በሲዳማ ክልል ኃላፊነታቸውን በአግባቡ ባልተወጡ 384 አመራር አካላት ላይ ፖለቲካዊ ውሳኔ መሰጠቱን በብልፅግና ፓርቲ የሲዳማ ክልል ጽህፈት ቤት አስታወቀ። ፖለቲካዊ ውሳኔ ከተላለፈባቸው መካከል 146 ከአመራርነት እንዲነሱ ሲደረግ፤ ለ238ቱ ማስጠንቀቂያ ተሰጥቷል።
በክልሉ “ተለውጦ ሀገርን ለመለወጥ” በሚል መሪ ሃሳብ ሲያካሂደው የሰነበተው ፓርቲው የአመራርና አባላት የአቅም ግንባታ ሥልጠና ተኮር የግምገማ መድረክ ትናንት ተጠናቋል።
የጽህፈት ቤቱ ኃላፊ አቶ አብርሃም ማርሻሎ የመድረኩን መጠናቀቅን አስመልክተው ትናንት ማምሻውን ለመገናኛ ብዙሃን መግለጫ ሰጥተዋል።
ኃላፊው በመግለጫቸው እንዳሉት ለዜጎች ክብር መቆም፤ ጎጠኝነትና ሌብነትን መፀየፍና ማስወገድ ፍትሃዊ ተጠቃሚነትን በማረጋገጥ በመደመር እሳቤ ሀገርንና ህዝብን ማሻገር የብልፅግና ፓርቲ ግብ ነው።
ለህዝብና ለሀገር መለወጥና ቅን አስተሳሰብ ማጎልበት ጊዜ የማይሰጠው ጉዳይ በመሆኑ ለሁሉም የፓርቲው አመራሮችና አባላት የአቅም ግንባታ ስልጠና መድረክ ተዘጋጅቶ መሰጠቱን አብራርተዋል።
አቶ አብርሃም በመግለጫቸው እንዳመለከቱት መድረኩ በአገልግሎት አሰጣጥና በዳተኝነት፣ ግለኝነት፣ ጥቅመኝነት፣ ጎጠኝነት፣ ስንፍናና ሌሎች መሰል ህዝብን ያማረሩ ችግሮች እንዳሉ በግልፅ ተገምግሟል።
የህዝብን ጥቅም ማስቀረት ሊደረስበት የተወጠነውን የብልፅግና ጉዞ የሚያደናቅፉ በመሆናቸው በአጭሩ ለመቅጨት መወሰኑን አስረድተዋል።
በመሆኑም ከፓርቲው ስነ ምግባርና አስተሳሰብ ያፈነገጡ አካሄዶች፣ አስተሳሰቦችና ተግባሮች ፓርቲው ተሸክሞ እንደማይጓዝ ከጋራ መግባባት ላይ መደረሱን በመግለጫቸው ጠቁመዋል።
የብልፅግና ፓርቲ የመደመርና የወንድማማችነት እሴት መሆኑን አቶ አብርሃም በመግለጫቸው በአፅኖት ተናግረዋል።
በገቢዎች፤ በንግድና በመሬት አስተዳደር ዙሪያ የሚስተዋሉ የሌብነት፣ የጉቦኝነትና መሰል ህዝብን ያማረሩ ብልሹ አሰራሮችን ፓርቲው በፍጹም እንደማይታገስም ገልጸዋል።
በዚህም በክልሉ በየደረጃው የሚገኙ 2ሺህ 490 አመራሮች በግልፅ መረጃዎች በመሞገት ጭምር የማጥራት ሥራ መሰራቱን አቶ አብረሃም በመግለጫቸው አመልክተዋል።
“በዚህ መሰረት በተጠቀሱት የመልካም አስተዳደር ችግሮች እጃቸው ያሉባቸው 384 የአመራር አካላት ተለይተው ፖለቲካዊ ውሳኔ ተላልፎባቸዋል” ብለዋል።
ከዚህም ባሻገር ህጋዊ እርምጃ መውሰድ እንዲቻል የስነምግባር ጉድለታቸውን የሚያጣራ ከዐቃቤ ህግ፣ ከፖሊስና ከሌሎች አካላት የተውጣጣ ግብረ ኃይል ተቋቁሞ ስራ ጀምሯል ብለዋል።
በቀጣይም የፓርቲውን የሥነምግባር እሴቶችና መሰረታዊ መርሆዎችን አክብረው ሕዝብን በቅንነትና በታማኝነት የማያገለግሉ የአመራር አካላት ከፓርቲው ጋር አብረው መጓዝ እንደማይችሉም አረጋግጠዋል።
በክልሉ እስከታችኛው እርከን ድረስ በተካሄዱ የአቅም ግንባታ ሥልጠና ተኮር የግምገማ መድረክ የህዝቡና የፓርቲው አባላት ተሳትፎ ከፍተኛ መሆኑን አቶ አብርሃም ገልጸዋል።
ኃላፊው እንዳሉት ይህ ብልፅግና ፓርቲ በቀጣይ ሊያከናውናቸው ለወጠናቸው የልማትና የፖለቲካ ስራ ስኬት የማይነጥፍ አቅም ነው።
በዘላቂነት ችግር ፈቺ የሆነ የስራ ዕድል ለዜጎች መፍጠር፤ የወጣቱን አቅም፤ ዕውቀትና ክህሎት መጠቀም የጋራ መግባባት የተደረሰባቸው ጉዳዮች መሆናቸውን አስታውቀዋል።
ሁሉንም ዕድሎች በመጠቀም አርዓነት ያለው ስራ ለመስራት ዕድሉ የተሰጣቸው አመራር አካላት ህዝቡን በማስተባበር የታለመው የብልፅግና ጉዞ ከግብ የማድረስ ኃላፊነታቸውን በአግባቡ እንዲወጡ አሳስበዋል ሲል ኢዜአ ዘግቧል።
በመድረኩም “ከፈተና ወደ ልዕልና” በሚል መርህ ቃል በሀገር አቀፍ ደረጃ በሚያካሄደው የፓርቲው የመጀመሪያው ጉባኤ ክልሉን የሚወክሉ አባላት ምርጫ መካሄዱንም ጨምረው ገልጸዋል።
ኢፕድ