በቴ ኡርጌሳ ቅርበት ወደ መቂ የተጓዙት ከከተማዋ አቅራቢያ ያላቸው የፓፓያ እርሻ ለመመልከት ነበር ተብሏል። የተለያዩ የዜና አውታሮች እንዳሉት ሟች መቂ የትውልድ ከተማቸውም ናት። የኦነግ የፖለቲካ ኦፊሰር አቶ በቴ ኡርጌሳ በትውልድ ከተማቸው መቂ መገደላቸው ከተሰማ ብሁዋላ የተለያዩ መረጃዎች ቢወጡም ማን እንደገደላቸው ፍንጭ የሰጠ አካል የለም። በዚሁ መነሻ “ማን ገደላቸው?” የሚለው ጥያቄ ግን በርክቷል። መንግስትም ገዳዩን ለይቶ ይፋ እንዲያደርግ ጥያቄ ቀርቦለታል። የኦርሞሚያ ክልልም ምላሽ ሰጥቷል።
በተደጋጋሚ ታስረው የነበሩት የአቶ በቴን ግድያ አስመልክቶ “አቶ በቴ በመቂ ከተማ አርፈው ከነበረበት የሆቴል ክፍል ውስጥ እንዲወጡ ከተደረጉ በኋላ ተገድለው አስክሬናቸው መንገድ ላይ ተጥሎ ተገኝቷል” ሲሉ የቅርብ ጉደኛቸው እንደነገሩት ጠቅሶ አማራኛው ቢቢሲ ዘግቧል። ይሁን እንጂ ማን፣ እንዴትና መቼ ካረፉበት ሆቴል እንዳስወጣቸው፣ ምስክርነቱን የሰጡት ወገኖች ይህ ሲሆን እንዴት ሊመለከቱ እንደቻሉ በዜናው አልተብራራም። ይህን እንዲያብራሩ ስለመጠየቃቸውም የተባለ ነገር የለም። ከሆቴል እንዲወጡ ከተደረገ በሁዋላ መገደላቸውን ለቢቢሲ ያስረዱት ወገኖች “የአቶ በቴ ኡርጌሳ ላይ ግድያውን ማን እንደፈጸመው አናውቅም” ብለዋል።
አድሮ በተሰማ ዜና አቶ በቴ ወደ መቂ ሲሄዱ አዘውትረው ከሚያርፉበት “አበበ ግራዝማች ፔኒሲዮን” ያረፉ ሲሆን፣ ግድያው የተፈጸመባቸው በሁለተኛው ሌሊት እንደሆነ ቢቢሲ እማኞችን ጠቅሶ አመልክቷል።
ይህንኑ ተከትሎ ጥያቄ የሚያነሱ “የሆቴሉ ጥበቃ ይህ ሁሉ ሲሆን ቢያንስ መከላከል ባይችል፣ እንዴት ለምርመራ መሪ የሚሆን አንኳር መረጃ ሊሰጥ ሳይችል ቀረ” እያሉ ነው። “በተለያዩ መገናኛዎች ምስክር የተደረጉ ወገኖች እንዴት ስለገዳዮቹ ፍንጭ መስጠት ተሳናቸው?” የሚሉ ወገኖች ” ሟች ከሆቴል ሲወሰዱ በሆቴሉ ውስጥ አየሁ ሰማሁ የሚል መረጃ ሰጪ አለመኖሩ እንቆቅልሽ ነው” ባይ ናቸው።
ወደ አንድ ሆቴል ለያውም በለሊት ዘልቀው የሚገቡ አካላት ማንነት መጠየቅ የተለመደ እንደሆነ የሚናገሩ ወገኖች ደግመው ደጋግመው ከሆቴሉ አካባቢ ፍንጭ አለመገኘቱ በቀላሉ የሚቀበሉት ጉዳይ አልሆነም። “አንድን የሚታወቅ፣ የሆቴሉ ደንበኛ የሆነ ሰው አስረው ለግድያ ሲያጓጉዙ የሆቴሉ ጥበቃ ምን አደረገ? ወይስ የት ነበረ? ወይስ ታግቶ ነበር? ወይስ … ?” የሚሉ ወገኖች ተያያዥነት ያላቸው የስጋት ጥያቄዎች አሉዋቸው።
በግድያው መንግስትን የከሰሱ አሉ። የመቂ ከተማ ከንቲባ አቶ ዲልቦ ኡርጌሳ ለአሜሪካ ድምጽ በሰጡት ቃለ ምልልስ ግድያው የተፈጸመው ቤተሰብ መካከል በተፈጠረ አለመግባባት መሆኑን ገልጸው፣ ጉዳዩን ለማጣራት ምርመራ እንደሚያደረግ አመልክተዋል። ፖሊስ ሟች ተገድለው ከወደቁበት ስፍራ ጥያት ለቅሞ መውሰዱን አይተናል የሚሉ ለቢቢሲ አስታውቀዋል። የመቂ ከተማ ከንቲባ ለሰጡት አስተያየት ቤተሰብ ተቃውሞውን አስምቶ ” ይልቁኑ ፍርድ ስጡን” ሲሉ ተማጽነዋ።
በየትኛውም መስፈርት ግድያው ሊወገዝ የሚገባውና ገዳዮችን ለህግ የማቅረብ ስራ ባስቸኳይ ሊከናወን እንደሚገባ በርካቶች ጠይቀዋል። ኦነግ፣ የኦሮሚያ ክልላዊ መንግስትና በገለልተኛነቱ የሚከሰሰው የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን “የፍርድ ያለህ” ብለዋል። ቤተሰቦችም በተመሳሳይ “የፍትህ ያለህ” ሲሉ ተደምጠዋል።
ግድያዉን በማውገዝ ነጻ፣ ገለልተኛ፣ ከአድሏዊነት የጸዳ አፋጣኝ ምርመራ እንዲደረግ ጠይቆ ኦነግ መግለጫ አውጥቷል። በተመሳሳይ የኦሮሚያ ክልልም ምንም እንኳን የፖለቲካ ልዩነት ቢኖርም ግድያው ሊወገዝ እንደሚገባ ጠቅሶ ምርመራው ሲጠናቀቅ ለህዝብ ይፋ እንደሚደረግ አመልክቷል። ግድያውን ተከትሎ የሚሰራጨውን በመላምት የታጀበ ፕሮፓጋንዳም ክልሉ አውግዟል።
ኦነግ በመግለጫው የፓርቲው አባል እና የፖለቲካ ኦፊሰር ጃል በቴ ኡርጌሳ ዘግናኝ እና አሰቃቂ በሆነ ሁኔታ መገደላቸውን አመልክቶ የተሰማውን ሀዘን ገልጿል።” በነቁ የኦሮሞ ፖለቲከኞች እና በታዋቂ ሰዎች ላይ የሚደረገው ግድያ ቀጥሏል ” ያለው ኦነግ የታዋቂውና ተወዳጁ አርቲስት ሀጫሉ ሁንዴሳ ግድያ ሳይረሳ እና ቤተሰቦቹ እስካሁን ፍትህ ሳያገኙ የበቴን ኡርጌሳን ግድያ መስማት እጅግ አሳዛኝ መሆኑን አመልክቷል። ሃጫሉ ሁንዴሳ ከመሞቱ በፊት ከየትኞቹ ወገኖች ዛቻና የግድያ ማስፈራሪያ ይደርስበት እንደነበር ስም ጠቅሶ በይፋ መናገሩ የሚዘነጋ አይደለም። ኦነግ በተደጋጋሚ በዚህ ጉዳይ ላይ ጥርት ያለ መረጃ ሰጥቶም አይውቅም።
ጃል በቴ በተወለዱበት መቂ ከተማ በጥይት መገደላቸውን የኦነግ መግለጫ አረጋግጧል። ” ምንም እንኳን ሁኔታው ለሁላችን እጅግ በጣም ከባድ ቢሆንም በግድያው ላይ ተጨማሪ ምርመራ እያደረግን ነው ” ብሏል። ዛሬ ስማቸውን የደበቁ የህክምና ባለሙያ እንደነገሩት የጠቀሰው ቢቢሲ ሟች በጥይት መደብደባቸውን አረጋግጠዋል። ቤተሰብም አስከሬን ሲያነሱ ያዩትን ምስክርነት ሰጥተዋል።
መቀመጫውን ናይሮቢ እንዳደረገ ያስታወቀው ጃዋር መሃመድም አቶ በቴ ደግ፣ ሩህሩህና ቂም እንደማያውቁ ጠቅሶ “ማን ሊገላቸው ይችላል” ሲል ህልፈታቸውን አስመልክቶ በግል የማህበራዊ አውዱ ጽፏል።
ግድያውን ተከትሎ የሚሰራጨውን ቅስቀሳ ያልተገባና አግባብነት የሌለው መሆኑንን ያመለከተው የኦሮሚያ ክልል ከለውጡ በሁዋላ የዴሞክራሲ አውድ እንዲሰፋ ዋጋ መከፈሉን አውስቷል። ይህን ሃቅ መካድ እንደማይቻል ጠቅሶ ከአቶ በቴ ግድያ ጋር ንክኪ ያላቸው ወንጀለኞችን ህግ ፊት ለማቅረብ በቁርጠኛነት እንደሚሰራ አመክቷል። አይይዞም የፖሊስ የምርመራ ውጤት ሲጠናቀቅ ይፍ እንደሚሆንም አስታውቋል።
ከተለያዩ ወገኖች የሚሰሙ መረጃዎች የሟችን አሟሟት ልብ ሰባሪነት፣ አሳዛኝነትና ጭካኔ የተመላው መሆኑን ከመግለጽ ውጪ በምርመራ ላይ የተመሰረተ ሪፖርት የቀረበበት አይደለም። አሜሪካ ግድያው በገለልተኛ ካል እንዲጣራ መንግስት እንዲፈቅድ ጥያቄ ማቅረቡን ቪኦኤ ዘግቧል።