መንግስት ከዓለም ዓቀፉ የገንዘብ ድርጅት ጋር ውይይት ላይ መሆኑ መጠቀሱን ተከትሎ ኢዜማ ” የብርን የመግዛት አቅም ማዳከም የኢትዮጵያን የኢኮኖሚ ሥብራት አይጠግንም!” በሚል ኢዜማ አሳብ ሰጠ።
ድርጅቱ በኢትዮጵያ ከለውጡ በሁዋላ በርካታ የኢኮኖሚ ማሻሻያ ውሳኔዎችና ርምጃዎች መከናወናቸውን አሞካሽቶ በተለያዩ ምክንያቶች አገሪቱ የገጠማትን የውጭ ምንዛሬ እጥረት ለመቅረፍ በሚል የገንዘብን የመግዛት አቅም ማቀነስ የሚለውን የአበዳሪዎች መርህ መቀበል አሉታዊ ገጹ እንደሚያመዝን አመልክቷል።
አዲስ አበባ ላይ በተደረገ የመጀመሪያው ውይይት ዓለም ዓቀፉ የገንዘብ ድርጅት የብር የመግዛት አቅም እንዲቀንስ ያቀረበውን ጥያቄ መንግስት እንዳልተቀበለው ይታወሳል። አሁንም በአመኢሪካ በተካሄደ ውይይት ይህንን አቋሙን መንግስት ስለመቀየሩ ከማንም ወገን የተባለ ነገር የለም። ኢዜማም በትቅል የአሰራሩን ልምድ በማጣቀስ ስጋቱን ከማጋራቱ በቀር ስምምነት ለመደረጉ መረጃ እንዳለው አልጠቆመም።
ከኢትዮጵያ ዜጎች ለማኀበራዊ ፍትሕ (ኢዜማ) የተሠጠ መግለጫ
* የብርን የመግዛት አቅም ማዳከም የኢትዮጵያን የኢኮኖሚ ሥብራት አይጠግንም!
ኢትዮጵያ ሀገራችን የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ መንግሥት ወደ ሥልጣን መምጣትን ተከትሎና ከዚያም በፊት ከለውጡ ጋር ተያይዞ ኢኮኖሚያችን ካለበት የኢኮኖሚ መዛባት ይታደጋሉ የተባሉ በርካታ ምጣኔ ሀብታዊ የማሻሻያ ማዕቀፎችን በመተግበር ላይ ትገኛለች፡፡
በዚህም ምክንያት የዓለምአቀፍ የገንዘብ ተቋማት ሲሰጡ የነበረው የኢኮኖሚ ድጎማዎች የሰሜኑ የሀገራችን ክፍል የተከሰተውን ጦርነትን ተከትሎ እና በሌሎች ማሻሻያውን በሚመለከት በተፈጠሩ ልዩነቶች ምክንያት ዓለምአቀፍ ተቋማት ከድጋፋቸው ወደኋላ በማለታቸው፤ ከአጎዋ ተሳትፏችን በመታገዳችን፤ የምናገኛትም ጥቂት የውጭ ምንዛሪ ለእዳ መክፈያ እየዋለ በመሆኑ፤ እንዲሁም በጦርነቱ ምክንያት የአምራች ዘርፉ ከፍተኛ ተግዳሮት ስለገጠመው የውጭ ምንዛሪ ክምችታችን ዝቅተኛ ደረጃ ላይ እንደሚገኝ መረጃዎች ያሳያሉ፡፡
ይህን ለማስተካከል መንግሥት ከዓለም አቀፍ የፋይናንስ ተቋማት ጋር የጀመራቸው ውይይቶች የተሳኩ እንዲሆኑ፤ የፋይናንስ ተቋማትም ድጋፋቸውን በማድረግ የኢትዮጵያን ኢኮኖሚ በመደገፍ በዚህ ምክንያት ሊከሰቱ የሚችሉትን ሀገራዊና ቀጣናዊ ችግሮች ለመፈታት ጥረት ያደርጋሉ ብለን እናምናለን፡፡
ዛሬም ይህን መሰል ድጋፍ ለማድረግ የዓለም አቀፍ ፋይናንስ ተቋማት ከሚጠይቋቿው ኢኮኖሚ ማሻሻያ ማዕቀፎች አንዱ የብርን የመግዛት አቅምን ማዳከም (devaluation) እንደሆነ የሚጠበቅ ነው፡፡ ይሁንና በዓለም አቀፍ የገንዘብ ተቋማት ግፊት የሚደረግ የብርን የመግዛት አቅም የማዳከም ስራ ሊያመጣ ከሚችለው ታሳቢ ጥቅም ይልቅ በዜጎች ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ደኅንነት ላይ ከፍ ያለ አሉታዊ ተጽእኖ ሊያመጣ ከመቻሉም በላይ፤ እንደ ሀገር የጊዜያዊ የውጭ ምንዛሪ ችግራችንን ሊያቃልልም ሆነ ዘለቄታዊ መፍትሄ ሊያመጣ የሚችልበት እድል አለ ብለን አናምንም፡፡
ይህም በንድፈ ሀሳብ ደረጃ ሳይሆን በሀገራችን ተሞክሮ ታይቶ በተደጋጋሚ ያልተሳካ የፖሊሲ አማራጭ በመሆኑ መንግሥት ወደዚህ ውሳኔ ከመግባቱ በፊት እንድምታው ላይ በሰከነ መንፈስ እንዲያስብበት በአፅዕኖት ለማሳሰብ እንፈልጋለን፡፡
በመሠረቱ ሀገሮች የገንዘባቸውን የመግዛት አቅም ከፍ በማድረግ ወይም በማዳከም ከንግድ ሸሪኮቻቸው አንጻር ያላቸውን የንግድ ሚዛን ለማስተካከል ወይም ትርፍ የንግድ ሚዛን (ከፍ ያለ የውጭ ምንዛሪ ክምችት) እንዲኖራቸው የውጭ ምንዛሪ ፖሊሲን መጠቀማቸው የተለመደ ነው፡፡ በንድፈ ሀሳብ ደረጃ የሀገር ውስጥ ገንዘብ የመግዛት አቅም ማዳከም እንደ ፖሊሲ አማራጭ የሚቀርበው፤ ሀገሮች ወደ ውጭ የሚልኩትን ሸቀጥ የሀገር ውስጥ ዋጋ እንዲቀንስ በማድረግ፤ ከሌሎች ተመሳሳይ ሸቀጥ ከሚያቀርቡ ሀገሮች አንፃር በዓለም አቀፍ ገበያ የተሻለ ተወዳዳሪ ስለሚያደርጋቸው ገዥዎች ብዙ ሸቀጥ ይገዛሉ፤ ይህም የውጭ ምንዛሪ ክምችታቸውን በማሳደግ ከንግድ ሸሪኮቻቸው ጋር ያላቸውን የንግድ ሚዛን ያስተካክልላቸዋል የሚል መነሻ/ታሳቢ (assumption) ታሳቢ በማድረግ ነው፡፡
ይሁንና ይህ አረዳድ ከግምት የማያስገባቸው ጉዳዮች በተለይ እንደኛ ባሉ ያላደጉ ሀገሮች ፖሊሲው ውጤታማ እንዳይሆን የሚያደርጉ ብዙ መዋቅራዊ ችግሮች ያሉ መሆኑ ነው፡፡ አንደኛውና የመጀመሪያው መዋቅራዊ የሆነ የማምረት (የአቅርቦት) ችግር መገለጫ የሆነባቸው እንደኛ ያሉ ሀገሮች በፖሊሲው ምክንያት ሊያገኙ የሚችሉት ጥቅም፤ የማምረት አቅማቸው ደካማ በመሆኑና በውጭ ምንዛሪ የሚገኙ ግብአቶች ላይ ያለው ጥገኝነት ከፍተኛ በመሆኑ ከዚህ ዓይነት ፖሊሲ እርምጃ የሚገኘውን ጥቅም ያሳጣል፡፡ ሌላኛው የዚህ ታሳቢ ጉድለት ሌሎች ተመሳሳይ ምርት ወደ ዓለምአቀፍ ገበያ የሚልኩ ሀገሮች ተመሳሳይ ፖሊሲ ሊጠቀሙ መቻላቸውን ከግምት ያለማስገባቱ ነው፡፡
በተጨማሪም ምርት እንኳን በብዛት ማቅረብ ቢቻል በጥራት ተወዳዳሪ የሆኑ ምርቶችን ማቅረብ አንዱ የአምራች ተቋሞቻችን ችግር በመሆኑ ፖሊሲው ታሳቢ የሚያደርጋቸውን ጥቅሞች ማግኘት አዳጋች ሆኖ መገኘቱ በተግባር የታየ ጉዳይ ነው፡፡
በኢትዮጵያ ውስጥ የገንዘብን የመግዛት አቅም ማዳከም በሚመለከት የዘርፉ ባለሙያዎች ባደረጓቸው ጥናቶች የተለያየ ውጤቶች ተገኝተዋል፡፡ ከግኝቶቹ ዋነኛውና ካለው ነባራዊ ሁኔታ ተናባቢ የሆነው ከመዋቅራዊ የአቅርቦት ችግር ጋር ተያይዞ፤ ይህን ችግር ሳይፈቱ ፖሊሲውን ተግባራዊ ማድረግ የተፈለገውን ውጤት የማያስገኝ፤ የዋጋ ንረትን በማስከተል በተለይም በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ያሉና በደሞዝ የሚተዳደሩ ዜጎችን ኑሮ ከድጡ ወደማጡ ከመውሰዱም በላይ ለፖለቲካዊ ቀውስ መነሻ ምክንያት ሊሆን ይችላል የሚለው ነው፡፡
በመሰረቱ የውጭ ምንዛሬን በባንኮች እና በጥቁር ገበያው መካከል እኩል ብናደርገው እንኳን የውጭ ምንዛሬ አቅርቦት ፍላጎቶችን በአስተማማኝ እና በዘላቂ ሁኔታ በሚመልስ መለኩ ባልተስተካከለበት፤ የጥቁር ገበያው በማግስቱ ከነበረበት እንደሚጨምር እና ልዩነቱ መልሶ እንደሚፈጠር ግልፅ ነው። ለዚህ ዋና መፍትሄው የውጭ ምንዛሬ አቅርቦት ፍላጎትን በሚያረካ መልኩ እንዲጨምር ማድረግ እንጂ የብርን የመግዛት አቅም ማዳከም ሊሆን አይችልም።
በእኛ እምነት፤ ሀገራችን ከዚህ በፊት ከተገበረችው ተመሳሳይ ፖሊሲ ውጤቶች በመነሳት፤ አሁን ካለንበት የግጭት እና የጦርነት ድባብ ባልወጣንበት ሁኔታ፤ የማምረት አቅማችን በውጭ ግብአቶች ላይ ያለውን ከፍተኛ ጥገኝነት መፍትሄ ሳያገኝ ተግባራዊ የሚደረግ ፖሊሲ ከጥቅሙ ይልቅ ጉዳቱ የሚያመዝን በመሆኑ መንግሥት ፖሊሲውን የሚደግፉ የዘርፉ ምሁራንን ብቻ ሳይሆን የሚቃወሙትንም ምሁራን ምክር ሰምቶ ለሀገራችን የሚጠቅም እርምጃ እንዲወስድ በአጽንዎት እያሳሰብን፤ በዓለማቀፍ ገንዘብ ተቋማት ጥያቄ ሊተገበር የታሰበው ይህ የፖሊሲ አቅጣጫ ትግበራ እንደ ኢዜማ አምርሮ የሚቃወመው መሆኑን እንገልጻለን፡፡
በመጨረሻም በተደጋጋሚ የተጓዝንበትን እና ውጤት ያላመጣንበትን መንገድ በመጓዝ የተለየ ውጤት መጠበቅ ቀውስ ከመጥራት ውጪ መፍትሔ እንዳልሆነ እያሳሰብን፤ የሀገር በቀል ኢኮኖሚ ሪፎርም መኖር ካለበት ከውጭ በሚመጣ ግፊት ላይ ሳይሆን ሀገር በቀል መፍትሔ ላይ በማተኮር መሆን ይኖርበታል፡፡ ለዚህም ባለድርሻ አካላትን ያካተተ ዘላቂ መፍትሔ መፈለግ ላይ ትኩረት ይደረግ የሚል ጥሪያችንን እናቀርባለን፡፡
የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኀበራዊ ፍትሕ (ኢዜማ) ሚያዝያ 12/2016 ዓ.ም አዲስ አበባ ፤ ኢትዮጵያ