ቀሲስ በላይ ከስድስት ሚሊዮን አምስት መቶ ሺህ ዶላር በላይ ገንዘብ በህገወጥ ለማዘዋወር ሲሞክሩ መያዛቸውን በማህበራዊ ገጾች ስምና ቦታ ተጠቅሶ ቅድሚያ መዘገቡ ይታወሳል። ይሁን እንጂ ፋና ዜናውን ፍርድ ቤትን ዋቢ አድርጎ እሲክዘግበው ድረስ ከመንግስት ወገን የተሰማ ነገር አልነበረም።
ዛሬ ይፋ እንደሆነው ከሁለት ቀናት በፊት በማህበራዊ ሚዲያ ተበትኖ የነበረው ብዙም ከእውነት ያልራቀው ዜና አግባብ ሆኖ ተገንቷል። “ቀሲስ በላይ መኮንን በተጠረጠሩበት በሀሰተኛ ሰነድ ከ6 ሚሊዮን ዶላር በላይ ገንዘብ ዝውውር ወንጀል ለምርመራ ማጣሪያ ጊዜ ቀጠሮ ተፈቀደ” ሲል ፍርድ ቤትን ጠቅሶ ፋና ዘግቧል።
የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ጊዜ ቀጠሮ ችሎት ቀሲስ በላይ መኮንን በተጠረጠሩበት በሀሰተኛ ሰነድ የዶላር ዝውውር ወንጀል ለምርመራ ማጣሪያ ጊዜ ቀጠሮ መፍቀዱ ተሰምቷል፡፡
የፌደራል ፖሊስ መርማሪ ቀሲስ በላይ መኮንን ከትናንት በስቲያ በአፍሪካ ህብረት ቅጥር ጊቢ ውስጥ በሚገኘው የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ውስጥ በአካል ቀርበው ሀሰተኛ የክፍያ ሰነዶችን በመያዝ ለ3 ግለሰቦች እና ለአንድ የግል ድርጅት ሒሳብ 6 ሚሊየን 50 ሺህ ዶላር ሊያዘዋውሩ ሲሉ በአፍሪካ ህብረት ሴኪዩሪቲዎች ተይዘው ለፌዴራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ተላልፈው መሰጠታቸውን ጠቅሶ የጥርጣሬ መነሻውን ለችሎቱ ማቅረቡን ፋና ዘግቧል
በዚህ መነሻ መሰረትም መርማሪ ፖሊስ ተጨማሪ የምርመራ ማጣሪያ ሥራ ለማከናወን የ14 ቀን ጊዜ ቀጠሮ እንዲሰጠው ጠይቋል።ተጠርጣሪ ቀሲስ በላይ መኮንን ድርጊቱ መፈጸሙን አምነው፤ ይሁን እንጂ ወንጀል አለመፈጸማቸውን አስረድተዋል።ስለሆነም የዋስትና መብታቸው እንዲፈቀድላቸው ጠይቀዋል።የግራ ቀኝ ክርክሩን የተመለከተው ጊዜ ቀጠሮ ችሎቱ ተጠርጣሪው ያቀረቡትን የዋስትና ጥያቄ በማለፍ ለፖሊስ የ7 ቀናት የምርመራ ፈቅዷል።