በኢትዮጵያ የአሜሪካ አምባሳደር ጊታ ፓሲ ጡረታ እንደሚወጡ ማሳወቃቸውን ተከትሎ አዲስ አበባ ላለው ኤምባሲዋ ጊዜያዊ ጉዳይ አስፈጻሚ መሰየሟን የአሜሪካ ውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት አስታወቀ።
አሜሪካ በአዲስ አበባ ላለው ኤምባሲዋ ትሬሲ አን ጃኮብሰንን ነው በጊዜያዊነት በኃላፊነት ቦታ ላይ ያስቀመጠችው።
አሜሪካዊቷ ዲፕሎማት ትሬሲ አን ጃኮብሰን በቱርክሜኒስታን፣ ታጂኪስታንና ኮሶቮ የአሜሪካ አምባሳደር ሆነው አገልግለዋል፤ በተጨማሪ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ለዓለም አቀፍ ድርጅት ጉዳዮች ተጠባባቂ ረዳት ፀሀፊ ሆነውም አገልግለዋል።
የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት ኃላፊው አንቶኒ ብሊንከን አምባሳደር ትሬሲ አን ጃኮንሰንን ለዚህ ኃላፊነት ሲመርጡ በሰሜን ኢትዮጵያ ያለው ጦርነት እንዲያበቃ አስቸኳይ ተኩስ አቁም እንዲደረግ፣ የሰብአዊ መብት ጥሰቶች እንዲቆሙ፣ እርዳታ ያለገደብ እንዲቀርብ ግጭቱን የሚያስቆም ድርድር እንዲደረግ አምባሳደር ጊታ ፓሲ ሲያከናውኑ የነበረውን ተግባር ይቀጥሉበታል ተብሏል።