“የትግራይ ተወላጆች ትህነግ ለፈጸመው ወረራ፣ ዘረፋ፣ ማፈናቀልና የግድያ ተግባራት የተቀናጀ የፖለቲካና የሚዲያ ድጋፍ ሰጥተዋል። በተለይም በትግራይ ክልል መቀሌ ከተማ ሮማናት አደባባይ ላይ የተለመደው አይነት የፈንጠዝያ ድጋፍ ሲደረግ ሰንብቷል ሲል አብን ወቀሰ። አማራና ሰላም ወዳድ ወገኖች ለትግል እንዲነሱ ጥሪ አቀረበ። ” “የህዝባችንን ድምጽ የሚቀማና የሚያፍን የ’አማራ ስብስብ’ ለአማራ ክልል ተግዳሮት ሆኗል” ሲል በአማራ ስም ከትህነግ ጋር ለትህነግ የሚሰሩትን አወገዘ።
ሰሞኑን በሰሜን ወሎ ራያ አካባቢዎች በተደራጀ መንገድ ወረራ በመፈፀም በብዙ ሽህ የሚቆጠሩ የአካባቢው ኗሪዎችን በማፈናቀል በራያ ባላ፣ አላማጣና ኦፍላ ወረዳዎች እንዲሁም በኮረም ከተማ የሚገኙትን የህዝብ፣ የመንግስትና የሃይማኖት ተቋማትን ንብረት ዘርፏል፤ የአካባቢውን አርሶ አደሮች አዝመራ ዘርፏል በቃጠሎ ጭምር አውድሟል፣ ቤት ለቤት እየገባ ጌጣጌጦችን ሳይቀር ከእናቶች ላይ ቀምቶ ወስዷል፣ የቤት እንስሳቶችን አጓጉዟል፣ ከአርሶ አደሩ ጓዳ የተገኘን እህል ጭኗል ወዘተ። በተመሳሳይ ህወሀት በጎንደር በኩል የወረራና የጥፋት ተግባራትን ለመፈፀም አቅዶ እየተንቀሳቀሰ መሆኑን መረጃዎች ያሳያሉ።
ከአማራ ብሄራዊ ንቅናቄ (አብን) በወቅታዊ ጉዳዮች የተሰጠ መግለጫ
ለሕዝባዊ ወያኔ ኃርነት ትግራይ (ህወሃት) ህዝብ፣ ሀገር እና ሰላም ተራ የፍጆታ ጉዳዮች መሆናቸው ይታወቃል።
ህወሃት ወያኔ የፕሪቶሪያ ስምምነት ዋና ማጠንጠኛ የሆነውን የትጥቅ መፍታት ጉዳይ ባለመፈፀምና በተግባር በመጣስ በጠላትነት ፈርጆ ሰለባ ያደረገውን የአማራ ህዝብ በውስጥ ምልምሎቹ (the quisling) አማካኝነት በወዳጅነት ስም ቀርቦ ህዝባችንን ዳግም ለጥቃት ለማጋለጥ ቀደም ሲል የነበረውን የሽብር ሰንሰለት እንደገና በማነቃቃት በአማራ ክልል እና በተለያዩ የሃገራችን ክፍሎች የጥፋት ስምሪቱን አጠናክሮ ቀጥሏል።
ሰሞኑን በሰሜን ወሎ ራያ አካባቢዎች በተደራጀ መንገድ ወረራ በመፈፀም በብዙ ሽህ የሚቆጠሩ የአካባቢው ኗሪዎችን በማፈናቀል በራያ ባላ፣ አላማጣና ኦፍላ ወረዳዎች እንዲሁም በኮረም ከተማ የሚገኙትን የህዝብ፣ የመንግስትና የሃይማኖት ተቋማትን ንብረት ዘርፏል፤ የአካባቢውን አርሶ አደሮች አዝመራ ዘርፏል በቃጠሎ ጭምር አውድሟል፣ ቤት ለቤት እየገባ ጌጣጌጦችን ሳይቀር ከእናቶች ላይ ቀምቶ ወስዷል፣ የቤት እንስሳቶችን አጓጉዟል፣ ከአርሶ አደሩ ጓዳ የተገኘን እህል ጭኗል ወዘተ። በተመሳሳይ ህወሀት በጎንደር በኩል የወረራና የጥፋት ተግባራትን ለመፈፀም አቅዶ እየተንቀሳቀሰ መሆኑን መረጃዎች ያሳያሉ።
ይህ አሰቃቀቂ እና ያልተቋረጠ ተደጋጋሚ ግፍ በህዝባችን ላይ እየተፈፀመ ባለበት ሁኔታ በተጓዳኝ ሁለት አሳፋሪና አደገኛ የማህበረ-ፖለቲካ ዝንባሌዎች ጎልተው ተስተውለዋል:-
1/ በአንድ በኩል የትግራይ ተወላጆች ለዚህ ወረራ፣ ዘረፋ፣ ማፈናቀልና የግድያ ተግባራት የተቀናጀ የፖለቲካና የሚዲያ ድጋፍ ሰጥተዋል። በተለይም በትግራይ ክልል መቀሌ ከተማ ሮማናት አደባባይ ላይ የተለመደው አይነት የፈንጠዝያ ድጋፍ ሲደረግ ሰንብቷል።
2/ በተቃራኒው በአማራ ስም ዘወትር የሚምል ሆኖም በህዝባችን ላይ የሚፈፀመውን ግልፅና በቀላሉ የሚታይ (obvious and noticeable) ሰቆቃ የሚክድ እና የሚያድበሰብስ፣ የህዝባችንን ድምጽ የሚቀማና የሚያፍን የ”አማራ” ስብስብ መኖሩ በግልፅ ተስተውሏል።
ይህ በህዝባችን ላይ እየተፈጸመ የሚገኘው ጥቃት እና ብሶት ፍፁም እንዳይታወቅ እና እንዳይነገር ከውስጥ እና ከውጭ በሸፍጥ የተሰለፈ ግልብና መንደርተኛ ስብስብ የትግሉ ግንባር ቀደም ተግዳሮት ሆኗል። በመሆኑም በተለይም የድርጅታችን አባላት ደጋፊዎችና መላው ህዝባችን ፍትህ ወዳድ ከሆነው የኢትዮጵያ ህዝብ ጋር በመሆን እንዲህ አይነቱን የተዛነፈ የሀሳብና የተግባር አካሄድ በመራቅና በማስተካከል ለቀጣይ ትግል ዝግጁ መሆን ይኖርበታል።
ህወሃት በጠባጫሪነት የጀመረው ጦርነት ትላንት ወረራ በፈጸመባቸው የአማራና የአፋር ክልሎች መጠነ ሰፊ ውድመት ያደረሰ ሲሆን በቆሰቆሰው ጦርነት የራሱ የትግራይ አካባቢወችም ጭምር በጦርነቱ መጠነኛ ውድመት አልገጠማቸውም አይባልም። ሆኖም በተለመደ የ”እኛ ብቻ ተጎድተናል” የጩኸት ዘመቻ አለማቀፉን ማህበረሰብ በማምታታት፣ መንግስትና ሀገር ላይ ሰፊ ጫና በመፍጠር፣ በህወሃት ወረራ ዘረፋና ውድመት የደረሰባቸው የአማራ አካባቢወች የደረሰው መጠነ ሰፊ የሰብአዊና ቁሳዊ ጉዳት ጆሮ እንዳያገኝ በማድረግ ጭምር ህዝባችን ከውስጥም ከውጭም ተገቢውን ድጋፍ ሳያገኝ እንዲቆይ አድርጓል። ይህ ሁሉ የህወሃት የማይነጥፈው በአማራ ህዝብ ላይ የያዘው የጠላትነት መንፈስ አካል ነው።
በመሆኑም መንግስትም ይሁን አለማቀፍ “የሰብአዊ መብት” እና “የተራድኦ” ድርጅቶች ነን የሚሉ አካላት በተለይ ህወሃት በጦርነት ባወደማቸው አካባቢወች ያደረሰውን ሰፊ ጉዳት ለመጠገን በቂ የመልሶ ማቋቋሚያ ስራ ሲሰሩ አልተስተዋለም። ይልቁንም መንግስታዊ ያልሆኑና የውጭ ተራድኦ ድርጅቶች (NGOs) ከአማራ ክልል ነቅለው በመውጣትና ድንኳናቸውን ትግራይ ውስጥ በመትከል ስራ ሲሰሩ መቆየታቸውን እናውቃለን። ህዝባችን የሰላም አየር ካገኘ ከራሱ አልፎ ለሌላውም የሚተርፍ ታታሪ ህዝብ በመሆኑ በተራድኦ ስም የሚመጣ መናኛ እርዳታ በምንም መልኩ ከችግሩ የማያላቅቀው በመሆኑና ይልቁንም የስንፍናና የጥገኝነት ባህል የሚያጣባው በመሆኑ ከሰፊው ኢትዮጵያዊ ወገኑ ጋር የሚደጋገፍበትን አቅም እየገነባ በተራድኦ ስም ከሚመጣለት መናኛ እርዳታ ጨርሶ የሚላቀቅበትን ሁኔታ መፍጠር ቀጣይ የምናረጋግጠው የቤት ስራችን ይሆናል።
ህወሃት በህዝባችን ላይ የፈጸመው ወረራ ውድመትና ሰብአዊ ቀውስ በቂ እንዳልሆነ ሁሉ ተጨማሪ የወረራና የጦርነት ጉሰማ ውስጥ ሲገባ በመንግስት በኩል አሁንም ድረስ የሚታየው የጎላ የሃላፊነት እና የግልፀኝነት ጉድለት ሃገራችን ወደባሰ ችግር ውስጥ እንድትገባ ግንባር ቀደም አስተዋፅኦ አድርጓል ብሎ ድርጅታችን አብን ያምናል።
በመሆኑም በተለይም የአማራ ተወላጆች በጠላት በኩል የሚነዙ የፕሮፖጋንዳ ማደናገሪያዎችን እውነተኛ አላማ በመረዳት ዳግም ለጥቃት ላለመጋለጥ አስፈላጊውን ራስ የመከላከል ዝግጅት እንዲያደርግ፣ አንድነቱን እንዲያጠናክር እና በዚህ ረገድ የከፊሉ አካባቢ መጠቃት የመላው ህዝባችን መጠቃት እንዳልሆነ በማስመሰል መረጃዎች እንዳይወጡና እንዳይጋለጡ ከጠላት ባልተናነሰ በስሙ እየማሉ ሸፍጥ የሚፈፅሙ አካላትን እንዲቃወምና እንዲታገል፤
በመንግስት በኩል፤ ሃገራዊና ቀጠናዊ የፖለቲካ እና የደህንነት ጉዳዬችን በግልፅና በሃላፊነት ስሜት ለመፍታት አስፈላጊውን ትጋት እንዲያደርግና እንዲያስተካክል፣ ችግሮቹ ተባብሰው ወደ ለየለት ግጭት ከመገባቱ በፊት ተገቢውን ርምጃ እንዲወስድ በጥብቅ እያሳሰብን፤ ህዝባችን በተደጋጋሚ በደረሰበት ሰፊ መፈናቀሎች ምክንያት አቅሙ ስለተዳከመ እና ተጨማሪ ችግሮችን ለመቋቋም አዳጋች ስለሚሆንበት የህወሃት ታጣቂዎችን ከአካባቢዎቹ ባስቸኳይ በማስወጣት የተፈናቀሉ ወገኖቻችን ወደ ቀያቸው እንዲመለሱ እንዲያደርግና ተገቢ መንግስታዊ ሀላፊነቱን እንዲወጣ ስንል ጥሪ እናደርጋለን።
ሚያዝያ 14/2016 ዓ.ም
አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ