በህገወጥ መልኩ በኢትዮጵያ የሚኖሩ ዜጎች ከጥር አንድ ጀምሮ ወደ ህጋዊ መስመር እንዲገቡ ያሳሰበው የኢሚግሬሽንና የዜግነት አገልግሎት
እስከ ጥር 30 ቀን 2016 ዓ.ም ድረስ ወደህጋዊ መስመር በማይገቡት ላይ እርምጃ እንደሚወስድ አስጠንቅቋል። በተጭበረበር ሰነድ የሚኖሩ እንዳሉ ቁጥርና የሰነዳቸውን ዓይነት ጠቅሶም ጉዳዩን አጥንቶ እንደጨረሰና ለእርምጃ መዘጋጀቱን ፍንጭ ሰጥቷል።
ከተፈቀደላቸው የጊዜ ገደብ በላይ የሚኖሩና በህጋዊ መስመር ያልገቡ የተለያዩ ሀገራት ዜጎች መኖራቸውንም ያስታወቀው የኢሚግሬሽንና የዜግነት አገልግሎት፣ በሕገወጥ መልኩ በኢትዮጵያ የሚኖሩና የሌላ ሀገር ዜግነት ያላቸው አካላት ወደህጋዊ መስመር የማስገባት ስራን አስመልክቶ ዜናውን ይፋ ያደረገው ለመገናኛ ብዙኃን መግለጫ በሰጠበት ወቅት ነው።
የኢሚግሬሽንና የዜግነት አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር ሰላማዊት ዳዊት በሰጡት መግለጫ እንዳስታወቁት፤ በርካታ የውጭ ሀገር ዜጎች ሀሰተኛ ቋሚ የመኖሪያ ፈቃድ፣ ሀሰተኛ ጊዚያዊ የመኖሪያ ፈቃድ፣ ሀሰተኛ ፓስፖርት፣ ሀሰተኛ ቪዛ፣ እና ሀሰተኛ ሰነድ አዘጋጅተው በሀገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች እየኖሩ መሆኑን አስታውቀዋል።
የዳይሬክተሯን መግለጫ ጠቅሰው የአገር ውስጥ መገናኛዎች እንዳሉት ከሆነ አገልግሎቱ ባደረገው የማጣራት ስራ ከ18 ሺህ በላይ ሀሰተኛ ጊዚያዊ የመኖሪያ ፈቃድ፣ ከ1ሺህ 500 በላይ ሀሰተኛ ቪዛ እና ከአንድ ሺህ 800 በላይ የትውልደ ኢትዮጵያዊ መታወቂያን ያሰሩ ዜጎች በሀገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች መገኘታቸውን ይፋ አድርጓል። ሃሰተኛ ሰነዱ የኢሚግሬሽንና የዜግነት አገልግሎት በሌብነት ያድለው ስለመሆኑ በመግለጫው አልተገለጸም።
የኢሚግሬሽንና የዜግነት አገልግሎት ሃላፊዎችንና ሰራተኞች ከደላሎች ጋር ትስስር ፈጥረው በከፍተኛ ደረጃ ያሰራጩት ሃሰተኛ ሰነድ የወሰዱ ግለሰቦች መለየታቸውን ጠቅሰን ዜናውን መዘገባችን አይዘነጋም።
እነዚህንና ሌሎች ህገወጥ ሰነድ ያለቸው ዜጎች ከጥር አንድ ቀን 2016 ዓ.ም እስከ ጥር 30 ቀን 2016 ዓ.ም ድረስ ወደ ተቋሙ በመምጣት ህጋዊ ሰነድ እንዲዘጋጅላቸው የማያደርጉ ከሆነ እርምጃ ይወሳዳል ሲሉ ዳይሬክተሯ አሳስበዋል።
በሕገወጥ መልኩ በኢትዮጵያ የሚኖሩ እና የሌላ ሀገር ዜግነት ባላቸው አካላት ላይ በተጠቀሰው ጊዜ ህጋዊ ሰነድ እንዲዘጋጅላቸው ካለደረጉ መንግስት እርምጃ እንደሚወሰድ ያፋ አድርገዋል። በየትኛውም የዓለም ክፍል ህጋዊ ሰነድና ማንነት በአንድ አገር ለመኖር የሚጠየቁ የህግ ጥያቄዎችና መስፈርት በመሆናቸው መንግስት ዘግይቷል ካልተባለ በቀር ቅሬታ የሚያነሱ ይኖራሉ ተብሎ አይጠበቅም።
በዝርክርክ አሰራርና በቁጥጥር አናሳነት ሲወቀስ የቆየው መንግስት የደህነት፣ የፕሊስና የጸጥታ ሁለንተናዊ መዋቅሩን ከሽግግሩ በሁዋላ እንደ አዲስ ገንብቶ አሁን ላይ ህገወጥ አካሄዶችን፣ ሌብነትና ዝርፊያን ለመቆጣጠር ሰፊ ዘመቻ መጀመሩን የፌደራል ፖሊስ በቅርቡ ማስታወቁ አይዘነጋም። ከኮንትሮባንድና ከተደራጀ ደረቅ ወንጀል ጋር በተያያዘ በርካታ የውጭ አገር ዜግነት ያላቸው ተሳታፊ እንደሆኑ በተደጋጋሚ ሲገለጽ መቆየቱ አይዘነጋም።