከተማ አስተዳደር በጥቅሉ በ59 አካባቢዎች ዉይይቶች የተደረጉ ሲሆን ከ40 ዩኒቨርሲቲ የተዉጣጡ ከ200 በላይ የህግ መምህራን በሂደቱ ተሳታፊ መሆናቸዉ በመግለፅ በእነዚህ መድረኮች የተሰባሰቡ ግብአቶችን ማደራጀትና መተንተን፣ ዋና ዋና ግኝቶች ላይ የማጠቃለያ ሪፖርት ማዘጋጀትና በበመጨረሻም ብሄራዊ የሽግግር ፍትህ ፖሊሲ ማእቀፍ አዘጋጅቶ ማስረከብ የቀጣይ የቡድኑ ተግባራት መሆናቸዉ ተብራርቷል፡፡

የሽግግር ፍትህ ፖሊሲ ከአገራዊ የምክክር ጋር ያለዉን ልዩነትና ተመጋጋቢነት ያብራሩት ሌላኛዉ የቡድኑ አባል አቶ ምስጋናዉ ሙሉጌታ ሲሆኑ እንደ እሳቸዉ ማብራሪያም ዉስብስብና መጠነ ሰፊ ችግር ባለባቸዉ አገራት ከነዚህ አማራጮች በዘለለ ሌሎች ሂደቶችም በአንድ ላይ እንደሚተገበሩና አገራዊ ምክክርና የሽግግር ፍትህ ፖሊሲዎችም ተመጋጋቢና ነገር ግን የተለያዩ አዉድና ግብ ያላቸዉ ሂደቶች መሆናቸዉን ገልፀዋል፡፡

ሁለቱም ለዘላቂ ሰላምና ለአገረ መንግስት ግንባታ የራሳቸዉ መሰረታዊ አስተዋፅኦ እንዳላቸዉና የሽግግር ፍትህ ዋነኛዉ ትኩረት ተፈፀሙ የሚባሉ ከፍተኛ የሰብአዊ መብት ጥሰቶች ላይ መሆኑንና በእነዚህ ሂደቶች ክስ የሚኖር መሆኑን በመግለፅ በአገራዊ ምክክር ላይ ግን በአብዛኛዉ ክስ የሌለ መሆኑ ልዩ ያደርጋቸዋል ሲሉ ከተቋማዊ አደረጃጀት አነፃርም የሽግግር ፍትህ በሁለት አይነት እንደሚደራጀና እነዚህም እዉነት ኮሚሽንና ፍርድ ቤት ላይ የሚተገበሩ ሲሆን አገራዊ ምክክር በአገራዊ ምክክር ኮሚቴ መሰል ቡድኖች እንደሚደራጅና በጥቅሉ አገራዊ ምክክር በሽግግር ፍትህ አማራጮች እንደ አንድ አማራጭ መካተቱንም አያይዘዉ አዉስተዋል፡፡


Exit mobile version