“መዓዛን ከሕግም፣ ከዕምነትም አንጻር የሽልማቱን መሥፈርት ጠይቁልኝ”
በአሜሪካ የሩሲያ አምባሳደር አናቶሊ አንቶኖቭ የዚህ ዓመቱ ደፋር ሴቶች ዓለምአቀፍ ሽልማት (2023 International Women of Courage Award) ለናዚ አባል መሰጠቱን በጥብቅ አወገዙ። አምባሳደሩ ያወገዙት ሽልማቱ ለዩክሬናዊቷ ዩሊያ ፓዬቭስካ በመሰጠቱ ነው። ከኢትዮጵያ ይኸው ሽልማት ለመዓዛ መሐመድ ተሰጥቷል። ዜናውን የተከታተሉ “ሽልማቱን ተከትሎ ወለል ብለው የሚታዩ ጉዳዮች አሉ” እያሉ ነው።
ዓለምአቀፉ የሴቶች ቀን በተከበረበት ማርች 8 ቀን 2023ዓም “ደፋር ሴቶች” በመባል በአሜሪካው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር መሥሪያ ቤት መራጭና አቅራቢነት የተለየ ሥራ የሠሩ ሴቶች ሽልማታቸውን ከቀዳማዊት እመቤት ጂል ባይደን ተቀብለዋል።
ይህ ሽልማት ከተሰጣቸው መካከል ዩክሬይናዊቷ ዩሊያ ፓዬቭስካ (Yuliia Paievska) አንዷ ነች። “ታዪራ” (“Taira”) በመባል የምትታወቀው ፓዬቭስካ ከተጀመረ ዓመት ባሰቆጠረው የሩሲያ ዩክሬይን ጦርነት ቁስለኞችን ለማከም የ“ታዪራ መላዕክት” የተሰኘ የፈቃደኛ የአምቡላንስ አገልግሎት የጀመረች ናት። ጦርነቱ እንደተጀመረ በሩሲያ ወታደሮች ተይዛ ከሁለት ወር እስር በኋላ ተለቅቃለች።

ፓዬቭስካ የዛሬ አምስት ዓመት የዩክሬይንን መከላከያ የተቀላቀለች ሲሆን በወቅቱም ስድሳ አንደኛውን (61ኛ) ተንቀሳቃሽ ወታደራዊ ሆስፒታል ስትመራ ነበር። በመቀጠል ግን ከሚሊታሪው በመውጣት የራሷን የፈቃደኛ አምቡላንስ አገልግሎት ጀምራለች።
ለዓለምአቀፍ ሚዲያ በተደጋጋሚ የዩክሬይን ቀኝ አክራሪ ጽንፈኛ ቡድኖች አባል እንደነበረች የምትናገረው ፓዬቭስካ በኒዎ-ናዚነት የሚታወቀው አዞቭ ባታሊዮን (Azov Battalion) የተሰኘው እጅግ አረመኔና ጨካኝ ገዳይ ወታደራዊ ቡድን አባል ወይም ደጋፊ ነች በማለት ሩሲያ ትናገራለች።
የተለያዩ የሩቅ ምስራቅ ታይኳዶና ጁዶ ልዩ ችሎታ ያላት ፓዬቭስካ በፈቃደኝነት የአምቡላንስ አገልግሎት የተሰማራችበት ቦታ የጽንፈኛው አዞቭ ባታሊዮን ቤዝ ባለበት ማሪፑል (Mariupol) ሲሆን በሩሲያ ቁጥጥር ሥር የዋለችውም እዚያው ነበር።
ለዚህ ዓመቱ የደፋር ሴቶች ሽልማት የበቃችውን ፓዬቭስካ የአሸባሪ ድርጅት አባል ነች በማለት ሩሲያ ትከስሳለች። ከዚያ ባለፈም የአሸባሪው አዞቭ ባታሊዮን ጦር አባል ነች በሚልም ተጨማሪ ክስ ታቀርባለች።
የፓዬቭስካን ሽልማት በተመለከተ አምባሳደሩ ሲጠየቁ የመለሱት “በነጩ ቤተ መንግሥት ግድግዳዎች ውስጥ ናዚ ሲወደስና ሲከበር ማየት እጅግ አስጸያፊ ነው” በማለት ነበር።
አምባሳደሩ ሲቀጥሉም “ምናልባት ለማታውቁ ሰዎች ፓዬቭስካ በቅጽል ስሟ ታዪራ ተብላ የምትጠራ ሲሆን ጉሮሮ ቆራጭ፣ አንገት በጣሽ እና እጇ በበርካታ አዛውንቶች፣ ሴቶች እና ሕጻናት ደም የተበከለ የዩክሬይን ወንበዴ አሸባሪ ነች” ብለዋል። “ይቺ ሴት” ይላሉ አምባሳደሩ ሲያብራሩም፤ ይቺ ሴት ማለት አሁን በሩሲያ ቁጥጥር ሥር በሆነው ማሪፑል ከተማ የሁለት ልጆችን ወላጆች ከገደለች በኋላ የልጆቹ እናት መስላና ራሷን ቀይራ ልታመልጥ የሞከረች ናት፤ በኋላ ልጆቹ ሲጠየቁ ካልተባበሩ እነሱንም እንደምትገላቸው ስላስፈራራቻቸው እሺ እንዳሏት ተናግረዋል።
የአዞቭ ባታሊዮን አባላት በ2014 (የዛሬ ዘጠኝ ዓመት) አካባቢ በዩክሬይን ሥልጣን በኃይል ለመያዝ የሞከሩ ሲሆን ከዚያ በመቀጠል በ2018 በዶንባስ ግዛት ኒዎ-ናዚዎችን ሲያሠለጥን የነበረ ድርጅት ነው። እሷም የዚያ ባታሊዮን አባል ሆና በሰብዓዊ ፍጡራን ላይ የከፋ ወንጀል ፈጽማለች በማለት አምባሳደር አንቶኖቭ ተናግረዋል።
“ሌላው መታወቅ ያለበት ጉዳይ” አሉ አምባሳደሩ “የአዞቭ ባታሊዮን ማለት ጸረ ሰው ርዕዮት የሚያራምድ መሆኑ ነው። የባታሊዮኑ መለያ ምልክት ኤስ ኤስ (SS) ተብሎ የሚታወቀው የናዚ ጀርመን ወታደሮች ምልክት ነው። ይህንን የአሜሪካ ባለሥልጣናት ያውቃሉ። በ2019 ዓም አንድ የአሜሪካ የሕዝብ እንደራሴ ይህ ባታሊዮን የውጪ አገር አሸባሪ ተብሎ እንዲፈረጅ ለስቴት ዲፓርትመንት ጥያቄ አቅርበው ነበር። አሁን ግን ሩሲያን ለመጉዳት ስትል አሜሪካ ናዚን ለማወደስና ከፍ ከፍ ለማድረግ ፈቀደች። የአሜሪካ ባለሥልጣናት “ቡናማው መቅሰፍት” ተብሎ ከሚጠራው ሕይወታቸውን ሰውተው ዓለምን ነጻ ባወጡት የአሜሪካና የሶቪየት ወታደሮች ፊት መቆም የማይችሉ ወራዳ መሆናቸውን ነው ያሳዩት” ብለዋል።
በጭከናው እጅግ የሚታወቀው የአዞቭ ባታሊዮን አባል ከሆነችው ፓዬቭስካ ጋር የደፋር ሴቶች ሽልማት ከተቀበሉ መካከል ከኢትዮጵያ መዓዛ መሐመድ ትገኛለች።

በዕለቱ ከተሸለሙት 11 ሴቶች መካከል ከአርጀንቲና የአልባ ሩዌዳ ሽልማት በማኅበራዊ ሚዲያ ውዝግብ ያስነሳ ሆኗል። በአርጀንቲና የመጀመሪያ ትራንስ (transgender) ወይም በጾታ ወንድም ሴትም ወይም ወንድ ወይዘሮ የሆነችው እንደ ሴት ተቆጥራ በሴቶች ቀን ሽልማቱ መሰጠቱ ሴቶችን “የሰረዘ ተግባር” ነው በማለት መሳለቂያ ያደረጉት አጀንዳ ሆኗል።

የአሜሪካ ፖለቲከኞች በበኩላቸውም ወቀሳቸውን አሰምተዋል። የአርካንሳ አገረ ገዢና በጾታም ሴት የሆኑት ሳራ ኸከቢ ሳንደርስ “ለዓለምአቀፍ የሴቶች ቀን እንኳን አደረሳችሁ፤ ዕለቱን ዴሞክራቶች ሴት ማለት ምን ማለት እንደሆነ የረሱበት ቀን አድርገን ለማክበር ጥሩ ጊዜ ነው” ብለዋል። ቅኔው ወንድና ሴት (transgender) ተሸላሚዋን ከመወረፍ ባለፈ አንድም ዴሞክራቱ ፕሬዚዳንት ጆ ባይደን በእርጅና ምክንያት ነገሮችን መርሳታቸውን የጠቆመ ሲሆን ችግሩ በዕለቱ ሽልማቱን ወደሰጡት ባለቤታቸው መሄዱን ያሳየ ሽንቆራ ነው ተብሏል።
በድንገት በዚህ ዓለም አቀፍ ሽልማት ላይ ከኢትዮጵያ “ተሸለሙ” ተብሎ ስማቸው የተጠሩ ሰዎችን አስመልክቶ የገባቸው ወዲያው፣ ያልተረዱ ዘግይቶም ቢሆን ሲገባቸው “ሽልማቱ አሜሪካ ምን፣ ለምንና እንዴት እንደምታበረታታ የሚያሳይ ነው” በሚል ስም አንስተው በቁጭት ሲናገሩ እንደነበር ይታወሳል።

ታዋቂዋ የሬዲዮ አዘጋጅ ዳና ሎሽ ደግሞ “በዓለምአቀፉ የሴቶች ቀን ሴቶችን እያነሱ መሄድ ወይም መኮሰስ በማበረታታቸው ቀዳማይ እመቤት መልካም አድርገዋል። ሴቶችን መሰረዝ ግን አግባብ አይደለም” በማለት በጻፈችው የትዊተር መልዕክት ተሳልቃለች።
በዚሁ መነሻ ይመስላል የመዓዛን ሽልማት አስመልክቶ “አገር ቤትም ያላችሁ ሆናችሁ፣ ከአገር ውጭ የምትገኙ የሚዲያ ሰዎች መቼም መዓዛን መጋበዛችሁ አይቀርምና ሁለት ጥያቄ ጠይቁልኝ” ብለዋል።
ሰዶማዊነት በኢትዮጵያ ሕግ ወንጀል፣ በኢትዮጵያ እምነቶች ዘንድ እስላም ክርስቲያን ሳይል ደግሞ የተረገመ እንደሆነ በማስታወስ የሽልማቱን መሥፈርትና ተሸካሚዎቹን አስመልክቶ እንደ አንድ ኢትዮጵያዊ፣ ከዛም አልፎ እንደ አንድ ሙስሊም እንዴት እንደምትመለከትው፣ በዝርዝር እንዲጠይቅላቸው በጎልጉል በኩል ጥያቄ ያቀረቡት አቶ ያሲን ሳኒ ናቸው። ይህን ያሉትም አዲስ አበባ ለሚገኘው ተባባሪ መረጃ አቀባያችን ነው።
ስቴት ዲፓርትመንት ባለፈው ዓመት በዚሁ ሽልማት ወቅት ሁለት ግብረሰዶማዊያን ወይም ደጋፊዎችን መሸለሙ ይታወሳል። ይህ በተደጋጋሚ እየታየ ያለው የሽልማት ምዘና ብዙዎችን ያነጋገረ ሲሆን “የኢትዮጵያውስ መመዘኛ ሁለት ኪሎ ጥሬ ሥጋ ጭጭ ማድረግ ይሆን?” ሲሉም ተደምጠዋል። የሩሲያው አምባሳደር አሜሪካኖቹን “ወራዳ መሆናቸውን ያሳዩበት ነው” ሲሉ የገለጹበትን አግባብ ወደ ኋላ ሄድ ብሎ የተሸላሚዎችን ዝርዝር መመልከት ለቻለ ግልጽ እንደሆነም አመልክተዋል።
ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ