ፖለቲካ ባብዛኛው የትርክት የበላይነትን narrative control የመቆጣጠር ስራ ነው። ትርክቱን መቆጣጠር ስትችል የሀገር ውስጥ ፖለቲካውም በተሻለ ይረጋጋል ከውጭ ሀገራት ጋር የሚደረግ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነቱም በጥሩ መልኩ ሊካሄድ ይችላል።
የተሸጠው ትርክት – አቢይ አህመድ አሀዳዊ ነው
ህወሃት ለተከታዮቿና የአለም አቀፍ ማህበረሰቡ የተለያዩ ትርክቶች ትሸጣለች። ለአብዛኛው ትግራዋይ ህወሃት አንበሳ ነች ፣ ከደብረብርሃን መቀሌ የሸሸችው ከአሜሪካ ስልክ ተደውሎላት እንጂ ሸገርን ምሳ ለማድረግ ምንም አይገዳትም። ብዙው ትግራዋይ ‘ ትግራይ የኢትዮጵያ ሞተር ነች ‘ ያለውን አቢይ የትግራይ ህዝብ ጠላት አድርጎ ያስባል። ከሚኒሊክ አንስተህ እስከ አቢይ አህመድ ድረስ የትግራይ ህዝብ ጠላት ያልተባለ መሪ የለም። ህዝቡ ደግሞ እንዴት ? ብሎ አይጠይቅም ልጆቹን ክላሽ ያሸክማል የማያባራ ጦርነት የማያልቅ ረሀብና ቸነፈር ውስጥ ሲገባ ሁሌም ጣቱን ወደ አራት ኪሎ ይጠቁማል። ይኼ የተሸጠ ትርክት ጥያቄ የተነሳበት ቀን ህወሃት ወዮላት !
የአባይ ግድብ ተሽጧል ትርክት :

አፈሩ ይቅለላቸውና ስዩም መስፍንም ይሁኑ ጌታቸው ረዳ ” አቢይ አህመድ ግድቡን ሸጦታል ” ሲሉ ሊተላለፍ የተፈለገው ትርክት አባይ የመለስ ዜናዊና የህወሃት ሌጋሲ ብቻ እንዲሆን ነበር። ዋናው መልዕክት ከእኛ በላይ ትላልቅ ሀገራዊ ፕሮጄክቶችን ማንም ሊያልምም ሊፈጽምም አይችልም የሚል ነሆለል ድምዳሜ ነው። አቢይ አህመድ የፕሮጄክት ሰው ነው የእነ ስዩምን ትርክት ባናቱ ለመድፋት ሁለት አመታት ብቻ ነው የፈጀበት። ህወሃት ኖረም አልኖረም የአባይ ግድብ ይከወናል ፍጻሜውም ቅርብ ነው።
መጪው የልማት ትርክት
ህወሃት ኢትዮጵያ ላይ ልማትንም ፣ ጸጥታንም ዲሞክራሲንም እኔ ብቻ ነኝ ማስፈን የምችለው የምትለውን ትርክቷን ለምዕራባውያን በቅጡ ሸጣዋለች። አራት ኪሎ ላይ አቢይ ተቀምጦ አሁንም ያለህወሃት የአፍሪቃ ቀንድን ፖለቲካ መሾፈር የሚችል ሀይል የለም ብለው የሚያስቡ ምዕራባውያን የቀድሞ ዲፕሎማቶች ጥቂት አይደሉም። ችግሩ ያለው ታዲያ የኢትዮጵያ የጸጥታ መውቅርም ይሁን ልማት ህወሃታውያን እንደሚያስቡት ደካማ አለመሆኑ ላይ ነው። አልሸባብን ገርፎ ሶማሊያ ውስጥ buffer security zone ስላቋቋመው መከላከያ ሰራዊታችን የውጭ ሀገር መገናኛ ብዙሃን ዝም ማለትን መርጠዋል። ምክንያት ? ለወራት ሰራዊቱ ተዳክሟል ሲሉ ከርመዋላ ! የተተፋ አይላስ ሆኖባቸዋል።

ኢኮኖሚውም እንደዚያው ነው። የኢትዮጵያ ግብርና እመርታ እያሳየ ነው ምዕራባውያኑም ይህንን እውነታ ያውቁታል አደባባይ ወጥተው እንዳይመሰክሩ አሁንም የቀደመውን የራሳቸውን ትርክት ማፍረስ ሊሆንባቸው ነው። የስንዴ ምርታችን ፣ አረንጓዴ አሻራ ፣ agricultural diversification ብዙ ተስፋ ያላቸው ጅምሮች አሉን ፈረንጆቹ ግን ጸጥ ማለት መርጠዋል።
ህውሃት ብቻ ነው ኢትዮጵያን ሊሾፍር የሚችለው የሚለው ትርክት እያደር ጉድጓድ እየገባ ነው። አረንጓዴ የስንዴ ማሳ ባየን ቁጥር ህወሃታውያን ” ሰው እያለቀ ስንዴ ምን ዋጋ አለው ? ” ይሉናል። የጅምላ ፍጅቱን ከኦነግ ጋር ሆነው የሚከውኑት ግን እነርሱው ናቸው። የጽጥታ ሀይላችን እየተጠናከረ በሚሄድበት በእያንዳንዱ ቀን ይኼም የፍጅት ትርክት ጉድጓድ መግባቱ አይቀርም።