ለአንድ ቀን ከጮኸና አየሩን ሁሉ ከተቆጣጠረ በሁዋላ ውሃ የተቸለሰበት “ሕወሓት ብልፅግናን ለመቀላቀል በድርድር ላይ ነው” የሚለው የዋዜማ ዜና ፖለቲካውን ለሚረዱ የዜናው ሰምና ወርቅ ትርጉም ላይ እንዲያተኩሩ ያደርጋቸዋል። ለዚህም እይታቸው ምክንያት አላቸው። ይህን እየታቸውን ያጠራላቸው ደግሞ ትህነግ ዜናውን በፍጥነት በውጭና አገር ውስጥ ሚዲያዎቹና ማህበራዊ አውዶቹ ለማስተባበል የሄደበት ፍጥነት ነው።
ለውጡ እውን እንደሆነ ” ከብልጽግና ጋር አልሰራም” ያለው የትግራይ ህዝብ ነጻ አውጪ ግንባር ከብልጽግና ጋር ለመዋሃድ እየመከረ መሆኑ ተጠቅሶ ዜና ሲሰራጭ ” ከዜናው በላይ ከዜናው ጀርባ ያለው ጨዋታ ገብቶናል” ያሉ “ከቶውንም ሊሆን የማይችል” ሲሉ ወዲያው መረጃ ሰጥተዋል። አንዱ የሆኑት ፕሮፌሰር ጌትነት GAT በሚባለው የዩቲዩብ ገጻቸው ላይ ” ትንቢቴ ባይሳካ ደስ ይለኛል። ይህ የማምታቻ ዜና ነው። ትህነግ ጦርነት መክፈቱ አይቀሬ ነው” የሚል ትንተና ሰጥተዋል።
የገባቸው አስቀድመው እንዳሉት ሁሉ ትህነግም ዜናውን ፈጥኖ ” ሙሉ በሙሉ ከእውነት የራቀ ነው ” ሲል መግለጫ አውጥቷል። ትህነግ ዜናውን በራሱ አውድ ብቻ ሳይሆን በቢቢሲ ፎከስ አፍሪካ ላይ አቶ ጌታቸው ረዳ ሰፊ ማስተባበያ ሰጥተዋል። ይህ ደግሞ ለነጮቹ እንዲደርስ ታስቦ ነው። “የፕሪቶሪያው ስምምነት አብረን እንድንሠራ ዕድል ስለሰጠን፤ ለሕዝብ ጥቅም ሲባል ልዩነቶቻችን ምንም ይሁኑ ምን አብረን እንድንሠራ አስችሎናል። ይህም ወደፊት ይቀጥላል ብዬ አስባለሁ” ሲሉ ንግግሩ ጭራሹኑ የመዋሃድ እንዳልሆነ ገልጸዋል።
ለሎች የትህነግ ህጋዊ የሆኑ የማህበራዊ ገጾችና አመራሮች በርብርብ “ዜናው ሃሰት ነው” የሚል መረጃ በፍጥነትና በተከታታይ እያሰራጩ ነው። ይህን ተከትሎ ነው “የዜናው ሰምና ወርቅ ተገልጧል” ሲሉ በገሃድ አስተያየታቸውን መስጠት የጀመሩት።
እነዚህ ወገኖች ትህነግ ከብልጽግና ጋር ለመዋሃድ ውይይት ላይ እንደሆነ ተደርጎ ዜናው እንዲሰራ የተደረገው ከትህነግ ሰፈር ነው። ዜናውን ለዋዜማ የሰጡ ወይም ” አብረን እንስራ” ሲሉ ያጋሩ የትህነግ ሰዎች በዋናነት ዓላማቸው “የአማራ ህዝብን ለማስቆጣት፣ የአማራ ህዝብ ተከዳን በሚል መንግስት ላይ እንዲያኮርፍ” ለማድረግ እንደሆነ ይናገራሉ። በተለይም በራያ ሰቆጣ አካባቢ ከ50 ሺህ ሰዎች በላይ ያፈናቀለውን ዳግም ወረራ ” ከመንግስት ጋር ተነጋግረን ነው” በሚል የትህነግ ሰዎች ለተናገሩት ግልጽ ያልሆነ ምክንያት ይበልጥ ማጠናከሪያ አድርገውታል።
አቶ ጌታቸው ለቢቢሲ ፎከስ ኦን አፍሪካ፣ ቀደም ሲል ምክትላቸው የቀድሞ ሌተናል ጄነራል ታደሰ ወረደ የትህነግ ይሃሎች ወደ ራያና አላማጣ የገቡት ከፌደራል መንግስት ጋር በተደረገ ስምምነት እንደሆነ መግለጻቸውን ተከትሎ የውህደት ዜናው መሰራጨቱ መንግስት ላይ ቁጣ ለማስነሳት ያለመ፣ በቀጣይ ወደ ወልቃይት ለመሄድ መንግስት እንደፈቀደ ተደርጎ እንዲታሰብ ለማድረግ እንደሆነ እነዚሁ ወገኖች ይገልጻሉ። የዜናው ሰሙ ይህ እንደሆነ የሚገልጹት እነዚህ ወገኖች፣ ዜናው ባልታሰበ መንገድ ተመልሶ ትህነግን እንዳቃጣለው ሲያስታውቁ ” ይህ የዜናው ወርቁ ነው። ዜናውን ያሰራጩትም ሆነ የሰጡት ያልገመቱት ጉዳይ” ብለውታል። በተለይም ዋዜማ ብልጽግና ላይ ያነጣጠሩ ዜናዎችን የሚሰራና አጀንዳ የሚተክል ሚዲያ ከመሆኑ አንጻር ዜናውን ሙሉ በሙሉ ለትህነግ ሲል እንደሰራው የሚያምኑ፣ ባልታሰበ ደረጃ ዜናው ትህነግ ላይ ተመልሶ አደጋ መሆኑ ለማስተባበል ሩጫ መመረጡን እነዚሁ ወገኖች ይናገራሉ።
ዜናው መልሶ ራሳቸውን ስለጎዳው በውጭ አገር ሚዲያዎች ሳይቀር ማስተባበያ የተፈለገው፣ ትህነግ ብልጽግናን እንዲያፈርስ የቤት ስራ ወስዶ የሚሰራ ድርጅት በመሆኑ፣ ዜናው የቤት ስራውን ከሰጡት ወገኖች ጋር ስለሚያጋጨው እንደሆነ አስተያየት የሚሰጡ ወገኖችም እየተሰሙ ነው።
ዛሬ በማህበራዊ ሚዲያዎች ላይ ህዝባዊ ወያነ ሓርነት ትግራይ (ህወሓት) ከብልጽግና ፓርቲ ጋር ለመቀላቀል ተከታታይ ድርድር እያደረገ ነው የሚሉ መረጃዎች ሲሰራጭ እንደነበር ጠቅሶ ትህነግ ዜናውን ሙሉ በሙሉ ከእውነት የራቀ መሆኑን ጠቅሶ ማስተባበያውን በማህበራዊ ገጾች በፍጥነት ያሰራጨው ከአባላቱና ደጋፊዎቹ ባላሰበው መልኩ ተቃውሞ ስለገጠመው እንደሆነ የሚናገሩም አሉ።
” ከብልጽግና ጋር በተከታያይ እየተካሄደ ያለው ውይይት ከፕሪቶሪያ የሰላም ስምምነት በኋላ የተፈጠረውን ሰላም ለማስፋት እና ለማጠናከር ያለመ ነው ” ሲል ያስታወቀው ትህነግ፣ ከብልጽግና ፓርቲ ጋር መሰረታዊ የሆነ የዓላማና የአስተሳሰብ ልዩነት እንዳለው አምልክቷል። ” ልዩነቱ እንዳለ ሆኖ ሁለቱ ፓርቲዎች ሊወያዩባቸው የሚገቡ ብዙ አጀንዳዎች አሉ ” ሲልም በማስተባበያው ላይ ጠቁሟል።
በሌላ በኩል ጦርነት ያስነሳና መሳሪያ ያነሳ የፖለቲካ ድርጅት በምርጫ ቦርድ ህግ መሰረት እንደሚሰረዝ ስለሚጠቅስ፣ ህጎ ስለማባረር እንጂ ስለመመለስ የሚለው ነገር እንደሌለ የሚጠቅሱ ” ህግ እስካልተቀየረ ድረስ ትህነግ ህጋዊ ሰውነቱን ዳግም የሚያገኝበት አግባብ የለም። ስለሆነም ትህነግ በህይወት ለመቆየት የሚችልበት አግባብ የለም። ይህ ትልቅ ስጋት ሆኖበታል” ሲሉ አስተያየታቸውን ይጀምራሉ።
ትህነግ እንደ ፓርቲ ህልውናውን ይዞ መቀጠል ካልቻለና አማራጩ ብልጽግናን መጠጋት አለያም ስሙን መቀየር ብቻ ነው። ይህ ሲሆን ደግሞ ላለፉት ሃምሳ ዓመታት ” የትግራይ ህዝብ ነጻ አውጪ ግንባር” በሚል እንደ ዕምነት አብዮታዊ ዲሞክራሲን ይዞ ሲጓዝ ከነበረበት ርዕዮተ ዓለም ይለያል። ስብከቱና ፕሮግራሙ ይሟሟል የሚሉ ” ትህነግ ከምንም በላይ በዚህ አጣብቂኝ ውስጥ ነውና ምንም ዓይነት አማራጭ ቢከተል አይገርምም”
ከውህደት ድርድሩ ጋር ስሙ የተነሳው ብልጽግና ዜናው አናቱ ላይ ያነጣጠረ ቢሆንም ይህ እስከተጻፈ ድረስ ምንም አላለም። ይልቁኑም ከትዕግስት በሁዋላ የሚወሰድ እርምጃ የከፋ እንደሚሆን አስታውሶ በመንግስት የጸጥታና ደህንነት ካውንስል አማካይነት መግለጫ አሰራጭቷል።
ይህ መግለጫ ከመውጣቱ በፊት “ትህነግ ከመንግስት ጋር ተስማምቼ ነው” በሚል በራያ አቅጣጫ በፈጸመው ወረራ ከሃምሳ ሺህ በላይ መፈናቀላቸው ይፋ መሆኑን ተከትሎ መንግስት ቀነ ገደብ አስቀምጦ ማስጠንቀቂያ መስጠቱ ተሰምቷል። በዚሁ ማስጠንቀቂያ መሰረት ከሰላማዊ ነዋሪዎች በስተቀር ወደ አማራ ክልል የገቡ ታጣቂዎች ወደ መጡበት እንዲመለሱና በተጀመረው የውይይት አግባብ ችግሮች እንዲፈቱ አሳስቧል። አክሎም አማራጩ የሰላም መንገድ ብቻ እንደሆነም አበክሮ አስታውቋል።
አቶ ጌታቸው ረዳ የፕሪቶሪያውን ስምምነት ተግባራዊነት የማይፈልጉ ወገኖች እንቅፋት እንደሆኑ ቢያመልክቱም፣ እነዚህ አካላት ግን እነማን እንደሆኑ አይገልጹም።
በትግራይ ” ጦርነት በቃን” የሚል አካላት መበራከታቸው ይሰማል። እነዚህ ወገኖች ፖለቲካዊ መፍትሄ ብቻ ሊተኮርበት እንደሚገባ ያምናሉ። መጠናቸው ባይታወቅም የዚህ አመለካከት ደጋፊዎች ብዛት ከስፍራ ስፍራ ይለያያሉ። በዚሁ ዓላማና አጀንዳ ስር በድርጅት ደረጃም እየተንቀሳቀሱ እንዳሉ በተለያዩ ጊዜያት ሲገለጽ ነበር።