ሰሞኑንን ለይቶለት ይፋ ሆነ እንጂ ውስጥ ውስጡን የጦርነት እንቅስቃሴ ሲደረግ እንደነበር መረጃዎች ከበቂ በላይ ነበሩ። ለዚህም ይመስላል ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ ” ንገሩዋቸው፣ ምክሩዋቸው” ሲሉ ከትግራይ ህዝብ ተወክለው ከመጡ ጋር ሲወያዩ ደጋግመው ያስታወቁት። በወይይቱ ላይ የተገኙ እናቶችም ” ካሁን በሁዋላ” ሲሉ ጦርነቱ ያስከተለው መዘዝና ጠባሳ እያንዘፈዘፋቸው ” ልጆቻችንን አንሰጥም” ሲሉ የተሰሙት።
የድንበርና የማንነት ውዝግብ ያልተለየው የአማራና የትግራይ ክልል በግልጽ የህዝብ ጥያቄ የነበረበት መሆኑ አይካድም። የህዝብ ጥያቄ በተለያዩ አግባቦች ሲቀርቡና ሃይልን ጨምሮ የተለያዩ ግብረ ምላሾች ሲሰጡ መቆየቱም የሚካድ አይደለም። እናም ይህ ጥያቄ ሁሉንም በሚያስተናግድ መልኩ ምላሽ እንዲያገኝ ” ህዝብ ራሱ የሚወስንበት ህገ መንግስታዊና ዓለም ዓቀፋዊ መርህ የተከተለ መላ ይፈለግለት። እሱም ህዝብ ውሳኔ ነው። ከዚያ ቀድሞ ግን የተፈናቀሉ ይመለሱ” በሚል ግብ ተቀምጦ ወደ ስራ ቢገባም አሁን ላይ የትግራይ ሃይሎች በራያ አላማጣ በኩል በስም የተጠቀሱ ቀበሌዎችን ይዘዋል። አላማጣንም ከበዋል።
አማራ ክልል ባወጣው መግለጫ ቀደም ሲል የትግራይ ባለስልጣኖች ” ነጻ ወጥተዋል” ያሉዋቸው ቀበሌዎችና አካባቢዎች ” ለራተኛ ጊዜ ተወረዋል” ብሏል። የራያ አላማጣ፣ ራያ ባላ፣ ኦፍላ፣ ኮረም እና ዛታ ዳግም በትግራይ ሃይሎች መያዛቸውን ዘርዝሮ አመልክቷል።
አቶ ጌታቸው ረዳ ይህን የፈጸሙ ውገኖች የፕሪቶሪያው ስምምነት ተግባራዊ እንዲሆን የማይፈልጉ ከዛም ከዚህም አካላት ያደረጉት እንደሆነ ጠቅሰው ችግሩ የፌደራል መንግስትና የትግራይ ክልል ወይም የትግራይ ክልልና የአማራ ክልል እንደሆነ አድርገው የሚያቀርቡ ወገኖች የተሳሳቱ መሆናቸውን ዘወትር ለዓለም ዓቀፉ ሚዲያና ህብረተሰብ መረጃ በሚያደርሱበት የኤክስ ገጻቸው አስፍረዋል።
ከአላማጣና አካባቢው ህዝብ እየተፈናቀለ ወደ ቆቦ እየሸሸ እንደሆነ ምስክሮች ለሚዲያ ተናግረዋል። የሸሹት ራሳቸውም አመልክተዋል። የትግራይ ሃላፊዎችም ስም ጠቅሰው “አካባቢዎቹ ከታጣቂዎች ነጻ ሆነዋል” ሲሉ ተናግረዋል። በአቶ ጌታቸው መዋቅር ውስጥ ያሉ የአስተዳደር አካላት ይህን በመሰከሩበት አኳዃን የአቶ ጌታቸው መረጃ ምን ያህል ይታመናል የሚለው ያለፈውን የሰውየውን የአፈ ቀላጤነት ዘመን ንግግር ጋር ተመሳሳይ እንደሆነ እየተገለጸ ነው።
እሳቸው ከአማራ ክልል ጋር ጸብ እንደሌለ በመመካከር እየተሰራ መሆኑን ባስታወቁ አንድ ቀን ሳይሞላ አማራ ክልል ” ፖለቲካዊ ግልሙትና” ሲል ተቃውሞውን ባሰማበት መግለጫ አቶ ጌታቸውን የሚመሩትን ክልልና ድርጅት ” ከጦርነት አዙሪት የማይወጣ” ሲል ኮንኖ ህዝቡን ለመታደግ እንደሚገደድ አመልክቷል። ወንድም ሲል ለጠራቸው ክልሎችም የፍትህ ያለህ ሲል ጥሪ አቅርቧል። የፌደራል መንግስትም አቋም እንዲይዝና ትህነግን እንዲያስታግስ ጠይቋል።
ሁሉም በየፊናቸው የሚሉትን እንተወውና ከዚህ ቀደም በሶስት ዙር ከትግራይ ተነስቶ ትህነግ አማራና አፋር ክልልን ሲወር የደረሰውን ሰብአዊና ኢኮኖሚያዊ፣ ከዚያም በላይ የስነልቦና ቀውስ ለሚያስታውስ ዳግም ወደ ጦርነት መግባት እንዴት ይታሰባል የሚለውን ማንሳቱ ግድ ይላል።
የኢትዮጵያ የገንዘብ ሚኒስትር ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን፣ በጀት እና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ባቀረቡት ሪፖርት በሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነት ምክንያት ሀገሪቱ 28 ቢሊዮን ዶላር የሚገመት በአሁኑ የውጭ ምንዛሪ 1.5 ትሪሊዮን ብር ኪሳራ ማድረሱን አስታውቀዋል። በሪፖርቱ ጦርነቱ ሦስት ሚሊዮን ዜጎች ለከፋ ድኅነት እንደተዳረጉም ተጠቁሟል። ይህ የመንግስት አፍ ነው።
ከትግራይ የወጡ መረጃዎች እንደሚያሳዩት ትግራይ ወድማለች። ትግራይ ብቻ አንድ ሚልዮን የሚጠጋ ሰዎችን አጥታለች። አካላቸው የጎደለው ጥቂት አይደሉም። ህሳጻናት ከትምህርት ገበታቸው ተገልለዋል። በጭንቀትና ትራኡማ ተጎድተዋል። ህክምና አልነበረም። አገልግሎት የለም። ጨላማ ነበር። እጅግ ለጆሮ የሚቀፉ ተግባራት ተፈጽመዋል። አጋጣሚው ሰርግና ምላሽ የሆነለት ሻዕቢያም ወሮ ዘርፏቸዋል። ደፍሯቸዋል። ታሪክ የማይረሳው ግድያና ወንጀል ፈጽሞባቸዋል።
በአማራ ክልልም የተፈጸመው ውድመት፣ ዝርፊያ፣ ግድያ፣ በደፈናው ቤት ይቁጠረው ካልተባል በስተቀር ተዘርዝሮ አያልቅም። አፋር የሆነው ሁሉ ልብ የሚያደማ ነው። ያ ሁሉ የሆነው በእብሪት፣ በስልጣን ጥማት እንጂ ለህዝብ ጥቅም ሲባል አልነበረም። ያማ ቢሆን ኖሮ ትህነግ በስልጣን ላይ በነበረበት ወቅት የህዝብ ጥያቄ መልሶ፣ የትግራይን ህዝብ ከሴፍቲ ኔት ተረጂነት አላቆ ራሱን ባስቻለ ነበር። ለሰላሳ ዓመታት የተሰጠውን ዕድል ሳይጠቀም ዳግም ትግራይን ጦርነት የከተተው ትህነግ ዛሬም ወደ ለመደው ግጭት ማምራቱ የቀደመውን ስህተት ከመድገም ውጪ ለትግራይ ህዝብም ሆነ አጎራባች ክልሎች የሚያመጣው በረከት የለም።
ጦርነት ከተጀመረ ነገም መንገድ ይዘጋል። አገልግሎት ይቆማል። የእህል፣ ነዳጅ፣ መድሃኒትና የመሳሰሉ አቅርቦቶች ይቆማሉ። የሰው ልጅ ይረግፋል። በተጀመረው አግባብ የይገባኛልም ሆነ የማንነት ጥያቄዎች እጅግ በስለጠነ አግባብ፣ በዓለም አቀፍ ተሞክሮዎች ታጅቦ ማከናወን ሲገባ ወደ ዳግም ጦርነት ማምራቱ በርካቶችን ያሳዘነው ውጤቱ ከቀደመው ይብስ እንጂ ያነሰ ሊሆን እንደማይችል ሰፊ ማሳያዎች በመኖራቸው ነው።
ከአማራ ክልልም ቢሆን የተፈናቀሉ ነጹሃን ዜጎች ቀድመው ወደ ቀያቸው በነጻነት እንዲመለሱ በግልጽ መስራትና የተጎዱትን በፍቅር መንከባከብ ይገባዋል። ተፈንናቃዮችን መመለስ በቃላት ደረጃ ሳይሆን በተግባር፣ በርህራሄ ታጅቦ ነገ ዛሬ ሳይባል ሊፈጸም ግድ ነው። በየቦታው ነፍጥን አንግበው በማይታወቅና ውል በሌለው አጀንዳ ክልሉን ሰላም የምንትነሱ “እጄን በጄ” እዳይሆንባችሁ ደጋግማችሁ በማሰብ ወደ ሰለጠነው አግባብ መመለስ እንደሚሻል በመረዳት ህዝብ ላይ የተደቀነውን አደጋና ስጋት ለመግፈፍ መረባረቡ ይበጃል።
“በሌሎች ክልሎች ዜጎች በነጻነት ሊኖሩ ይገባል” በሚል አክራሪ፣ ገዳይና አስገዳይ ሽፍቶችን የሚያወግዙ፣ ቀድመው ከነሱ ክልል የተፈናቀሉ ሰላማዊ ዜጎች እንዲመለሱ በማድረግ ሰብ አዊነታቸውን ማሳየት ሲገባቸው፣ በሴራና በውስጥ ለውስጥ ቁማር ሌላ ጦርነት እንዲነሳና አገሪቱ የቀራትን በሙሉ አውድማ ባዶ እንድትሆን የተጀመረው ሩጫ ካልቆመ በሁዋላ ለጸጸትም ጊዜ አይኖርም።
አቶ ጌታቸውም ሆኑ ሌሎች የትግራይ ባለስልጣናት አጉል የሆነውን የተለመደ የቃላት መገለባበጥ አቁሙ። ህዝብ ያስጨረሳችሁት በተመሳሳይ ቅስቀሳና ቅጥፈታችሁ መሆኑንን አትርሱ። አንድ ሚሊዮን ህዝብ አስጨርሳችሁ ስታበቁ፣ ያላችሁትንና ስትፎክሩ የነበረውን ሁሉ ዘንግታችሁ ” የሰላም ያለህ” ብላችሁ ተመልሳችሁ አራት ኪሎ ሻምፓኝ ጠጥታችኋል። ዞራችሁ ቁማራችሁን ለትቀጥሉ ህዝብ አትማግዱ። ቁጭ በሉና ተወያዩ። ህዝብ ትግራይም ይሁን በመላው አገሪቱ የናንተ ፕሮፓጋንዳ እንደሰለቸው እወቁ። ከምንም በላይ የእናንተ ሴራ መከራ ላይ የጣለውን ህዝብ አስቡ። በየስርቻው የወደቀውን ዜጋ ብዛትና የመከራ ጥልቀት ገምግሙ። አካላቸው ጎድሎ ለማኝ ያደርጋችኋቸውን ዜጎች ተመልከቱ….
ያን ሁሉ የጦርነት ቅስቀሳና ፕሮፓጋንዳ በዓለም ዙሪያ ስታሰራጩ ያሳለፋችሁትን ጊዜ፣ የተከተለውን ውጤት፣ በዚሁ ቅስቀሳችሁ ያለቀውን ህዝብ ለአፍታ አስቡና እባካችሁን ወደ ሰላማዊው መንገድ ተመለሱ። ሁሉንም በውይይት ለመፍታት ሆደ ሰፊ ሁኑ። ህዝብ ማንም መራው ማን የሚፈልገው ሰላምና የእለት ጉርስ ነውና ይህንን አትንፈጉት። ያረጀ የዘር ፖለቲካ አራግፋችሁ ጣሉ።
አሁን አላማጣ ተከባለች። አላማጣ በፌደራል ፖሊስና መከላከያ ስራ ናቸው ። እነሱን ደምስሰን አላማጣን እንይዛለን ስትሉ መከላከያ ዝም አይልም። መንግስትም ዝም አይልም። ህዝብም ዝም አይልም። ክልሎች ሁሉ ዝም አይሉም። አፋር ክልልም ” ነግ በኔ” ማለቱ አይቀርም። አማራ ክልልም የውስጥ ቁርቁሱን አቁሞ ማበሩ የማይታበል ሃቅ ነው። ወልቃይትም ” በለተራ ነኝ” ብሎ መነሳቱ አይቀርም። እንደተለመደው ሻእቢያም እንደራበው ጅብ ተንደርድሮ ዳግም ዝርፊያና ግድያ ላለመፈጸሙ ዋስትና የለም።
መንግት ደጋግሞ እንዳስታወቀ ካሁን በሁዋላ የሚደረጉ ውጊያዎች ቲክኖሎጂ መሰረት ያደረጉ ናቸውና ጉዳቱ ከፍተኛ ነው። እንደ ቀድሞ በህዝብ ማዕበል የሚሆን ነገር የለም። ለጊዜው ሊመስል ይችላል እንጂ አያዋጣም። የመከላከያ አመራሮችና መንግስት ደጋግመው “ምከሩ” ያሉት ለዚህ እንደሆነ ጥርጥር የለውም። ዛሬ ባለው መረጃ የኢትዮጵያ መከላከያ ቀደም ሲል ከነበረው በስምንት እጥፍ አድጓል። በአምስት እጥፍ ተበልጦ በነበረበትና ትጥቁን በተዘርፈበት ወቅት ያልተሸነፈ ሰራዊት ዛሬ ይረታል ማለት የሚቻል ስለመሆኑ ደጋግሞ ማሰብ ደግ ነው።
በቅርቢ የፕሪቶሪያውን ስምምነት አስመልክቶ በተደረገ ግምገማ የተወሰነው ውሳኔ የሚታወቅ ነውና የቀደመው ዓይነት የፖለቲካ ትርፍ ማግኘት እንደማይቻል የግምገማው ማሳረጊያ የውሳኔ አሳብ ሰነድ ያዩ መስክረዋል። ይህ ለሁሉም ወገኖች ግልጽ ነውና አማራ ክልልም ሆነ የትግራይ ክልል ህዝብ አብሮ የሚኖርበትን መላ ቁጭ ብለው ቢያሰሉ ውብ ይሆናል።
አማራ ክልልን በመውረር “ከአማራ ሃይሎች ጋር እንሰራለን” የሚለው ቅስቀሳ አጉል ቀልድ መሆኑን በመረዳት አቶ ጌታቸው እንዳሉት ከልብ ውይይት ቢቀድም ይበጃል። ይህ ሳይሆን ቀርቶ ዳግም ጦርነት ከተነሳ ለቅሶም፣ ጩከትም፣ ሰልፍና እንጉርጉሮ የሰው ልጅን ህይወት የሚተኩ አይሆንም። ጦርነት ይብቃን!! የፍጀውን ጊዜ ቢፈጅም ለውይይት ብቻ ዕድል ይሰጥ። ሳናገገም ዳግም ውድመትና ሞትን መሸከም የሚችል ጫንቃ ያለው አገርም ሆነ ህዝብ የለንም።